ሁሌም ፈር ቀዳጅነት ከታሪክ ጋር ያስተሳስራል። ሴት ክብሯ ጓዳዋ ነው በሚባልበት በዚያ ዘመን ከቀዳሚዎቹ የቀደመች፤ በቆንጆ ፈገግታ በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ያለች ሴት 60 ዓመታት የኋልዮሽ ተመልሰን እንድናነሳት ሞት አስገድዶናል።
ሞት የመኖር አካል ቢሆንም ዋናዎቻችንን ሲወስድብን፤ ሽማግሌ ሲያሳጣን ማየት ግን ያማል። ኢትዮጵያዊት የመገናኛ ብዙሃን አንፀባራቂ ፈርጥን ባለፈው ረቡዕ ሀምሌ 14 ቀን 2013 ዓ.ም በሞት ተነጥቀናል:: አዲስ ዘመን ጋዜጣም በሴቶች አምድ ላይ ባለሙያዋ ከስድስት አስርት ዓመታት በላይ ያበረከተቻቸውን አበርክቶዎች በጥቂቱ ለመዘከር እዚህ ቀርበናል፤ መልካም ንባብ።
በ1934 ዓ.ም ነበር ታላቋን ጋዜጠኛ ለኢትዮጵያችን የተበረከተችው። ከወላጅ አባቷ አቶ መኩሪያ ወልደስላሴና ከእናቷ ወይዘሮ ሶስና ወርቅነህ በአዲስ አበባ ከተማ ካዛንቺስ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ነው ተወልዳ ያደገችው። ወይዘሮ እሌኒ መኩሪያ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን በዘነብ ወርቅና በእንግሊዝ ስኩል /ሳንፎርድ/ ተከታትላለች።
የልጅነት ጊዜዋ ደስታን የተሞላ፣ የወጣትነት ዕድሜዋን ደግሞ በቴኒስ ጨዋታ፣ ውሃ ዋና፣ ፈረስ ግልቢያ፣ ዳንስ፣ ቴአትር ማየትና መተወን፤ እንዲሁም ልዩ ልዩ የመዝናኛ ዝግጅቶችን ማዘውተር ምርጫዋ እንደነበረ የቅርቦቿ የሚመሰክሩላት ይች ሴት በአንድ ቃለ-ምልልስ ላይ እንደገለፀችው ገና በአፍላ የታዳጊ ዘመንዋ ለልዑል መኮንን መታሰቢያ ሆስፒታል የግንባታ ስራ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ-ግብር በተዘጋጀበት ወቅት አንድ አጭር የመድረክ ቴአትር ተውና የነበረ መሆኑን ተናግራለች።
በመቀጠል አዲስ አበባ ከተማ በተቋቋመው የወጣት ሴቶች ክርስቲያናዊ ማህበር /ወሴክማ/ ውስጥም ንቁ ተሳትፎ ስታደርግ የኖረችው ወጣት በተፈጥሮዋ ሳቂታ፣ ቀልድ አዋቂና በቀላሉ ከሰው ጋር ተግባቢ ነበረች። በሳንፎርድ ትምህርት ቤት መማሯ የእንግሊዘኛ ቋንቋ ክህሎት እንዲኖራት ያደረገላት ወይዘሮ እለኒ፣ የልጅነት ምኞቷ በማህበራዊ ሳይንስ ትምህርት የበለጠ ትኩረት ማድረግ የነበረ መሆኑን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ምንም እንኳን ምኞቷ ማህበራዊ ሳይንስ ዘርፍ ላይ መሳተፍ ቢሆንም በ1951 ዓ.ም ቤሩት በሚገኘው የአሜሪካ የነርሶች ማሰልጠኛ ዩኒቨርሲቲ የነርስ ሙያ ነጻ የትምህርት ዕድል በማግኘቷ በድሉ ተጠቅማም ነበር። ቤተሰቦቿ በወቅቱ ወደ ህክምና ሙያው እንድታዘነብል ግፊት ያደርጉባት የነበረው የአያቷን ፈለግ እንድትከተል ከመነጨ ጉጉት ቢሆንም ወትሮም ቢሆን የእሌኒ ፍላጎት ከህክምና ውጪ ስለ ነበር ከጥቂት ቆይታ በኋላ ትምህርቱን ሳትገፋበት አቋርጣ ወዳገር ቤት ተመለሰች።
