በ“ሳምንቱን በታሪኩ” አምዳችን ላይ በኢትዮጵያ ውስጥ ነግሰው የነበሩትን አፄ ልብነ ድንግልን ለማስታወስ ወደናል። ሁሌም እንደምናደርገው ሁሉ በአገረ መንግስት ግንባታ ላይ ጉልህ ድርሻ ያላቸውና የማይፋቅ አሻራን አሳርፈው ያለፉ ነገስታትንና ስራዎቻቸውን እናወሳለን። ወርሃ ነሃሴ አያሌ ታሪካዊ ክንውኖች የያዘ ነው። በዚሁ ወር መጨረሻ ማለትም ነሃሴ 30 1532 ዓም ደግሞ እኚሁ ዛሬ ርእሰ ጉዳያችን አድርገን ልናወሳቸው የወደድናቸው ንጉሰ ነገስት አፄ ልብነ ድንግል ህይወታቸው ያለፈበት እለት ነው። ለዚህም ነው በርከት ያሉ ዘመናትን ወደኋላ መለስ ብለን ትውስታን ለመጫር የወደድነው። ለመሆኑ “አፄ ልብነ ድንግል”ና በአገዛዝ ዘመናቸው የነበረው ታሪክ ምን ይነግረናል?
ልብነ ድንግል
አጼ ልብነ ድንግል “የአጼ ናኦድ ልጅ የአጼ በእደ ማርያም የልጅ ልጅ” መሆናቸውን የታሪክ መዛግብት ይነግሩናል። አጼ ዘርዓ ያዕቆብ ደግሞ ቅድመ አያታቸው እንደነበሩ ዜና መዋእሎችና የታሪክ ምሁራን ይገልፃሉ። እኚህ እንቁ የኢትዮጵያ ልጅ አባታቸው አጼ ናኦድ ለ13 ዓመት ገዝተው በ1500 ዓ.ም ሲሞቱ እርሳቸው ገና የ12 ዓመት ታዳጊ ነበሩ። በዚህ ምክንያት ገና በለጋ እድሜያቸው (ማለትም በ12 አመታቸው) የንግስና ዙፋኑን የመረከብ ከባድ ሃላፊነትን ለመሸከም ተገድደው ነበር። በግዜው ስመ መንግሥታቸውም “ወናግ ሰገድ” እንዲባልም ተወሰነ። በግዜው በኢትዮጵያ ውስጥ ንጉስ አክሊሉን በሚደፋበት ወቅትና የንግስናውን ካባ በሚደርብበት ግዜ “ስመ መንግስት” ይወጣ ነበር።
በአዲስ ዘመን ክምችት ክፍል ዜና መዋእልንና የታሪክ ምሁራንን ጠቅሶ ከዓመታት በፊት ባወጣው ፅሁፍ የአፄ ልብነ ድንግል ታሪክ ላይ የወጣላቸውን ስመ መንግስት ትርጉም እንዲህ ብሎ ያስቀምጠዋል “ወናግ ማለት በውጋዴን ቋንቋ አንበሳ ማለት ነው። የግዕዙን ወይም የአማርኛውን ቋንቋ “አንበሳ” ሰገድነን ትተው በውጋዴን (ሱማሌ) ቋንቋ ወናግ ሰገድ የተባሉበት ምክንያት ምናልባት ያን ጊዜ በይፋትና በፈጠጋር ያለውን ግዛት የሚያውኩ ያዳልና የሱማሌ ተወላጆች ስለነበሩ እነርሱ በሚያውቁት ቋንቋ ተሰይሞ ለማስፈራራት ይሁን ወይም የእነርሱ ገዢ ጭምር መሆናቸውን ለማስተዋወቅ አሊያም ከአባታቸው ከአጼ ናኦድ ስመ ነገስት (አንበሳ ሰገድ) በትርጉም ቢቀር በአጠራር እንዲለይ መሆኑ በትክክል አይታወቅም”
የንግስና ዘመን
