በብዛት ወጣት ከሚገኝባቸው አገራት መካከል አንዷ ኢትዮጵያ ናት:: በኢትዮጵያ ታድያ ወጣቱ ክፍል ከመስራትና አገርን ከማሳደግ ይልቅ ባልባሌ ትርክቶች ተጠምዶ እርስበርስ ሲጋጭ ማስተዋል ከተጀመረ ዋል አደር ብሏል:: በአገሪቱ የሚሰራ ስራ ጠፍቶ ሳይሆን አለመስማማቶች በመበራከታቸው የሚሰሩ እጆች ለጥፋት እየዋሉ ይገኛሉ:: በመንግስትም ደረጃ ጠንከር ያሉ ስራዎች ባለመከናወናቸው ዝርፍያና ቅምያ በከተሞች አካባቢ እየተስፋፋ ይገኛል:: ይህን ጉዳይ ያለ ምክንያት አይደለም ያነሳሁት:: ለጥፋት የሚውሉ እጆች እንዳሉ ሁሉ ለበጎ ተግባራት የሚሰነዘሩ እንዳሉ ለማሳየት ፈልጌ ነው:: የተቸገሩ አረጋውያንንና የጎዳና ተዳዳሪዎችን የሚደግፉና አለንላችሁ የሚሉ በርካታ በወጣቶች የተመሰረቱ ማህበራት እንዳሉ በዚሁ አምዳችን አስቃኝተናችሁ ነበር:: አብዛኛዎቹ ማህበራት እውቅናና ፈቃድ አግኝተው እርዳታ በማሰባሰብ ድጋፍ የሚያደርጉ ናቸው::
በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ወጣቱ ማህበረሰባዊ ተሳትፎ እያደረገ ሲሆን አቅመ ደካማዎችን በማገዝ ረገድ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ነው:: የመረዳዳትና የመደጋገፍ ባህል በሁሉም ቦታዎች እየተቀጣጠለ ሲሆን በተለይ በተለያዩ ምክንያቶች የተፈናቀሉ ወገኖችን በመርዳት ወጣቱ ግንባር ቀደም ነው:: መንግስትም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የተቸገሩ በማብላትና ቤታቸውን በመጠገን ውጤታማ ስራ እያከናወነ ነው:: ይህም እንቅስቃሴ በበዓላት ወቅት ብቻ ሳይሆን በሌሎችም ወቅቶች ሊሰራ የሚገባው ጉዳይ ነው:: የሲቪክ ማህበራት አዋጅ ከተሻሻለ በኋላ በሁሉም ቦታዎች በጎ አድራጎት ማህበራት እየተበራከቱ ይገኛል:: በተለይ የህብረተሰቡን ችግር ከስሩ ለመፍታት ውጤታማ ስራ እያከናወኑ ይገኛሉ::
አረጋውያን አመቺ የሆነ የማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ምቹ ሁኔታ ከተፈጠረላቸው በልዩ ልዩ የእውቀት ዘርፍ ያካበቱትን ልምድና ተሞክሮ ተተኪ ለሆነው ለአዲሱ ትውልድ ታሪኩን፣ ባህሉን፣ ወጉን እና አጠቃላይ ማንነቱን ጠብቆ እንዲያስቀጥል በማስቻል በራሱ የሚተማመን ትውልድ በማፍራት አገሪቱን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ማሸጋገራቸው አያጠያይቅም:: ከዚህ በተጨማሪ አረጋውያን በህይወት ዘመናቸው ባጋጠማቸው ውጣ ውረድ ያካበቱትን ዕውቀትና ልምድ በመጠቀም ማህበረሰቡ ለሚገጥመው ችግሮች መፍትሄ በማፈላለግ፣ የሚነሱ ግጭቶችን በመዳኘትና በማስማማት፣ በአጠቃላይ የአካባቢን ሰላምና ደህንነት በማስጠበቅ ረገድ ጉልህ ሚና አላቸው::