እንደሚታወቀው በኢትዮጵያ ዘመናዊ የህክምና ታሪክ የመጀመሪያው ሀኪም የሚባሉት ሀኪም ወርቅነህ እሸቴና የአንጋፋዋ ጋዜጠኛ እሌኒ ወላጅ እናት ወይዘሮ ሶስና አባት ሲሆኑ ጣሊያን ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት በልዩ ልዩ ሀገራት በሙያቸው አገልግለዋል። ከድል በኋላም በንጉሱ ትዕዛዝ በአባይ ወንዝ ላይ ኢትዮጵያ ስለምትገነባው ግድብ ከአሜሪካ ባለስልጣናት ጋር እንዲደራደሩ ተወክለው ተልከዋል:: “በኢትዮጵያ የጋዜጠኝነት ታሪክ ላይ ደማቅ አሻራ አሳርፋለች” ሲሉ የቅርብ የሙያ አጋሮቻቸው የሚገልጿቸው እሌኒ በ1950ዎቹ የቴሌቪዥን ሥርጭት የቴክኖሎጂ ስልጣኔ ዓለምን ባስደመመበት ወቅት የሕይወታቸውን አቅጣጫ ወዳላሰቡት መስመር የሚቀይር አንድ አስገራሚ ክስተት ተፈጠረ።
ከቤሩት መልስ የማህበራዊ አገልግሎት ሙያተኛ /ሶሻል ወርከር/ በመሆን ሕብረተሰቡን የማገልገል ውጥንን ሰንቃ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ማህበራዊ ሳይንስ የትምህርት ዘርፍ ትምህርቷን የቀጠለችው እሌኒ፣ ብዙም ሳይቆይ የቀድሞው የኢትዮጵያ ራዲዮ ዓለም አቀፍ አገልግሎት ወይም ብስራተ-ወንጌል ይባል የነበረው የራዲዮ ጣቢያ የእንግሊዘኛ ፕሮግራም ለመጀመር ጋዜጠኞችን አወዳድሮ መቅጠር እንደሚፈልግ የሚገልጽ ማስታወቂያ ስትሰማ ትኩረቷ በመሳቡ ተወዳድራ ፈተናውን ካለፈች በኋላ ዛሬ ከፍ ወዳለ የስኬት ማማ ያወጣትንና “የመጀመሪያዋ እንስት ኢትዮጵያዊት የቴሌቪዥን ጋዜጠኛ” ያሰኛትን ሙያ አንድ ብላ መጀመሯን ከአራት ዓመታት በፊት ለታላቅ የሙያ ስኬት የበቁ እንስት ኢትዮጵያውያትን የእውቅና ሽልማት በመስጠት የሚያበረታታው ኤዩብ ኢትዮጵያ ኤውብ የተሰኘው ድርጅት የ2017 ዓ.ም አሸናፊ መሆናቸውን ካበሰረ በኋላ ስሜታቸውን እንዲገልጹ በሰጣቸው እድል አጠር ያለ ቃለ-ምልልስ ያደረጉ ሲሆን ምልልሳቸውን ቀጥለን በምንገልፀው ላይ ያጠነጠነ ነበር::
ዕውቋ ጋዜጠኛ እሌኒ መኩሪያ በጋዜጠኝነት ሙያ ከተሰማሩ በኋላ ቀደም ሲል እንደገለጹት፣ በወቅቱ በአሜሪካ የልማት ተራድኦ ድርጅት በተልዕኮ ትምህርት የሚሰጠውን የጋዜጠኝነት ሙያ መሰረታዊ ሥልጠና ተከታትለዋል:: የእንግሊዘኛ ቋንቋ ክሂሎታቸው በአለቆቻቸው ዘንድ አድናቆትና ዕውቅና ስላተረፈላቸው ብዙም ሳይቆዩ ከዓለም አቀፉ የራድዮ ጣቢያ በተጨማሪ በኢትዮጵያ ራድዮ ብሔራዊ አገልግሎትም በተመሳሳይ ቋንቋ ዜና አንባቢነት፣ የሙዚቃና የመዝናኛ ፕሮግራሞች አዘጋጅነትና የቃለ መጠይቅ ዝግጅቶችንም ደርበው እንዲሰሩ በር ከፍቶላቸዋል::
ከውጭ በቀሰሙት የሙያ ልምድም የኢትዮጵያ ራዲዮን የድምጽ ክምችት መዘክር ክፍልን /ኣርካይቭ/ በዘመናዊ መልክ በማደራጀት ቆየት ያሉ በሸክላ የተቀረጹ ድምጾች፣ ሪል ቴፖች፣ ካሴቶችና የሲዲ ማቴሪያሎች፤ እንዲሁም ልዩ ልዩ ታሪካዊ የጽሁፍ መዛግብትን በዓይነት እና በዘመናቸው በካታሎግ ሥርዓት ለይቶ በማደራጀት ጋዜጠኞችና የምርምር ባለሙያዎች በፈለጉት ጊዜና በቀላሉ እንዲጠቀሙ የሚያስችላቸውን አሰራር ዘርግተዋል::
