በአሜሪካ፣ የተለያዩ የአውሮፓ ሃገራት፣ በደቡብ አፍሪካ እና በሌሎች በርካታ ሃገራት ተዘዋውረው የመንፈስ ከፍታን የሚሰጡ ሰብዓዊ ሥራዎችን ሠርተዋል። በተለይ ወጣቱን ካለመኖር ወደ ህይወት ጎዳና በመመለስ ረገድ ያከናወኗቸው ተግባራት ለብዙዎች ምሳሌ የሆኑና ለእናት ሃገራቸው ክብርን የሚቸሩ ናቸው። አርሲ አካባቢ ሚኔ በሚባል ስፍራ አድገዋል። ከገበሬ ቤተሰብ መወለዳቸው በጽናትና በትጋት ለስኬት እንዳበቃቸው ደጋግመው ይናገራሉ፤ በኢትዮጵያ የላቭ ቱ ኔሽን መስራችና ዋና ተጠሪ ማስተር ሄኖክ መገርሳ።
ከሠላሳ ዓመታት በላይ የአዕምሮን እረፍት የሚሰጡ በጎ ተግባራትን በማከናወን የሚታወቁት ማስተር ሄኖክ፤ በወጣትነታቸው ከሃገር ቢወጡም፤”ኢትዮጵያ ገብቼ በተለይ ወጣቱን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ስራዎችን መስራት የሁልጊዜ ህልምና ፍላጎቴ ነው” በማለት ደጋግመው የሚናገሩት ማስተር ሄኖክ፤ ጊዜ ለኩሉ ነውና ከአንድ ዓመት በፊት ወደ ሃገራቸው በመግባት በመሰረቱት የላቭ ቱ ኔሽን ዓለም ዓቀፍ ምግባረ ሰናይ ድርጅት ለሃገራችው ዕድገት ሲሉ፣ ወጣቱን፣ ህዝቡን ከፍ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ ወደ ተግባር ገብተዋል። ማስተር ሄኖክ ስለ አጠቃላይ ህይወትና የስራ እንቅስቃሴያቸው ከአዲስ ዘመን የዝግጅት ክፍል ጋር ሰፋ ያለ ቆይታ አድርገዋል። መልካም ንባብ።
አዲስ ዘመን፡- ቅድሚያ የት አካባቢ ተወልደው አደጉ ከሚለው እንጀምር?
ማስተር ሄኖክ፡– የተወለድኩት አምቦ አካባቢ ሲሆን እድገቴ ደግሞ አርሲ አካባቢ ሚኔ በተባለ ቦታ ነበር። ትምህርቴንም የተከታተልኩት ባደኩበት አካባቢ ነው። የገበሬ ልጅ እንደመሆኔ ስራን የጀመርኩት ገና ከልጅነቴ ነበር። ብዙ ጊዜ ከአባቴ ስር አልጠፋም ነበር። አባቴ ምርቱን ለመሸጥ ወደ ገበያ ሲሄድ ይዞኝ ነበር የሚሄደው። ከእርሱ አጠገብ አለመጥፋቴ ብዙ ነገሮችን ለመማር በር ከፍቶልኛል። ከአባቴ ደግሞ የስራ ፍቅሩ፣ ትጋቱ እንዲሁም ልግስናው እንዲጋባብኝ አድርጎኛል። በልጅነቴ የተቀረጸብኝ ስሜት ከፍ እያልኩኝ ስሄድ አብሮኝ እያደገ ነበር የሄደው። የልጅነት እድሜዬን በትምህርትና ቤተሰቤን በተለይ ወላጅ አባቴን በስራ እያገዝኩ ያሳለፍኩኝ ሲሆን፤ እድሜዬ ከፍ ሲል ወደ አዲስ አበባ መጣሁኝ።
