አገሪቱና ሕዝቧ በወቅታዊ ጉዳይ ፋታ አጥተዋል። ወሬው ሁሉ ‹‹ህ.ወ.ሓ.ት፣ ጁንታ፣ ተደመሰሰ፣ ተቆጣጠሩት፣ የህልውና ዘመቻ …›› ሆኗል።በእውቀትና በስነ ምግባር ደጅ ያላለፉ ‹‹አክቲቪስት›› ተብዬዎች የሚነዙትና ተከታዮቻቸው ተቀብለው የሚያራግቡት የውሸት መረጃ ሰፊውን ሕዝብ በእጅጉ ግራ አጋብቶታል።ሕዝቡ በውሸት መረጃዎችና ፋይዳ በሌላቸው አሉባልታዎች ግራ ከመጋባቱ ባሻገር፣ ሌሎች አገራዊ ጉዳዮች ተዘንግተዋል።
ጦርነትን በፌስቡክ በቀጥታ (Live) የሚያስተላልፉት ‹‹አክቲቪስት›› ተብዬዎቹ ስለሌሎች ወሳኝ አገራዊ ጉዳዮች የማውራት ፍላጎትም ሆነ ብቃት እንደሌላቸው ይታወቃል። ባለፈው ሳምንት የትዝብት ምልከታዬ ላይ እንደገለፅኩት ‹‹አክቲቪስት›› እየተባሉ የሚጠሩት ግለሰቦች ከመረጃ አያያዝና አቀራረብ ስርዓት ጋር የማይተዋወቁ እንዲሁም ምን ዓይነት መረጃ በይፋ እንደሚነገርና እንደማይነገር እንኳ ለይተው የማያውቁ ቂሎች ናቸው። የሚያሰራጯቸው መረጃዎችም በውሸት የታጨቁ፣ ብሔራዊ ጥቅምንና ወቅታዊ ሁኔታን ከግምት ውስጥ ያላስገቡ፣ ማኅበረሰባዊ እሴቶችን የጣሱ እንዲሁም ኢትዮጵያን ለበርካታ ጫናዎች የዳረጉ የጣሱ የጥራዝ ነጠቆች ፕሮፖጋንዳዎች ናቸው፡፡
መንግሥታዊ ዝርክርክነቱም ‹‹በለው፣ ፍለጠው፣ ቁረጠው፣ ተደመሰሰ …›› የሚሉ ጥራዝ ነጠቅ ‹‹አክቲቪስቶች›› የመረጃ ምንጭ እንዲሆኑ ፈቅዶላቸዋል። መንግሥት ወቅታዊ፣ ተዓማኒና የአገሪቱን ነባራዊ ሁኔታዎች የሚመጥን መረጃ መስጠት እጅግ ከብዶታል።ሕዝቡ የየትኛውን ወገን መረጃ ማመን እንዳለበት ግራ ገብቶታል።የጥራዝ ነጠቅ አክቲቪስቶችን መረጃ ከተመለከተና ካዳመጠ በኋላ፣ መንግሥት መረጃ ይሰጠኛል ብሎ ተስፋ ቢያደርግም የመንግሥት ነገር ‹‹ቄሱም ዝም፤ መጽሐፉም ዝም›› እንደሚባለው እየሆነ ነው።ሕዝቡ የውሸት መረጃዎችን የሚያሰራጩና መረጃዎች እንዴትና መቼ ይፋ መሆን እንዳለባቸው የማያውቁ ‹‹አክቲቪስቶች››ን በመረጃ ምንጭነት የሚጠቀመው ትክክለኛ መረጃ የሚሰጠው ሁነኛ የመንግሥት አካል ባለመኖሩ ነው፡፡
ሕዝቡ በ‹‹አክቲቪስቶች›› አደናጋሪ መረጃ ምክንያት ግራ ከመጋባቱም ባሻገር ስለሌሎች ወሳኝና ትልልቅ አገራዊ ጉዳዮች መረጃ እያገኘ አይደለም።በዚህም ምክንያት እንደግብርና፣ የኑሮ ውድነት፣ ክረምቱን ተከትሎ የሚከሰቱ አደጋዎችና ሌሎች ትልልቅ ጉዳዮች ችላ ተብለዋል።ነገሮቹ ችላ የተባሉት በአክቲቪስቶች ብቻ ሳይሆን በመገናኛ ብዙኃንም ጭምር ነው።ይህ ደግሞ ጉዳዩን ይበልጥ አስጊ ያደርገዋል።እነዚህ ጉዳዮች ችላ ከተባሉ በአገሪቱ ላይ የሚደርሰው ተፅዕኖ እጥፍ ድርብ ይሆናል።
ለመሆኑ ግብርናችን እንዴት ነው? ወቅቱ በአብዛኞቹ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የመኸር እርሻ ስራ የሚከናወንበት ጊዜ ነው። ስለሆነም የእርሻ ስራው፣ የግብዓት አቅርቦቱና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ዕለታዊ ክትትል ይፈልጋሉ። የጎደለውን መሙላት፤ የተበላሸውን ማስተካከል ያስፈልጋል።
