የሀገር ካስማነታቸውን ለማሳየት፤ ለሀገር ጉዳይ እኔም አለሁ ያሉ፤ ውሳኔያቸውን ያመኑ፤ የታያቸውን እውነት በአደባባይ ተናግረው ሊወስኑ ያሰቡ፤ በሀገር ጉዳይ እንሰማ ያሉ ከመላ አገሪቱ የተወጣጡ ሴት ምሁራን፣ ነጋዴ ሴቶች፣ በተለያዩ አደረጃጀቶች ውስጥ ያሉ በአጠቃላይ ከ500 በላይ ሴቶች እንዲሁም ሴት ከፍተኛ የመንግስት አመራሮች በወቅታዊ አገራዊ ጉዳይ ለመወያየት በአዲስ አበባ የኦሮሞ ባህል ማእከል ተገኝተው ነበር:: ሀገሪቱ አሁን ያለችበት ሁኔታ ላይ በተወያዩበት ወቅት በሀገራዊ ጉዳይ ከኢትዮጵያ ሴቶች ምን ይጠበቃል? የሚል ጥያቄ ላይ ትኩረት ተሰጥቶት ነበር።
ለውይይት መነሻ ይሆን ዘንድ በብልፅግና ሴቶች ሊግ ፅህፈት ቤት ሀላፊ ወይዘሮ መስከረም አበበ ፅሁፍ አቅርበው ነበር። በፅሁፉም ሴቶች ከማንኛውም ጊዜ በላይ አንድነታቸውን ማስጠበቅ እንዳለባቸው ተጠቅሷል:: አሁን የሚታዩትን ውስጣዊና ውጫዊ ተግዳሮቶች በድል ለመሻገር እንደ ሀገር በጋራ መቆምና መደራጀት ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር ይሆናል:: ዛሬ ከግራና ከቀኝ የተቃጣውን አደጋ ለመቀልበስ፣ ተቀልብሶም ወደ ታለመበት ከፍታ ለመውጣት እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ፣ እንደ አንድ ልብ መካሪ በመሆን መቆም የሚቻልበት ወቅት ነው:: ይህንን አስቸጋሪ ወቅት በጋራ በመተባበር በድል በመወጣት ኢትዮጵያ ሁሌም የጀግኖች እና ሀገር ወዳድ አርበኞች አገር መሆኗን ዳግም ማስመስከር እንደሚጠበቅ ኃላፊዋ በፅሁፋቸው አብራርተዋል::
‹‹እኛ ኢትዮጵያዊያን ምንም አይነት የብሄር፣ የሃይማኖት፣ የፖለቲካ አመለካከትም ሆነ ሌላ ልዩነት ቢኖረን በአገራችን ህልውናና ሉዓላዊነት ጉዳዮች ላይ ሁላችንም አንድ በመሆን አገራችንን ወደ ጦርንት በመማገድ፣ ኢኮኖሚዋን በማዳከምና በብሄርና በሃይማኖት ዜጎቿን በማጋጨት ደካማ አገር እንድትሆን የሚደረጉ ሴራዎችን በተባበረ ክንድ መመከት ማውገዝ ይጠበቅብናል::›› ያሉት ወይዘሮ መስከረም፤ በአሸባሪው የህወሓት ሀይልና የኢትዮጵያን ማደግ መለወጥ በማይሹ የሀገራችን የዘመናት ጠላቶች በጋራ ትብብር ኢትዮጵያን ለማንበርከክ እየተደረገ ያለዉን ዙሪያ መለስ እንቅስቃሴ የኢትዮጵያ ሴቶች በተገቢው መረዳት እና ይሄን የሚቀለብስ ሁሉ አቀፍ ተግባር ውስጥ መግባት ይኖርባቸዋል:: በሀገሪቱ ጉዳይ ጣልቃ እየገቡ ህወሓትን ለመደገፍ የሚሞክሩ የምዕራባውያን ሀገራትም በአገሪቱ ሉዓላዊነት የማይደራደር ህዝብ እንዳለ በተግባር ሊነገራቸው፣ አንድ ሆኖ ድምፅ በማሰማትና በተባበረ ክንድ ሊወገዝ እንደሚገባም አመልክተዋል::
የተፈጥሮ ሀብቶችን በማልማት ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮችን መፍታት ህጋዊ ብቻ ሳይሆን ተፈጥሯዊ መብት ጭምር መሆኑን አለም እንዲገነዘብ ያስፈልጋል:: አገሪቱ በተለያዩ አቅጣጫዎች የዲፕሎማሲ ጫና ውስጥ በማስገባት የተፈጥሮ ሃብቶቿን ለልማቷ እንዳትጠቀምም ሆነ የራሷን ችግሮች በራሷ እንዳትፈታ የሚደረገው ያልተገባ እንቅስቃሴ በመቃወም ኢትዮጵያዊነትን ይበልጥ በማጠናከር ከታለመው የልማት ግብ ለመድረስ ርብርብ ሊደረግ እንደሚገባ ወይዘሮ መስከረም አስረድተዋል::