አዲስ አበባ ከመጣሁ በኋላ የህይወቴን መስመር የቀየረ አንድ እድል ገጠመኝ። በኢትዮጵያ እርዳታ ማስተባበሪያ ድርጅት ውስጥ የመቀጠር እድል አገኘሁ። ከእንግሊዞች ጋር በመተባበር የሚሰራውን ይሕን ድርጅት ስቀላቀል ገና 17 ዓመቴ ነበር፡፡ ስራውን ደግሞ የምወደው በመሆኑ በአጭር ጊዜ ነበር አይነገብ ሠራተኛ ለመሆን የቻልኩት። ምክንያቱ ደግሞ፤ ከልጅነቴ ጀምሮ መርዳት እወዳለሁ። ከአባቴ የወረስኳቸው ባህሪያት የስራ ትጋትን እና ልግስናን ነው። የእርዳታ ማስተባበሪያ ድርጅት ሰዎችን መርዳት፣ መደገፍ ላይ የሚሰራ መሆኑ ስራዬን ወድጄውና አቀላጥፌ እንድሰራ ረድቶኛል። ከአባቴ የወረስኩት የስራ ትጋት ደግሞ የተሰጠኝን የስራ ኃላፊነት አቀላጥፌ እንድሰራ አድርጎኛል።
በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያለሁ ነበር ከእንግሊዝ የድርጅቱን እንቅስቃሴ ለመመልከት እንግዶች የመጡት። በድርጅቱ ውስጥ የስራ ትጋቴን በመመልከት ለእረፍት ወደ እንግሊዝ እንድሄድ በማበረታቻ መልኩ እድሉን ሰጡኝ። ወደ እንግሊዝ ለጉብኝት ያደረኩት ጉዞ ቢጠናቀቅም ትምህርት መማር ስለምፈልግ ወደ ሀገሬ ሳልመለስ ቀረሁ። ከትምህርቱ ባሻገር የበጎ አድራጎቱን ስራ እንድሰራ በመፈለጋቸው ስራዬን ቀጠልኩ።
አዲስ ዘመን፡- ወደ ኢትዮጵያ ከመመለስዎ በፊት ምን ምን ስራዎችን ያከናውኑ ነበር?
ማስተር ሄኖክ፡– በእንግሊዝ ከድርጅቱ ጋር በዋነኝነት እሰራ የነበረው “ካውንስሊንግ” ሲሆን፤ በተለይ በአደንዛዥ እጽ ሱስ የተጠቁ ወጣቶች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ናቸው። በአውሮፓ በአደንዛዥ እጽ ሱስ ተጠቂ የሆኑ ወንዶችም፣ ሴቶችም ወጣቶች በብዛት አሉ። ምንም እንኳን ገንዘቡ፣ እውቀቱ፣ ሃብቱ ቢኖራቸውም በጭንቀት ይሰቃያሉ። ይሕ ደግሞ በተለይ ወጣቶቹ የአደንዛዥ እጽ ተጠቂ እንዲሆኑ በር ከፍቷል። በሱስ የተጠቁ ወጣቶች ከገቡበት የሱስ ማቅ ለማውጣት የሚሰራ እንደመሆኑ፤ ወጣቶችን በስልጠና፣ በትምህርት ያግዛል፣ ሌሎች ድጋፎችንም ያደርጋል። የወጣትነት እድሜ የሰው ልጅ የነገ ህይወትን የሚወሰንበት አማካኝ እድሜ ነው። ይሕ የእድሜ ክልል ደግሞ ብዙ የሚያስቀሩ እንቅፋቶች አሉ።
በእንግሊዝ እና በሌሎች የአውሮፓ ሃገራት በመዘዋወር በርካታ ለአዕምሮ ምግብ የሚሆኑ ስራዎችን የሰራሁ ሲሆን፤ ቀጣዩ ማረፊያዬ የነበረው ደቡብ አፍሪካ ነበር። እ.ኤ.