የግብርናው ዘርፍ የአገሪቱ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት ስለሆነ የዚህ ወሳኝ ዘርፍ እያንዳንዱ እንቅስቃሴ ከፍተኛ ትኩረት ይፈልጋል። እነዚህ ጉዳዮች የማይካዱ ጥሬ ሀቆች ሆነው ሳለ በተግባር የምናየው ግን ሀቆቹን የሚደግፍ አይደለም።አክቲቪስቶችም ሆኑ መገናኛ ብዙኃን የግብርና ተቋማት ለዘርፉ ውጤታማነት እያደረጉ ከሚገኘው እንቅስቃሴ ይልቅ ለ‹‹ሕልውና ማስከበር ዘመቻ›› ስላደረጉት ድጋፍ የሚነግሩን ዜናዎች ይበዛሉ።
የዘንድሮው ግብርና ባለፈው ጊዜ በተከሰቱት የአንበጣ መንጋ እና የተፈጥሮ አደጋዎች (በተለይ ጎርፍ) ምክንያት ልዩ ትኩረት የሚሻ ነው።በአንበጣ መንጋና በጎርፍ ምክንያት ባለፈው ዓመት ምርት የቀነሰባቸውን አካባቢዎች ዘንድሮ የተሻለ ምርታማ በማድረግ ማካካስና ከዘርፉ የሚጠበቀውን አገራዊ የምርት መጠንም ማሳደግ ያስፈልጋል፡፡
የግብርናው ዘርፍ ለአፍታም ቢሆን ትኩረት ሊነፈገው አይገባም።ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ግብርና ዘንግተው መኖር አይችሉም። [ቢያንስ ለዓመታት በምኞት ላይ የኖረው ‹‹ኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ›› እውን እስከሚሆን ድረስ ግብርናውን መዘንጋት አንችልም] የኑሮ ውድነቱስ? የዋጋ ንረት በየጊዜው ማሻቀብ እንጂ ዝቅ ማለት አልሆነለትም።ይህም የኅብረተሰቡን፣ በተለይም ዝቅተኛ ገቢ ያለውን የኅብረተሰብ ክፍል፣ ኑሮ እጅግ የከበደ እንዲሆን አድርጎታል።ለዋጋ ንረቱ የተለያዩ ምክንያቶች ሲጠቀሱ ቆይተዋል። የዶላር የምንዛሬ ዋጋና የነዳጅ ዋጋ መጨመር እንዲሁም የምርት ግብዓቶችና የውጭ ምንዛሬ አቅርቦት እጥረት ተደጋግመው ሲነገሩ የኖሩ የዋጋ ንረቱ ምክንያቶች ናቸው።
እነዚህ ምክንያቶች ተደጋግመው ይገለፁ እንጂ ኑሮ ናላውን ላዞረው ኅብረተሰብ በሚፈለገው ደረጃ መፍትሄ አላስገኙም። ‹‹ኑሮውን አልቻልነውም … የዋጋ ንረቱ መፍትሄ ሊበጅለት ይገባል …›› የሚሉና ከተለያዩ አቅጣጫዎች ሲደመጡ የቆዩ የኅብረተሰብ ድምፆች ዛሬም እየተስተጋቡ ነው።አንዳንድ ግለሰቦች የዘንድሮው የዋጋ ንረት ከዚህ ቀደም ከነበረው ሁሉ የተለየ ስለመሆኑ ተናግረዋል።በአንዳንዶቹ ምርቶች ላይ ደግሞ በገበያ የሚታየው የዋጋ ንረት ጠዋት እና ከሰዓት በኋላ የዋጋ ልዩነት እስከማሳየት የደረሰ ነው፡፡
እጅግ የሚያስገርመው ነገር አገሪቱ ከበቂ በላይ የምታመርታቸው ምርቶች ሳይቀሩ ዋጋቸው ሰማይ መድረሱ ነው። ለአብነት ያህል የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶች ከበቂ በላይ ተመርተው ከማሳ የሚያነሳቸው አጥተው ለብክነት እንደሚዳረጉ የምርቶቹ ባለቤቶች ይናገራሉ።በከተሞች ያለው የእነዚህ ምርቶች ዋጋ ግን ‹‹ጆሮ አይስማ›› የሚያሰኝ ነው።
ከዓመት ዓመት መጨመር እንጂ መቀነስ ለማያሳየው ከፍተኛ የዋጋ ግሽበት መንስዔዎቹ መሠረታዊ የሆኑ የምጣኔ ኃብት መዋቅሮች አለመስተካከል፣ የምርት አቅርቦት እየቀነሰ መምጣት እንዲሁም የሰላምና የፀጥታ መደፍረስ እንደሆኑ የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች ያስረዳሉ። የውጪ ምንዛሬ እጥረት እና የገንዘብ የመግዛት አቅም መዳከም ተደራርበው የኑሮ ውድነትን ማክበዳቸውንም ይገልጻሉ።