አሸባሪዉ ቡድን በሚለቃቸዉ የሀሰት ፕሮፖጋንዳ ባለመሸወድ የመረጃ ምንጭ መንግስት እንዲሆን በማድረግ በሚያስፈልገው ሁሉ ከመንግስት ጎን መሰለፍ ይገባል:: ወቅቱ የአገሪቱ ሁኔታ እጅግ በከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ ማየት የሚገባ ጊዜ መሆኑንም ጠቅሰዋል:: በአገሪቱ ባንዳዎችም ሆኑ የውጭ መገናኛ ብዙሀን፣ መንግስታት፣ አሸባሪ ቡድኖች እንዲሁም በእርዳታ ስም ሆነ በሌላ ስም የተደራጁ ድርጅቶች ሙሉ በሙሉ ትኩረታቸውን በአገሪቱ ጉዳይ አድርገው የሃሰት መረጃ የተቀላቀለበት ዜናዎች በማሰራጨት ላይ ይገኛሉ:: እነዚህ መረጃዎች በተቀናጀ መልኩ ሽብርተኛው ህውሓት፣ ሱዳንና ግብፅ፣ አሜሪካና የምዕራባውያን መንግስታትና መገናኛ ብዙሀኖቻቸው እንዲሁም እርዳታ ድርጅቶች ኢትዮጵያን ለማፍረስ እና የመንግስትን እጅ ጠምዝዘው ሽብርተኛውን ቡድን ለመሾም ያላቸውን አቅም ሁሉ እየተጠቀሙ መሆናቸውን ወይዘሮ መስከረም በፅሁፋቸው ጠቁመዋል::
እነዚህን መረጃዎች በአግባቡ በመከታተል ትክክለኛ መረጃና አገሪቱ የምትገኝበትን ሁኔታ ለአለም በማሳወቅ ረገድ ሴቶች የበኩላቸውን ሊወጡ እንደሚገባ በፅሁፉ ተጠቁሟል:: መንግስት አለም እንዲያውቀው የሚለቃቸው መረጃዎችን ሴቶች በሚገባ እየተከታተሉ እና የጠላትን የውሸት ፕሮፓጋንዳ ለአለም ለማሳወቅ በሚደረገው ጥረት የራሳቸውን አስተዋፅኦ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል:: በዚህም በማህበራዊ ሚዲያ በፌስ ቡክ፣ በቲውተር፣ በሀገር ውስጥ እና በውጭ መገናኛ ብዙሀን በስፋት በመሳተፍ የሀሰት ፕሮፓጋንዳ በማዉገዝ ትክክለኛ ጉዳዮችን ለዓለም ማሰረዳት እንደሚገባ ወይዘሮ መስከረም አብራርተዋል::
ወይዘሮ መስከረም፤ ‹‹በየአካባቢዉ ሰላምን የሚያወኩ ጸጉረ ልዉጦችን መጠበቅ እና መከታተል ይገባናል:: አሸባረው የህወሓት ቡድን ‹ኢትዮጵያን ለማፍረስ ሲዖል ገብተን መመለስ ካለብንም እንመለሳለን› ብሎ በይፋ ካወጀ በኋላ ሃገራችንን ለማተራመስ የማይሞክረው ነገር የለም:: ሰለሆነም አከባቢያችንን ከተለያዩ የህወሓት አባላትና ደጋፊዎች መጠበቅ ይገባል:: እነዚህ አካላት ይህንን በህግ አሸባሪ ተብሎ የተፈረጀ ቡድንን በሃሳብ ከመደገፍ አልፈው በፋይናንሱም እንዲሁም ቦታዎችን በመጠቆም ለጠላት እንደ መንገድ የሚረዳ እና አስተኳሽ ሆነው ወገኖቻችን እያስመቱ ያሉ ስላሉ በከፍተኛ ትኩረት ማየት ያሰፈልጋል::
በተጨማሪም አሸባሪው ቡድን የራሳቸውን ህፃናትን ሳይቀር ለስለላ ስራ በየከተሞች በማስገባት ላይ ይገኛል:: ለዚህም የአዕምሮ በሽተኛ መስለው፣ የእምነት አባት መስለው በተለያየ መንገድ የሽብር ስራቸውን እያከናወኑ ስለሆነ አካባቢውን በመቃኘት መረጃ መቀባበልና በአንድ መቆም ይገባል::›› ብለዋል::