አ. በ2008 ወደ ደቡብ አፍሪካ ከተዛወርኩ በኋላ በተለይ በወጣቱ ላይ በርካታ ስራዎችን ሰርቻለሁ። በሌሎቹ ሃገራት ከነበረኝ የስራ ቆይታ በተለየ በደቡብ አፍሪካ በጣም ልብ የሚነካ ገጠመኞች ነበሩኝ። ደቡብ አፍሪካ ዝርፊያና ግድያ ከሚበዛባቸው ሃገራት መካከል ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ሃገር መሆኗ ይታወቃል። በዚህች ሃገር ዝርፊያውም ሆነ የግድያው ሰለባ ከሆኑት መካከል ደግሞ ኢትዮጵያዊያን ናቸው። በደቡብ አፍሪካ በቀን ሦስትና አራት ኢትዮጵያዊያን ይገደላሉ። ይሕ አይነቱ ሁኔታ ልቤን የሚነካኝ ነበር። በዚህ ደረጃ ተጋላጭ የሆኑበትን ምክንያት ዳሰሳ አድርገን ነበር። በአብዛኛዎቹ የሚሰሯቸው ስራዎች አንሶላ፣ መጋረጃ፣ ብርድ ልብስ በማዞር ነበር ህይወታቸውን ለመለወጥ የሚሰሩት። ይሕ ደግሞ ለአደጋ እንዲጋለጡ በር ከፍቷል።
ስለዚህ የስራ ሁኔታቸው ላይ ማሻሻያ እንዲያደርጉ በተለያዩ መንገድ እገዛ ማድረግ ጀመርን። በማዞር ከሚሰራው ስራ ይልቅ ወደ ሱቅ ቀይረው እንዲሰሩ በማስተማር፣ በተለያየ መልኩ እገዛ እንዲያገኙ የማድረግ ሥራዎችን ሰርተናል። በስልጠና፣ በትምህርት ብቻም ሳይሆን በፋይናንስ እና በማቴሪያል ጭምር በመደገፍ የአደጋውን ቁጥር ለመቀነስ ጥረት አድርገናል። በሚያስገርም መልኩ ጥረታችን የሰመረ ሲሆን፤ በደቡብ አፍሪካ የነበረው የኢትዮጵያዊያን ግድያ በጣም ቀንሷል። በቅርቡ ተነስቶ የነበረውን ረብሻ በቅርብ እከታተል የነበረ ሲሆን፤ ኢትዮጵያዊያን ብዙም አልተጎዱም። ምክንያቱም ከምታስተምረው፣ ተስፋ ከምታስጨብጠው ነገር ሰዎች ትምህርት ወስደው ከፊታቸው ካለው ሞት፣ ኪሳራ፣ ካለው ችግር ወደ መልካም እንዲሄዱ ያግዛል። ይሕ ደግሞ የአዕምሮ ዝግጁነት የሰጣቸው ሲሆን ተጋላጭነታቸውን ቀንሶታል በደቡብ አፍሪካ በነበረኝ ቆይታ ከሰራኋቸው ስራዎች መካከል ይሕ በእጅጉ ያስደስተኛል።
ሌላው ከአኗኗር ጋር የሚያጋጥሙ ችግሮችን ለመቅረፍ የተሰሩ ስራዎች ነበሩ። እኛ ኢትዮጵያዊያን አኗኗራችን ብዙውን ጊዜ ከድህነት ነው ወደ ሃብት የምንመጣው። ብዙ ኢትዮጵያዊያን ወጣቶች የተለያዩ ስራዎችን ሰርተው ትልቅ ገንዘብ ያገኛሉ። ብዙዎቹ በውጣ ውረድ ውስጥ ገንዘብ ያገኛሉ። ከምንም ተነስተው መኪና ሲኖራቸው፣ በሚሊዮን ራንድ ሲቆጥር አያያዙን ካላወቀበት ይዞት ይጠፋል። ስለዚህ ገንዘብን መሰብሰብ ብቻም ሳይሆን፤ የሚያገኙትን ገንዘብ ምን ላይ ማዋል እንዳለባቸው በማስተማር፣ ስልጠናዎችን በመስጠት ብዙዎችን መለወጥ ችለናል። በዋነኝነት የምናሰለጥናቸው በህይወታቸው ላይ ተስፋ እንዲኖር ሲሆን፤ በተስፋ ውስጥ ደግሞ አብሮትና ጽናት አለ።