ተክለ ጻዲቅ መኩሪያ “የኢትዮጵያ ታሪክ ከአጼ ልብነ ድንግል እስከ አጼ ቴዎድሮስ” በተሰኘ መጽሐፋቸው አጼ ልብነ ድንግል በነገሱ ጊዜ ወጣት ስለነበሩ እናታቸው እቴጌ ናኦድ ሞገሳና የቅድመ አያታቸው የአጼ በእደ ማርያም ባለቤት እቴጌ እሌኒ በሞግዚትነት ያግዟቸው እንደ አትተዋል። በዚህም ለረጅም ዓመት ኢትዮጵያንና ህዝቦቿን ፍትህ አስፍነው፣ ህግና ስርዓትን ጠብቀው፣ ወግ ባህሉን አበልፅገው መግዛታቸውን ፅፈዋል። ይሁን እንጂ በመጀመሪያ ስርዓታቸው የሰላምና የደስታ ቢሆንም የመጨረሻ ጊዜያቸው በግራኝ መነሳት ምክንያት የጦርነት፤ የሁከት፤ የመከራና የስደት ጊዜ ማሳለፋቸውን የታሪክ ተመራማሪው መረጃዎችን በማጣቀስ መዝግበዋል።
ንጉሰ ነገስት ዓፄ ልብነ ድንግል በግዜው ጠንካራ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያደርጉ እንደነበር የታሪክ መዛግብት ያትታሉ። በደህናው ግዜ ያፈሩት አጋርም በችግር ድጋፍ ሲሹ ወዳጅ ከጎናቸው እንዲኖር ማድረጉን ይነገራል። በተለይ ደግሞ ከአረብና ቱርክ መንግሥታት ድጋፍ እያገኘ የወጋቸውን ግራኝ አህመድን ለመመከት ፖርቹጋሎች እንዲረዷቸው በተጻጻፏቸው ደብዳቤዎችና ዲፕሎማሲያዊ ብልሃታቸው የተነሳ መሆኑን የተለያዩ መዛግብት ያትታሉ።
የተዛባውን ትርክት ለማረም
የታሪክ ተመራማሪውና ፀሃፊው ተክለ ፃዲቅ መኩሪያ የአጼ ልብነ ድንግል ጦር በሽምብራ ኮሬ ጦርነት ቢሸነፍም ጨርሶ ሊወድቅ አለመቻሉን በመፅሃፋቸው ላይ አስፍረዋል። በጦርነቱ ብዙ መኳንንት ቢያልቁም የግራኝ አህመድ ጦር “አንዱን አውራጃ አስገበርኩ ፤ ሹሙን አሰለምኩ፤ ገደልኩ ማረኩ” ይበል እንጂ ንጉሱንም ለመማረክ ከፍተኛ ጥረት ቢያደርጉም ሳይሳካላቸው መቅረቱን ነው የተረኩልን።
በበርካታ የታሪክ ምርምር ስራዎቹ የሚታወቀውና በተለይ የታሪክ ብዥታዎችን በማጥራት የተሳካለት ስራ የሚሰራው ልጅ ተድላ መላኩ በበኩሉ ንጉሰ ነገስቱን አፄ ልብነ ድንግል በመጨረሻው ዘመናቸው የገጠማቸውን የህልውና ጦርነትና እርሱን ለመመከት የሄዱበትን ርቀት መረጃዎችን በመጥቀስ በስፋት በስራዎቹ ላይ ማስፈር ችሏል። ዝርዝር ጉዳዩን ከታሪክ ተመራማሪው ቀጥተኛ በማስረጃ የተደገፈ ትንታኔ ከዚህ እንደሚከተለው እናገኘዋለን።
“ታሪክ ላይ አፄ ልብነ ድንግል እና የምስራቁ ወላሽማ/ አዳል ሱልጣኔት ግዛት መሪ የነበረው ሃደሬ-ሶማሌው አሕመድ አል ግሀዚ (አሕመድ ግራኝ) ያካሄዱት ጦርነት ከመሰረቱ ፖለቲካዊ እንጅ ሃይማኖታዊ ጦርነት እንዳልነበር የታሪክ ተመራማሪዎች ያትታሉ። የዚህም ማስረጃ አሕመድ ግራኝ አፄ ልብነ ድንግል ሴት ልጃቸውን ከዳሩለት ውጊያውን እንደሚተው የላከላቸው መልዕክት ነው ምሑራዊ ምንጭ (“The Historical Geography of Ethiopia: from the first century AD to 1704”) እንደሚነግረን አሕመድ አል ግሀዚ አፄ ልብነ ድንግልን “ሴት ልጅህን ከዳርከኝ ሰላም እሰጥሃለሁ፣ አልወጋህም” የሚል ጥያቄ አቅርቦላቸው ነበር” በማለት ይናገራል።