ሁሉም በተሰማራበት መስክ ዉጤታማ መሆን ይጠበቅበታል:: የሀገሪቱ የግብርና እና ሌሎችም ምርቶች ማደግ ይኖርባቸዋል፣ የንግድ እና ኢንቨስትመንት ስራዉ እየተቀላጠፈ የስራ አጥነት ችግር እየተቃለለ ሊሄድ ያስፈልጋል:: የታላቁ የህዳሴ ግድብን ጨምሮ በሀገሪቱ ያሉ ሁሉም የልማት ስራዎች በጥራትና በፍጥነት ተጠናቀዉ ብልጽግናው የሚሳለጥበት ሁኔታ ሊፈጠር ይገባል:: የትምህርት ስራዉ በተገቢ መከወን አለበት፤ በመሆኑም ሴቶች በየተሰማሩበት መስክ ከመንግስት አካላት ጋር በመቀናጀት ዉጤታማ ለመሆን መስራት ይገባቸዋል::
ይህ ሲሆን የዉጭ ሀገራት ሊያሳድሩ የሚፈልጉትን ተፅዕኖና ማዕቀብ ቢጥሉ እንኳን በራስ አቅም መቋቋም የሚቻልበት ሁኔታ ይፈጠራል:: በግንባር ደረጃ የተጀመረው ህግ የማስከበር ጦርነት በድል አድራጊነት መወጣት ይቻላል:: በመሆኑም በዚህ ወሳኝ እና ታሪካዊ ወቅት የሀገሪቱ ሴቶች በየተሰማሩበት መሰክ ቀንና ሌሊት ዉጤታማ መሆን እንደሚችሉ ወይዘሮ መስከረም ጠቅሰዋል::
ህግ ለማሰከበር ለተሰማራው ሀይል እና ለተፈናቀሉ ወገኖች የሚደረገዉን ድጋፍ አጠናክሮ ማሰቀጠል ሴቶች በግንባር ከመፋለም ጀምሮ ለመከላከያው ደጀን በመሆን ሰንቅ በማዘጋጀት ሁሉን አቀፍ ተጋድሎ እያደረጉ ይገኛሉ:: አሁንም ጦርነቱን በድል እስኪጠናቀቅ ድረስ መከላከያውን በማጀገን በየተሰማራበት የውግያ ቦታ ተገኝቶ በማበረታታት፣ በሎጅስቲክ በማገዝ፣ ደም በመለገስ፣ ወደ ግንባር ለሄዱ የቁርጥ ቀን ልጆች ቤተሰቦች የማገዝ፣ የማበረታተትና ደጀንነትን ማረጋገጥ ይገባል::
ሌላው በጦርነቱ ምክንያት በርካታ ዜጎች በክረምቱ ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለው ጎዳና ላይ ሰለሚገኙ እና ከተፈናቃዮች ውስጥም ሴቶች ነፍሰጡር እናቶች እና ህፃናት በስፋት በችግር ውስጥ ያሉ በመሆኑ ሀብት በማሰባሰብ የመደገፍ ስራ እንደሚሰራ ጠቁመዋል።
በግንባር በመሰለፍ ጉዳት የደረሰባቸውን አካላት መጠየቅ እና ማበረታት ያሰፈልጋል። በአጠቃላይ ሴቶች በተደራጀ መንገድ ሁሉን አቀፍ አስተዋፅኦ በማበርከት ኢትዮጵያ ወደ ሰላሟ፣ ልማቷ እና ወደ ጀመረችው የብልፅግና ጉዞ እድትቀጥል ጥሪ ያቀረቡት ወይዘሮ መሰከረም፣ ተሰብሳቢዎቹ ሀገሪቱ የገባችበትን ጦርነት በድል እንድታልፍ ሴቶች አንድ ላይ በመሆን አቅም ያለው ግንባር ድረስ ሄዶ በመዝመት፤ እናቶች ለሀገራቸው ህልውና ሲባል ልጆቻቸውን መርቀው በመሸኘት፤ የተቀሩትም ደጀን በመሆን ስንቅና ትጥቅን በማዘጋጀት በተባበረ ክንድ ሀላፊነታቸውን እንደሚወጡ ቃል ገብተዋል።
ውይይቱ ላይ የተሳተፉት ሴቶች በሀገሪቱ ላይ የተጋረጠው ጦርነት ከአሸባሪው ከህወሓት ቡድን ጋር ብቻ ሳይሆን ከሌሎች የውጭ ሀይሎችም ጋር በመሆኑ ይሄንን ሀገር የማፍረስ አላማ ይዞ የተነሳውን ጦርነት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመቋጨት ሴቶች ሀላፊነታቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል።