ጽናት ማለት ደግሞ እንደ ፍሬን ነው። መኪና መንገድ ስቶ ወደ ገደል እንዳይገባ፣ አደጋ እንዳይደርስ …. ፍሬን ያስፈልጋል። በህይወት ገንዘብ ስታገኝ አያያዙንም ካልቻልክበት የበለጠ የምትጠፋው የዛኔ ነው። ስለዚህ ያለፈውን የችግር፣ የድህነት፣ የጉስቁልና ዘመንን ለማለፍ ብዙ ዋጋ ብትከፍልም፤ ምንም ውጤታማ ሳትሆን ለሌላውም ሳትተርፍ ትጠፋለህ። በመሆኑም የብዙዎችን አኗኗር፣ ገንዘብ አያያዝ እንዲሁም በጋብቻ ዙሪያ ብዙዎችን አስተምሬያለሁ። ኢትዮጵያዊያንን ጨምሮ የተለያዩ ሀገራት ወጣቶች የሚኖሩለትን ምክንያት ኖሯቸው በተስፋ ሰርተው ወደ ውጤት እንዲደርሱ ማድረግ በመቻሌ በስራዬ ሁሌም እንድኮራ አድርጎኛል፡፡
እ.ኤ.አ በ2013 ከደቡብ አፍሪካ ወደ አሜሪካ ሎሳንጀለስ የመዘዋወሩ አጋጣሚ ተፈጠረ። በአሜሪካ በነበረኝ የስራ ቆይታ ትልቁ ትኩረት አድርገን ስንሰራ የነበረው ቤት አልባ /ሆምለስ/የሚባሉት ላይ ነበር። በተለያዩ ምክንያት ቤት አልባ ሆነው ጎዳና የወደቁ ሰዎችን መሰረት ያደረገ የበጎ አድራጎት ስራ ነበር። አሜሪካ ሃገር ከሰራህና ከተማርክ ትልቅ ስኬት የምታገኝበት፤ ከራስህ አልፈህ ለሌሎች አለኝታ የምትሆንበት አገር ነው። እንዲህ እንዳትሆን ደግሞ በየስርቻው የሚያስቀሩ ችግሮች አሉ። አብዛኛው ወጣት ከህይወት ጎዳና እንዲወጣ እና በየስርቻው ከሚያስቀሩት ምክንያቶች መካከል አደንዛዥ እጽና በተለያዩ ሱሶች ከመጠመድ ጋር የሚያያዝ ነው።
እነዚህን ወጣቶች ካለባቸው ችግር ለማላቀቅ እንደ አንድ ባለሙያ ጥረት ሳደርግ ነበር። በዚህ አይነቱ ችግር ውስጥ ደግሞ አሜሪካኖች ብቻም ሳይሆን በርካታ ኢትዮጵያዊያን፣ ኤርትራዊያን፣ ፊሊፒንስ እና የተለያዩ ሀገራት ዜጎች ናቸው። የድርጅታችን ተግባር ምንድነው፤ በእንዲህ አይነት የህይወት መስመር የሚገኙትን ሰዎች በመቅረብ ከችግራቸው እንዲወጡ በማድረግ ወደ ህይወት ጎዳና ለመመለስ ጥረት ያደርጋል። የሰዎቹን የችግር ሁኔታ መሰረት በማድረግ፤ ለምሳሌ ቤት ለሌላቸው ከአሜሪካ መንግሥት ቤት እንዲያገኙ በማድረግ፣ በተለያዩ ሱስ ውስጥ የሚገኙትን ወደ ማገገሚያ እንዲገቡ በማድረግ ከገቡበት ተስፋ የቆረጠ መንገድ ወደ ተስፋ እንዲመለሱ የማድረግ ስራን ነበር የምንሰራው። ይሕን ደግሞ የምናደርገው የተለያዩ ስልጠናዎችን፣ ትምህርቶችን በመስጠት ሲሆን፤ በዚህም ብዙዎችን ወደ ህይወት መስመር መመለስ ችለናል።
አዲስ ዘመን፡- ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሱ በኋላ ምን ስራዎችን ለመስራት አሰቡ? ምንስ ሰሩ?