ተመራማሪው ልጅ ተድላ በዚህ ሳያበቃ “ጉዳዩን በአግባቡ ለመረዳት የአፄ ልብነ ድንግል ቅም አያት የነበሩት አፄ ይኩኖ አምላክ በዘመናቸው ከነበረው የግብፅ ሡልጣን ጋር የተጻጻፉትን ደብዳቤ እና የምሥራቁ ሡልጣኔት (በኋላ አሕመድ ግራኝ የተነሳበትና የመራው) ከሰሎሞናዊ ነገሥታት ጋር የነበረውን የጠላትነት ምክንያትና መነሻ እና መሰረቱ ምን እንደነበረ የሚከተለውን ማስረጃ በጥንቃቄ መረዳትን ይጠይቃል” ይለናል። ለዚህም የሚከተለውን ምክንያት ያስቀምጣል። ጉዳዩን ሲያብራራም ጥልቅ ይዘትና ተዓማኒነት ያላቸው ምሁራዊ ሰነዶችን እንደሚከተለው በማጣቀስ ነው።
ሞርድካይ አቢር በቀረበው የተጠና ታሪካዊ ሃተታን እንደ መረጃ በማስደገፍ የታሪክ ተመራማሪውና ሞጋቹ ልጅ ተድላ መላኩ እንዲህ ሲል ይሞግታል “የመካከለኛው ዘመን የሰሎሞናዊ ነገሥታት አባት የሆነው አፄ ይኩኖ አምላክ ከኢትዮጵያ ሙስሊሞች ጋር በጎ ግንኙነት ነበረው። የሰሎሞናዊ ክርስቲያን ነገሥታት እንቅስቃሴ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ የነበረና ከኢትዮጵያ ሙስሊሞች ጋር በጎ ግንኙነትን የመሰረተ ነበር። ይህም ከሰባት መቶ ዘመን በፊት ነበር። አፄ ይኩኖ አምላክና እርሱን የተኩት ሰሎሞናዊ ነገሥታት የኢትዮጵያ ሙስሊሞች የንግድ መስመሮችን እንዲቆጣጠሩ በማመቻቸታቸው በኢትዮጵያ ሰሎሞናዊ መንግሥት ሙስሊሞችና በምሥራቅ (ሶማሌ) ሡልጣኔት ሙስሊሞች መካከል መቃቃር ተፈጥሮ ነበር”
ልጅ ተድላ ያስቀመጣቸው መሞገቻዎችና ማስረጃዎችን ጠቅሶ “ሰሎሞናዊ ነገሥታት የቀይ ባሕር የንግድ መስመሮች በአበሻ ሙስሊሞች እንዲያዙ በማድረጋቸው የምሥራቁ ሡልጣኔት ሙስሊሞች ከአበሻ ሙስሊሞች ጋር መቃቃር ውስጥ ገብተዋል” ይላል። ከዚያም አልፎ አፄ ይኩኖ አምላክ ለግብጽ ሱልጣን በላከው ደብዳቤ በርሱ ሰሎሞናዊ መንግሥት ውስጥ የሚኖሩ ሙስሊሞች ጠባቂ (ባለ አደራ) መሆኑን እና በርሱ መንግሥት ውስጥ አበሻ ሙስሊሞች ከአበሻ ክርስቲያኖች ጋር እኩል መብት ያላቸውና በሰሎሞናዊ መንግሥት ባለ አደራነት መብታቸው ተጠብቆ የሚኖሩ መሆኑን በማስረጃነት ይናገራል።
እውነቱ ሲጠራ
አፄ ልብነ ድንግልም ሆነ የሰለሞናዊ ነገስታት ያካሄዱት ጦርነት በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ሙስሊሞችን ለማጥቃት ታስበው የተደረጉ ናቸው የሚል የተዛባ ስሁት ትርክት ይነገራል። ይህንን ብዥታ ልጅ ተድላ መላኩ በአገር ውስጥና በውጪ ተመራማሪዎች የተደረጉ ጥልቅ ጥናቶችንና የታሪክ ማስረጃዎችን በማጣቀስ ይሞግታል “የመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያ ሰሎሞናዊ ነገሥታት ያካሄዷቸው ጦርነቶች በአበሻ ሙስሊሞች ላይ ያነጣጠሩ ሆነው አያውቁም። ያካሄዷቸው ጦርነቶች ለፖለቲካዊ የበላይነት ከተዋጓቸው የምሥራቅ ግዛት ኃይሎች ጋር እንጅ በራሳቸው ግዛቶች ውስጥ ያለውን ሕዝበ ሙስሊም አልነበረም” ይላል።