በጎ ስራ ማከናወን ጥቅሙ ለራስ ነው ይባላል:: ምክንያቱም ማንኛውም ሰው የዛሬን እንጂ ነገ የት እንደሚወድቅ አያውቅም:: በዚህም ዛሬ ላይ ባለው ጉልበትና ገንዘብ ሌሎችን መደገፍና የመደጋገፍ ባህልንም ማሳደግ ከቻለ ነገ ለራሱ መውደቂያ ያገኛል ማለት ነው:: በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች አቅመ ደካማዎችንና ህፃናትን የሚደግፉ ማህበራት እየተበራከቱ ይገኛሉ:: ከነዚህ ውስጥ አንዱ በሀረር ቀላድ አምባ የሚገኘው ቀላድ አምባ ፈርጥ ወጣቶች የበጎ አድራጎት ማህበር ነው:: ማህበሩ አቅም ለሌላቸው አረጋውያን ምርኩዝ ከመሆን በዘለለ አስፈላጊ የሚባሉ መሰረታዊ ነገሮችን እያቀረበላቸው ይገኛል:: ከማህበሩ መስራችና ገንዘብ ያዥ ብሩክ ለገሰ ጋር ቆይታ አድርገናል::
የማህበሩ አመሰራረት
ቀላድ አምባ በጎ አድራጎት ማህበር የተመሰረተው ጥር 25 ቀን 2010 ዓ.ም ላይ ነው:: ማህበሩን ለመመስረት ምክንያት የሆነው አንድ አካባቢ የሆኑ ወጣቶች የበጎ ስራ ለማከናወን ይመካከሩ ነበር:: በአንድ ወቅት በተዘጋጀ ሰርግ ላይ ወጣቶች ሰፋ ያለ ውይይት በማካሄድ ማህበር ለመመስረት የሚያስችላቸውን መሰረት ጣሉ:: በተለያዩ ጊዜያትም መስራት ስለሚችሉት ስራ እየተወያዩ ማህበሩን ለመመስረት በቁ:: ማህበሩ ሲመሰረት አስር አባላትን አካቶ ሲሆን በሂደት ብዙ ወጣቶች ተቀላቅለዋል::
ያከናወናቸው ተግባራት
ማህበሩ ሲመሰረት በዋነኝነት አላማ አድርጎ እየተንቀሳቀሰ የሚገኘው አረጋውያንን በመርዳት ላይ ሲሆን አረጋውኑን ማሳከም፣ ቤት ለፈረሰባቸው ቤት በመስራት እንዲሁም ከፍተኛ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ደግሞ ከከተማ አስተዳደሩ ጋር በማገናኘት እንዲረዱ ይደረጋል:: በአሁኑ ወቅት ደግሞ ቤታቸው የፈረሰባቸውን አረጋውያን የመጠገንና የማደስ ስራዎች ናቸው:: በገንዘብም የሚደጎሙበትን ሁኔታ ማህበሩ እያመቻቸ ነው:: የኮሮና ወረርሽኝ በተከሰተበት ወቅት በከተማው በመዞር የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች ሲያከናወኑ ቆይተዋል:: በቀላድ አምባ በግንባር ቀደምትነት ስለ በሽታው ማስተማር የጀመረው ማህበሩ ሲሆን የእጅ ማስታጠብ ስራዎች አከናውኗል::
ማህበሩ በዋናነት ሲመሰረት በጎ አድራጎት ስራና አረጋውያንን ለመንከባከብ እንዲሁም ወላጅ የሌላቸውን ልጆች ለመደገፍ ነው:: በየአካባቢው በበዓላት ወቅት አቅመ ደካማዎችን በመጠየቅና አብሮ በማሳለፍ፣ በየቤታቸው በመሄድ የመንከባከብና ቤታቸውን የማደስ ስራ ይከናወናል:: ድጋፍ ከሚደረግላቸው አስራ አራት አረጋውያን ውስጥ የአምስቱ በአሁን ወቅት በሂወት የሉም:: በየአካባቢው በመሄድ የጎርፍ ማስወገጃ ቦዮችን መስራት፣ ቤት ለቤት በመሄድ አዛውንቶችን መርዳት ማህበሩ በቻለው አቅም እየሰራ ነው::