ሀገሪቱን ለማፍረስ የተነሳው ይህ ሽብርተኛ ቡድን የትግራይ እናቶችን ልጆቻቸውን ከጉያቸው እየነጠቀ ለጦርነት ከመማገዱም በሻገር በአፋርና በአማራ በንፁሃን ዜጎች ላይ እየተደረገ ያለው ጭፍጨፋ ይቅር የማይባል መሆኑን የተናገሩት በመድረኩ የነበሩ ሴቶች፤ ይህን በትግራይ እናቶች ጉያ ተሸሽጎ ከባድ ጥፋት የሚሰራውን ሽብርተኛ ቡድን የትግራይ እናቶች አሳልፈው ሊሰጡት አንደሚገባ ጥሪ አቅርበዋል:: ተሰብሳቢዎቹ የትግራይ ሴቶች ይህ እልቂት እንዲያበቃ በመስራት የለውጥ አካል እንዲሆኑ ጠይቀዋል።
በትግራይ ክልል የሚኖሩ ሴቶች ሽብርተኛው ቡድን በሚያሰራጨው የተሳሳተ ፕሮፓጋንዳ በመታለል ለጥቂት ሰዎች ፍላጎትና አለማ ማሳኪያ እየሆኑ መሆናቸውን በመገንዘብ ከመላው ሀገሪቱ ሴቶች ጎን በመሆነ ለሰላም ዘብ እንዲቆሙና ልጆቻቸውን ከእልቂት መጠበቅ ሀላፊነት እንዳለባቸው ከተሰብሳቢው ሀሳብ ተሰጥቷል::
ከዚህም በተጨማሪ በጦርነቱ የተነሳ በክረምት ከሞቀ ቤታቸው ለተፈናቀሉ ወገኖች፤ ሴቶች እንደ ሀገር አንድ በመሆን ለእነዚህ ሰዎች መድረስ የሚገባቸው መሆኑን የጠቆሙት ተወያዩቹ፤ በሀገሪቱ የሚያጠቡ፤ አቅመ ደካሞችና ህፃናት ሴቶች እየደረሳባቸው ያለውን እንግልት በተባበረ ክንድ ማለፍ የሚገባ መሆኑን አስረድተዋል:: ሽብርተኛው የህወሓት ቡድን በስልጣን ላይ በነበረበት ወቅት በሰራው የሴራ ፖለቲካ ህዝቡ እርስ በእርሱ በጥርጣሬ እንዲተያይ እንዲከፋፈል ከማድረጉም ባሻገር ለፖለቲካ የበላይነት የኢኮኖሚ የበላይነት ያስፈልጋል በማለት የሀገሪቱን ሀብትና ንብረት ሲመዘብር መቆየቱን አስታውሰው፤ ከሀገርና ከህዝብ የሰረቀውን ገንዘብ በየስርቻው በመነስነስ የሚፈጠረውን ግጭት በአንድ ላይ በመሆን በእንቢተኝነት መፋለም የሚገባ መሆኑን ጠቁመዋል።
‹‹የውጭ ሀይሎችም እጃቸውን ከሀገሪቱ ላይ ያንሱ›› ያሉት የኢትዮዽያ ሴቶች፤ አቅም የፈቀደውን ሁሉ በተሰማሩበት መስክ በመወጣት ለሀገራቸው ዘብ እንደሚቆሙ ተናግረዋል:: እስካሁን ድረስም በመላው ሀገሪቱ ያሉት ሴቶች ዳር እሰከዳር በነቂሰ በመውጣት የስንቅ ዝግጅት ያደረጉ ሲሆን በሴቶች ሊግ ብቻ በ50 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት ስንቅ መዘጋጀቱን፤ በሴቶች በተደረገ የደም ልገሳ መርሀ ግብር 12ሺ ዩኒት ደም ወደ ደም ባንክ መግባቱን ጠቁመዋል።
በውይይቱ ላይ የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ዶክተር ሊያ ታደሰ፤ የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ሄርጎጌ ተስፋዬና ሌሎች የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች የተገኙ ሲሆን በውይይቱ መጨረሻ ባለ ስድስት ነጥብ የአቋም መግለጫ በማውጣት ተጠናቋል።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ነሃሴ 16/2013