ይህ አይነት ዘመቻና ጦርነት የሰለሞናዊ ነገስታት ዓላማ ብቻ ሳይሆን የምስራቁ ወገን ተፋላሚዎችም እንደነበር ሲገልፅ “እነርሱም ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ዓላማ የነበራቸው፣ እንዲሁም በወረራና በጥቃት ምክንያት የተካሄዱ መሆናቸው በታሪክ መጻሕፍት ይገለጻሉ። ክፉ ዓላማ ያላቸው አክራሪዎች ግን ሰሎሞናዊ ነገሥታት በራሳቸው ሕዝብ ላይ ጥቃት ያደረሱና ሙስሊም የሆኑን ኢትዮጵያውያን ለይተው ያጠቁ አስመስለው በማቅረባቸው ሕዝባችን በገዛ ታሪኩ ላይ ጥያቄ እንዲያነሳና ጥርጣሬ እንዲያድርበት አድርገዋል” የሚል ብዥታን የሚያጠራ ሙግቱን ያስቀምጣል።
የሙስሊሙ ማህበረሰብና አፄ ልብነ ድንግል
የታሪክ ተመራማሪው ልጅ ተድላ “አፄ ልብነ ድንግልን የሙስሊም ጠላት አድርገው ማቅረብ የሚፈልጉ አንዳንድ ታሪክን በትክክል ያላዩ ሰዎች ብዙዎችን አሳስተዋል። አፄ ልብነ ድንግል ጦርነት የገጠመው በሃይማኖት አመካኝተው ከውጭ ኃይላት ጋር በማበር የሰለሞናዊው መንግሥት የወረሩን ጠላቶች ነው” በማለት አብዛኛውን የንገስና ዘመኑ መላው ኢትዮጵያውያን ፍትህ፣ ስልጣኔን እንዲሁም በራሱ ማንነት ላይ የተመሰረተ ጠንካራ ሃገረ መንግስት እንዲኖረው የሰራውን ታላቅ ሰው በከንቱ የታሪክ ጥላሸት መቀባት ተገቢ አለመሆኑን ይመሰክራል።
በተለይ “ግራኝ አሕመድ ከምስራቅ ተነስቶ በቱርኮችና ዓረቦች እገዛ ‘ቤተ አምሓራን’ ያጠቃ በዘመኑ ግብር ለማዕከላዊ መንግሥት ከመክፈል ውጭ ራስ-ገዝ ግዛት የነበረው የምሥራቁ ሡልጣኔት መሪ ነበር። የግራኝ አህመድም ሠራዊት አረብና ቱርኮች ነበሩ” በማለት እውነታውን ገልጧል። ይህን የታሪክ ምስክርነት እርሱ ያደረገው ምርምር ብቻ ሳይሆን “ጆርጅ ዋይን ‘ታሪካዊው የኢትዮጵያ መልከአ ምድራዊ አቀማመጥ ከመጀመሪያው ዘመን እስከ 1704’” በማለት ያተተበትን መፅሃፍ፤ ሞርድካይ አቢር “ ኢትዮጵያና የቀይ ባህር ወሽመጥ የሰለሞናዊው ስርወ መንግስት ማንሰራራትና ውድቀት እንዲሁም የቀጠናው የእስልምናና አውሮፓውያን ግብግብ” በሚል የጠረዙ የታሪክ ድርሳናትም በሰፊው አትተውታል።
ዳግም ከበደ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 30 ቀን 2013 ዓ.ም