ማስተር ሄኖክ፡– ወደ ሀገሬ ገብቼ መስራት ከመሰረቱም የነበረኝ ህልም ነው። ኢትዮጵያ ገብቼ ከሠላሳ ዓመት በላይ በተለያዩ አለማት ተዘዋውሬ የቀሰምኩትን የስራ ልምድ፣ እውቀት፣ የስራ ባህልን በመቀመር ሃገሬን መጥቀም፣ ማገልገል፣ ለሀገሬ ወጣት ደጀን መሆን ሁልጊዜ እመኘው የነበረ ነው። የሁሉም ነገር ወሳኙም፣ ፈራጁም ጊዜም አይደል? ስለዚህ ጊዜ ፈቀደና ባሳለፍነው ዓመት ወደ ሀገሬ ገባሁ። የዓመታት ህልሜን ለመኖር የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽም ወደ ተግባር ከተሸጋገርኩ ሰንበት ብያለሁ። በኢትዮጵያ ላቭ ቱ ኔሽን /ፍቅር ለህዝብ/ ግብረ ሰናይ ድርጅት በመመስረት እንቅስቃሴ ማድረግ ጀምሬያለሁ። ድርጅቱ ዓለም ዓቀፍ በጎ አድራጎት ድርጅት ሲሆን በአሜሪካ፣ ደቡብ አፍሪካ ላይ ቢሮ ከፍቶ ለበርካታ ዓመታት በወጣቶች፣ በቱሪዝም እንዲሁም በቡና ላይ ሲሰራ ቆይቷል።
በቅርቡ ደግሞ በኢትዮጵያ ተቋቁሞ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ ወደ ተግባር ገብተናል። የኢትዮጵያ ቡና ለዓለም በስፋት መድረስ እንዲችል የማስተዋወቅ ስራ የመጀመሪያው ነው። ሀገራችን የቡና መገኛ ብትሆንም ኤክስፖርት በማድረጉ ረገድ ብዙ ሀገራት ይበልጡናል። ለዓለም ህዝብ በማስተዋወቅ ረገድ ብዙ አለመስራታችን እንዲሁም፤ ለጥራቱ ዋጋ በመስጠት ካለመራመዳችን ይመነጫል። የኢትዮጵያን ቡና ለዓለም ህዝብ በጥራት እንዲቀርብ ማስቀመስ አለብኝ በሚል ከአሜሪካ፣ ከፈረንሳይ እስፔሻል ኮፊ አሶሴሽን ጋር በመሆን በአዲስ አበባ የቡና ቅምሻ ዝግጅት አደረግን።ዝግጅቱ መደረጉ ደግሞ የቡናችን ጥራት የዓለም ህዝብ እንዲያውቀውና የሀገሪቱ የኤክስፖርት አቅም ከፍ እንዲል ትልቅ ሚና ነበረው። በዘንድሮ ዓመት ቡና እና ሻይ ባለስልጣን እንዳስታወቀው “የኢትዮጵያ ቡና በከፍተኛ ደረጃ የተሸጠ መሆኑን ነው።” ይሕ ጥሩ ጅማሮ ቢሆንም፤ የኢትዮጵያ ቡና በዓለም ዓቀፍ ደረጃ አንደኛ ላይ ለማስቀመጥ አቅደን እየሰራን እንገኛለን። በመንግሥት በኩል ያገኘነው ምላሽ እጅጉን የሚያበረታታ መሆኑ እንደሚሳካ አምናለሁ።