ግንቦት 18 1955 ዓ.ም የቀድሞ የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ጽ/ቤት አዲስ አበባ ውስጥ ሲፈረም የ21 ዓመቷ ወጣት ጋዜጠኛ እሌኒ መኩሪያ የስብሰባውን ሂደት ተከታትላ በእንግሊዘኛ ቋንቋ በመዘገብ ቀዳሚዋ ሴት ጋዜጠኛ ሆናለች:: ከዛም በኋላ በ1957 ዓ.ም የአፍሪቃ ህብረት ኦፊሴሊያዊ ምስረታን አስመልክቶ ለመጀመሪያ ጊዜ በሀገሪቱ የምስረታውን ሂደት ለዓለማቀፉ ማህበረሰብ ለማስተላለፍ የቴሌቪዥን ጣቢያ ሲቋቋም በአፍሪቃ ህብረት አዳራሽ ተገኝታ የድርጅቱን ምስረታና የስብሰባውን ሂደት በቴሌቪዥን በመዘገብ የመጀመሪያዋ ኢትዮጵያዊት እንስት የቴሌቪዥን አንባቢ በመሆን በታሪክ ተመዝግባለች::
ወዳጆቻቸው እና የሙያ አፍቃሪዎቻቸው «የሰው ልክ» እያሉ የሚያወድሷቸው ጋዜጠኛዋ ከኢትዮጵያ ራድዮና ቴሌቪዥን ጣቢያዎች ሌላ እንደ ቢቢሲ ላሉ ዓለማቀፍ የሚድያ ተቋማት የዜና ወኪል ሆኖ በመስራት ከፍተኛ የሙያ ልምድን አካብተዋል:: እንደ ጎርጎሪያዊያን አቆጣጠር በ2001 ዓ.ም በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅትም በግጭቱ የተፈናቀሉ በመጠለያ የሚገኙ ወገኖችን ለመርዳት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰላም አስከባሪ ተልዕኮ /አንሚ/ አማካኝነት ለተነደፈው በአማርኛ፣ ትግርኛና እንግሊዘኛ ቋንቋዎች የሚተላለፍ የራዲዮ ሥርጭት ለአምስት ዓመታት በፕሮግራም አስተባባሪነት አገልግለዋል:: በጋዜጠኝነት፣ በሕዝብ ግንኙነት ሙያና በበጎ አድራጎት ተግባራቸው የሚታወቁት ወይዘሮ እሌኒ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ጣቢያ ሲመሰረት ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ ሳሙኤል ፈረንጅና እንደ ልዑል ሰገድ ኩምሳ፣ ታቦቱ ወልደሚካኤል፣ ላዕከማርያም ደምሴና ሌሎችም የሙያ ባልደረቦቻቸው ለደረሱበት ከፍተኛ ስኬት ቁልፍ ሚና እንደነበራቸው በተለያዩ መድረኮች ገልፀዋል::
ለቢቢሲ ዘጋቢ በነበሩባቸው ከ8 የሚልቁ ዓመታት በተለይም ደግሞ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ፈታኝ ወቅት የግንባር ዘገባዎችን ከባለሙያዋ ጋር ተቀራርበው በሙያ እየተደጋገፉ መስራታቸውንም ያስታውሳል:: የሳቸውን አሻራና የሙያ ፈለግ ተከትላ በአሁኑ ወቅት ሸገር ኤፍ ኤም ራድዮ 102.1 ላይ ለአፍሪቃውያን የሚዘጋጅ የሙዚቃ ፕሮግራም የምታቀርበው ልጃቸው ቀፀላ ሰይፉም እናቴን በአንድ ቃል ብገልጻት “ፍፁም ፍቅር ነበረች” ስትል የእምባ ሳግ እየተናነቃት ነግራናለች:: “እንኳን ለሰው ልጅ ለእንስሳና እጽዋት ጭምር አዛኝ፣ ረዳት፣ ቸርና ለጋስ የሆነች፤ ጎዳና የወደቀን አንስታ የምትረዳ ድንቅ እናት ነበረችም” ብላለች ቀፀላ::
“ሴቶች በእራስ የመተማመን ችሎታን በማዳበርና የባህል ተጽዕኖ በመቋቋም በዕውቀት፣ በትምህርትና በጥረት ከወንዶች እኩል አልያም የላቀ አስተዋጽኦ ማበርከት ይችላሉ” የሚል ጠንካራ ዕምነት የነበራቸው ጋዜጠኛ እሌኒ መኩሪያ በሴቶች ጉዳይ በተለይም ለአካለ መጠን ያልደረሱ ሴት ታዳጊ ሕጻናት ላይ የሚደርሰውን አካላዊና የመንፈስ ጥቃት በተጓዳኝም ያለእድሜ ጋብቻን በተመለከተ ግንዛቤን የሚሰጡ ልዩ ልዩ ዶክመንተሪ ፊልሞችን አዘጋጅተው በሀገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ተዘዋውረው ለሕብረተሰቡ በማሳየት ከፍተኛ የግንዛቤና የማንቃት ስራ አከናውነዋል::