ድጋፍ ለሚደረግላቸው አዛውንቶች ቤታቸውን ማፅዳት፣ ምግብ ለመስራት የሚያግዙ መሰረታዊ ፍጆታዎችን መስጠት እንዲሁም ሌሎች ስራዎች ይከናወኑላቸዋል:: ማህበሩ ውስጥ የሚገኙ አባላት በቡድን በመከፋፈል በአዛውንቶቹ ቤት በመሄድ ክትትልና እንክብካቤ ይደረጋል:: በአረጋውያኑ ቤት የጎደለ ነገር ካለም የቡድኑ አባላት በመመልከት እንዲሟላ ይደረጋል:: ማህበሩ በደም ልገሳ ስራዎች ላይ በመሳተፍ. የወስጥ ለውስጥ መንገድ ስራ ላይ እንዲሁም በማንኛውም በጎ ስራዎች ላይ ተሳትፎ እየተደረገ ይገኛል:: በቋሚነት ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው አዛውንቶች የአስቤዛ ነገሮችን ማሟላትና ቤታቸው በመሄድ መንከባከብና ልብሳቸውን ማጠብ ስራ ይሰራል:: በማህበራዊ አገልግሎት ቡድን በየጊዜው አረጋውያኑን እንዲጎበኙና ለምግብ የሚያስፈልጋቸውን እቃዎች በየጊዜው ይሰጣቸዋል::
ማህበሩ በገቢ ምንጭነት እየተጠቀመ የሚገኘው የአባላት መዋጮና የትኬት ሽያጭን ነው:: የማህበሩ አባላት በየወሩ የሚጠበቅባቸውን መዋጮ በአግባቡ ይሰጣሉ:: በተጨማሪም ከሚኖሩበት ወረዳ የተበረከተላቸውን የውሃ መያዣ ሮቶ በመጠቀም ለአካባቢው ነዋሪ ውሃ እየሸጡ ይገኛሉ:: ይህም አንዱ የማህበሩ የገንዘብ ማመንጫ ሆኖ እያገለገለ ይገኛል:: የኮሮና ወረርሽኝ በተከሰተበት ወቅት በየአካባቢው እጅ በማስታጠብ፣ የግንዛቤ ስራዎችን በማከናወን እንዲሁም ሌሎች ስራዎች በማህበሩ ተከናውነዋል::
ማህበሩ የኮሮና ወረርሽኝ ከመከሰቱ በፊት በነበረ የክረምት ወቅት ከሶስተኛ ክፍል እስከ ስምንተኛ ክፍል ያሉ ተማሪዎች የማጠናከሪያ ትምህርት ተሰጥቷል:: በወቅቱም ከከተማው ሴቶችና ህፃናት ቢሮ ጋር በመተባበር ከፍተኛ ውጤት ላመጡ ተማሪዎች ሸልማት ተሰጥቷል:: የኮሮና ወረርሸ ወደ አገሪቱ ከገባ በኋላ ተማሪዎች እቤት ውለው የተማሩትን እንዳይረሱ በማሰብ በበጋ ወቅት የማጠናከሪያ ትምህርቶች ተሰጥተዋል:: ማህበሩም ባከናወናቸው ስራዎች በኢፌዴሪ ሴቶችና ህፃናት ሚኒስቴር ሀረርን በመወከል ተሸላሚ መሆን ችለዋል::
የህብረተሰቡ አቀባበል
የማህበሩ የገንዘብ ምንጩ የመጀመሪያው የአባላት መዋጮ ነው:: አባላቱ ማህበሩን በሶስት መንገድ ነው ማገዝ የሚችሉት:: የመጀመሪያው በገንዘብ ሲሆን ገንዘብ የሚያዋጡት ስራ ላይ ተሳትፎ የማያደርጉ ናቸው:: ሌላው በሀሳብ ድጋፍ የሚያደርጉ አሉ:: ሶስተኛው ደግሞ ስራዎች ላይ የነቃ ተሳትፎ በማድረግ በጉልበት ድጋፍ የሚያደርጉ አሉ:: የበጎ አድራጎት ማህበሩ ከተመሰረተ በኋላ የአካባቢው ሰው በበጎ ጎን በማየት እገዛ እያደረገ ይገኛል:: ማህበሩ ደከም በሚልባቸው ነገሮች ላይ ህብረተሰቡ እገዛ ከማድረግ በተጨማሪ ማበረታቻዎችን እየሰጠ ይገኛል:: በሌላ በኩል የአካባቢውን ህብረተሰብ በመሰብሰብ ከነዋሪው የቦርድ አመራር እንዲመረጥ ተደርጓል:: በአካባቢውም ማህበሩ ተቀባይነቱን እያሳደገ መጥቷል::
ማህበሩ እየሰራቸው በመጣቸው ስራዎች ህብረተሰቡ እምነት እየተጣለበት መጣ:: ቀደም ብሎ በማህበር የተሰበሰቡት ለሌላ አላማ ነው የሚሉ አስተያየቶች ነበሩ:: ገንዘብ የሚሰበስቡት ለራሳቸውም ለማዋል ነው የሚልም አመለካከቶች ነበሩ:: እነዚህን ነገሮች ወደ ጎን በመተው ስራ ላይ ብቻ በመተኮሩ እምነት ማግኘት ተችሏል:: የሰበሰቡትን ሀብት ጥቅም ላይ እያዋሉ ነው የሚለው ሀሳብ በስፋት ህብረተሰቡ ውስጥ በመግባቱ ቤቶችን ለማደስ፣ የፅዳትና የችግኝ ተከላ ስራ በተሳካ ሁኔታ ማከናወን ተችሏል::