ሌላው ደግሞ ከቱሪዝም ጋር የሚያያዝ ሲሆን፤ የተጀመሩ ስራዎች አሉ። በስፖርት ቱሪዝም ሃገራችንን ማስተዋወቅ ላይ መሰረት ያደረጉ ናቸው። ፕሮጀክቱ ከአፍሪካና ከብራዚል የተውጣጡ ምርጥና ኮከብ ተጫዋቾች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው “ሰላምና ቱሪዝም” በሚል መሪ እንዲጫወቱ ማድረግ ነው። ፕሮጀክቱ የላቭ ቱ ኔሽን ተባባሪ መስራች፣ የቀድሞ የፈረንሳይ እና የቼልሲ እግር ኳስ ተጫዋች ፓብሊክ ፓንክረስት ጋር በመነጋገር ህዳር 16 ቀን 2014 ዓ.ም ኢትዮጵያ በመምጣት እንደሚጫወቱ ከስምምነት መድረስ ተችሏል። ከሚመጡት ተጫዋቾች መካከል ደግሞ ብራዚል ካካ፣ ዱን፣ ሮናልዶ እና ሌሎች ከአፍሪካ ሳሙኤል ኢቶ እና ድሮግባ ሌሎችን ጨምሮ 42 የብራዚልና የአፍሪካ ኮከብ ተጫዋቾች ናቸው። ይሕ ደግሞ ለኢትዮጵያ ቱሪዝም ትልቅ መነቃቃት የሚፈጥር ከመሆኑ ባሻገር ወጣቱ በስፖርቱ የተሻለ መነቃቃት እንዲኖረው ያደርጋል። ድርጅታችን ከቱሪዝም አንጻር የያዘው ፕሮጀክት ይህ ሲሆን፤ በወጣቶች የስራ እድል ፈጠራ አኳያ ሌላው በሂደት ላይ የሚገኘው ፕሮጀክት ነው።
ቀደም ሲል እንደጠቀስኩት ሃገሬን ከፍ ማድረግን ሳስብ በተለይ ወጣቱ ያማከለ ስራ መስራት እንዳለብኝ አምናለሁ። ወጣቱን በስልጠና፣ በፋይናንስ፣ በቁሳቁስ፣ በትምህርት በመደገፍ የኢኮኖሚ አቅሙን እንዲያጠነክር ማድረግ ያስፈልጋል።
ወጣቱን ዝም ብለህ ገንዘብ ከሰጠኸው ውጤት አይኖረውም። ለወጣቱ ገንዘብ ሳይሆን ሙያዊ ስልጠና መስጠትና በሚሰማራበት የስራ ዘርፍ የሚያስፈልገውን ግብአት በማሟላት የሚሰራበትን ማዕቀፍ መፍጠር ቢቻል ውጤት እንደሚያመጣ አመንን። ሆፕ ፈንድ ማይክሮ ፋይናንስ የተሰኘ ብድርና ቁጠባ አገልግሎት ሰጪ የፋይናንስ ድርጅት ተቋቁሞ ስራ እንዲጀምር ተደርጓል። የዚህ ፕሮጀክት አገልግሎት የሚሆነው፤ ላቭ ቱ ኔሽን ወጣቱን ያሰለጥናል፣ ከተቋሙ ፈንድ ያፈላልጋል፣ ሆፕ ማሽኖችን በብድር መልክ ይሰጣል። ለምሳሌ ወርቅ የሚያወጡ ወጣቶች የሚያወጡት በባህላዊ መንገድ ነው።
ዘመናዊ የወርቅ ማውጫ ማሽን በብድር ገዝቶ በመስጠት አሠራራቸውን በማዘመን በቀላሉ ወርቅ ማውጣት ይችላሉ ማለት ነው። ስለዚህ በቡና፣ በወርቅ ማውጣት ሥራ ላይ የተሰማሩ ወጣቶችን በቴክኖሎጂ እንዲታገዙ በማድረግ ጠንካራ የኢኮኖሚው አቅም ለመፍጠር በማሰብ ነው። ይሕ ወጣቱን በተለያዩ የሙያ መስኮች አሰልጥኖ እና አስፈላጊውን ማሽን በብድር በማቅረብ በኢኮኖሚው ላይ የራሱን አበርክቶ ያደርጋል። በአዲስ አበባ፣ በክልሎች በስፋት ለመስራት እቅድ ይዞ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። ይህም ለሀገር፣ ለመንግሥት ትልቅ ጠቀሜታ ይሰጣል።
አዲስ ዘመን፡- ለሰጡን ማብራሪያ በጣም እናመሠግናለን፡፡
ማስተር ሄኖክ፡- እኔም አመሠግናለው
ዳንኤል ዘነበ
አዲስ ዘመን ነሃሴ 21/2013