እነዚህ ፊልሞች በለንደኑ ቻናል-4፣ በአሜሪካና አውስትራሊያ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ከመተላለፋቸውም ሌላ ፊልሙ ዓለማቀፍ አድናቆት በማግኘቱ የምርጥ ስራ ስኬት የሙያ አርበኛ በሚል እንደ ጎርጎሪሳዊያን አቆጣጠር በ2001 ዓ.ም ከለንደኑ አልትሩሳ ኢንተርናሽናል ድርጅት ልዩ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል:: በመሰረተ ትምህርት ዘመቻ፣ በኢትዮጵያ የሴቶች ድጋፍ ሰጪ ማህበር፣ በማህበራዊ ግልጋሎት ድርጅትና በሌሎችም ግብረ ሰናይ ድርጅቶች ውስጥ የሴቶችን ችግር ለመፍታትና የሙያ ብቃታቸውን ለማጎልበት ለረጅም ዓመታት ነጻ የበጎ አገልግሎት ተግባር ላይ ተሰማርተው የዜግነት ግዴታቸውን ተወጥተዋል:: ለታሪክ ከፍተኛ ፍቅርና አትኩሮት የነበራቸው ጋዜጠኛ እሌኒ የጡረታ ጊዜያቸውን በማንበብና በምርምር ስራ ማሳለፋቸውን ወዳጆቻቸውና ቤተሰቦቻቸው ይናገራሉ::
ሁልጊዜ ለምለምና አረንጓዴ ኢትዮጵያን ለማየት የሚናፍቁትና ተፈጥሮን የማድነቅ ዝንባሌ የነበራቸው ባለሙያዋ ስለሃገራችን ዛፎችና ዕጽዋት የሚያስተዋውቅ በምስል የተደገፈ መጽሐፍ አዘጋጅተው ለንባብ አብቅተዋል::
በኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙሃንና የጋዜጠኝነት ታሪክ ስማቸው እንዲህ በጉልህ የሚጠቀሰው እሌኒ መኩሪያ የኢትዮጵያ ሴት ጋዜጠኞች ማህበር እንዲመሰረትና እንዲጠናከር ካደረጉ ግንባር ቀደም ሙያተኞች አንዷ ሲሆኑ በአመራርነትም አገልግለዋል:: የአፍሪቃ ሴቶች የሚድያ ኮሚቴ የአማካሪዎች የቦርድ አባልም ነበሩ::
በ1959 ዓ.ም ከባለቤታቸው ኢንጂነር ሰይፉ ለማ ጋር ትዳር መስርተው 3 ሴት ልጆችን ያፈሩት ጋዜጠኛ እሌኒ መኩሪያ፣ ባደረባቸው ህመም በሀገር ውስጥና በውጭ በህክምና ሲረዱ ከቆዩ በኋላ የማይሞት ታሪካዊ አሻራቸውን ለተተኪው ትውልድ ትተው ባለፈው ረቡዕ ሀምሌ 14 2013 ዓ.ም በተወለዱ በ79 ዓመታቸው ሕይወታቸው አልፏል:: ሥርዓተ ቀብራቸውም በማግስቱ አዲስ አበባ ከተማ በሚገኘው የካ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ቤተሰቦቻቸው፣ በርካታ አድናቂዎቻቸውና ወዳጆቻቸው በተገኙበት ተፈጽሟል::
“የቱንም ያህል የኑሮ ፈተና የቱንም ያህል የሕይወት ውጣ ውረድ ቢገጥመኝ አምላክ እስትንፋሴን እስኪወስዳት ፈጽሞ ተስፋ አልቆርጥም::” በአንድ ቃለ ምልልስ ይህን ያሉት አንጋፋዋና ተወዳጇ የመጀመሪያዋ እንስት የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ጋዜጠኛ ናቸው። ለታላቋ ሴትም ነፍሳቸውን በአፀደ ገነት ከደጋጎቹ ጎን ያኑርልን ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መፅናናትን ይስጥልን ብለናል።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ነሐሴ 2/2013