ማህበሩ የሚገኝበት ከተማ አስተዳደር ምንም አይነት ድጋፍ እያደረገ አይደለም:: በቅርቡ ለአንድ አረጋዊት የቤት እድሳት ተደርጎ ነበር:: በዚህ ወቅት የወረዳው አስተዳደሮች የተወሰኑትን ሲደገፍ የተወሰኑ አመራሮች ደግሞ የመቃወም አዝማሚያ አሳይተው ነበር:: አንዱ ፈቅዶ አንዱ የሚከልክልበት ሁኔታዎች በመኖራቸው ችግሮች አጋጥመው ነበር::
ያጋጠሙ ችግሮች
የማህበሩ አባላት እየተንቀሳቀሱ ትኬት በሚሸጡበት ወቅት በተደጋጋሚ ለእስር ተዳርገዋል:: ትኬት በሚሸጡበት ወቅት ህገወጥ ስራ እየሰራቸሁ ነው ተብለው በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንዲውሉ ይደረጋል:: በወቅቱ ፈቃዳቸውን በማሳየት ከእስር ሊለቀቁ ችለዋል:: በሌላም በኩል በሰፈር ውስጥ የሚገኙ ወጣቶች በማህበሩ ስም የሚሰበሰበው ገንዘብ ለግል ጥቅም እየዋለ ነው በሚል ከአባላቱ ጋር ይጋጫሉ:: ማህበሩ ጠንክሮ በመስራቱ ሲቃወሙ የነበሩ ወጣቶች ወደ ማህበሩ ተቀላቅለዋል::
የወረዳው አስተዳደር ማህበሩ ቤት ማደስ ሲጀምር ፈቃደኛ ያልሆኑ አመራሮች ነበሩ:: እንጨት፣ ሲሚንቶና ቆርቆሮ ከበላይ አመራሮች የተፈቀደ ቢሆንም የሚመለከታቸው አመራሮች ይሰጥ የተባለውን ግብዓት ለመስጠት አንገራግረው ነበር:: ግብዓቶቹን ወስዶ ለመስራት ያለመስማማቶች ነበሩ:: በወረዳ አስተዳደሩ ውስጥ የተወሰኑ አመራሮች እንቅፋት እየፈጠሩ ይገኛሉ::
ማህበሩ የተመሰረተበት ወቅት አንዳንድ የማህበሩ አባላት ውስጥ ለውስጥ ውዥንብሮች ፈጥረው ነበር:: ይህን ለማስተካከል ጠቅላላ ጉባኤ ተካሂዶ የነበረ ቢሆንም የተወሰኑ አባላት የተሰበሰበው ገንዘብ እየተበላ ነው ብለው ክስ አቅርበው ነበር:: በወቅቱ የወረዳ አስተዳደሩ የማህበሩን አመራሮች በመጥራት ውይይት እንዲካሄድ አደረጉ:: በወቅቱ በማስረጃ የተረጋገጠ ነገር ስላልነበር ክሱ ውድቅ ተደርጓል:: ሌላው ማህበሩ ስራዎችን የሚያከናውንበት ቢሮ የለውም:: ከወረዳ አስተዳደሩ ለቢሮ የሚሆን ቦታ ቢሰጠንም በአቅም እጥረት ምክንያት ስራዎች ሊሰሩ አልቻሉም::
ቀጣይ እቅድ
ማህበሩ በቀጣይ ለመስራት ካሰባቸው ስራዎች ውስጥ ዋነኛው የቢሮ ችግር መፍታት ላይ ነው:: በተለያዩ ቦታ የሚገኙ ደጋፊ አባላት እርዳታ እንዲያደርጉ ሀሳብ አለ:: አሁን ከሚገኙት ተደጋፊ አረጋውያን በተጨማሪ ሌሎች አረጋውያንን ለመደገፍ ታስቧል:: የማህበሩ አባላትን ቁጥር በመጨመር የማህበሩን ተደራሸነት ለማስፋት እቅዶች ተይዘዋል:: ብዙ ስራዎች በእቅድ የተያዙ ቢሆንም በአቅም ውስንነት ምክንያት ለመስራት አልተቻለም::
ማህበሩ ለተለያዩ ስራዎች የተሰጠው ቦታ ላይ የጋራ መታጠቢያ ቤት ለመገንባት ሀሳብ ቢኖረውም በገንዘብ እጥረት እስካሁን አልተጀመረም:: ሌላው በዓል ሲመጣ ትኬት በመሸጥ ነበር ድጋፎች የሚያደረጉት ነገር ግን ለእነዚህ አይነት ስራዎች ቋሚ የሆኑ ገቢዎች የሉም::
መርድ ክፍሉ
አዲስ ዘመን ነሃሴ 14/2013