የማዕከላዊ ስታቲስቲክስ ኤጄንሲ ባለፈው ሰኔ ወር መጨረሻ ላይ ይፋ ባደረገው መረጃ፣ የሰኔ ወር የዋጋ ግሽበት ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር በ24 ነጥብ አምስት ከመቶ ጭማሬ አሳይቷል።የወሩ የምግብ ዋጋ ግሽበት፣ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር፣ የ28 ነጥብ ሰባት በመቶ ጭማሪ ያሳየ ሆኖ ተመዝግቧል። ጥራጥሬ፣ ዳቦ፣ ሥጋ፣ የምግብ ዘይት፣ ቅቤ፣ ቅመማ ቅመም፣ በርበሬና ቡና ዋጋቸው በየጊዜው እየጨመረ ነው።ምግብ ነክ ያልሆኑ እቃዎችም ዋጋቸው፣ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር፣ የ19 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል።የሰኔ ወር አጠቃላይ የዋጋ ግሽበት ከግንቦት ወር ጋር ሲነፃፀር ሰባት በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን የኤጀንሲው መረጃ አመልክቷል። የመጨመር እንጂ የመቀነስ አዝማሚያ ማሳየት የማይታይበት የእቃዎችና የአገልግሎቶች ዋጋ በሐምሌ ወርም እንደተለመደው ይጨምራል እንጂ ይቀንሳል የሚል ተስፋ የለም።
የኑሮ ውድነት የሕዝቡን ጓዳ ፈትሿል።በየቀኑ እየተሰቀለ የሚሄደው የእቃዎችና የአገልግሎቶች ዋጋ ሕዝቡን በእጅጉ አስጨንቋል። ከላይ እንደተጠቀሰው የኑሮ ውድነቱ ምክንያቶች ዓይነተ ብዙ ቢሆኑም ጉዳዩ ጠንካራ የሆነ መንግሥታዊ ቁርጠኝነትን የሚፈልግ ወሳኝ አጀንዳ ነው። የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች እንደሚሉት፤ በአገሪቱ እየታየ ያለው የኑሮ ውድነት ዘላቂ መፍትሄ ሳያገኝ ከቀጠለ አገሪቷን ውስብስብ ወደ ሆነ ችግር ሊመራት ይችላል። ስለሆነም መንግሥት ሰላምን በማስፈን ለኑሮ ውድነቱ የአጭር፣ የመካከለኛና የረጅም ጊዜ መፍትሄዎችን ማበጀት ይጠበቅበታል። ጉዳዩ ትኩረት መነፈጉ ደግሞ ጫናው ከዚህ የባሰ እንዳይሆንም ያሰጋል።
ክረምቱን ተከትሎ ሊከሰቱ የሚችሉ አደጋዎችም ትኩረት ሊነፈጋቸው አይገባም።መሰል አደጋዎች ባለፈው ዓመት በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ተከስተው በሰው ሕይወትና በንብረት ላይ ብዙ ጉዳት ማድረሳቸው ይታወሳል። ስለጉዳዮቹ ማስታወስና ስለቅድመ መከላከል እርምጃዎች መነጋገር አደጋዎቹ ዘንድሮም ተመሳሳይ ጥፋት እንዳያስከትሉ መፍትሄ ለመፈለግ የሚከናወነው ስራ የመጀመሪያ እርምጃ እንደሆነ ሊታወቅ ይገባል።
ግን ወሬው ሁሉ ስለክተት ዘመቻ በሆነበት ሁኔታ ስለግብርናም ሆነ ስለኑሮ ውድነት ማውራት የማይታሰብ እየሆነ ይመስላል። ወሳኝ ጉዳዮችን ዘንግቶ ስለወቅታዊ ጉዳይ ብቻ እየደሰኮሩና ሕዝብን ግራ እያጋቡ መቀጠል ተራዛሚና ለአገር አደጋ ተራዛሚ የሆኑ ብዙ ችግሮችን ይጋብዛሉ፡፡
ሕዝቡ ለአክቲቪስቶች መረጃ ጆሮ እንዲሰጥ መገደዱ ከሕግ ማስከበር ዘመቻው ባሻገር ያሉ ትልልቅ አገራዊ ጉዳዮች ተገቢውን ትኩረት እንዳያገኙ አድርጓል ማለት ይቻላል።የውሸት መረጃዎች ቦታ እንዳያገኙ ሲደረግ እንደግብርናና የኑሮ ውድነት ያሉ ጉዳዮች ትኩረት አይነፈጉም።ለዚህ መሳካት ደግሞ መንግሥት እውነተኛና ወቅታዊ መረጃን ለሕዝብ ማቅረብ ይገባዋል። ሕዝቡም የራሱ ኃላፊነት አለበት።የመረጃዎቹን ምንጮች ታማኝነት መገምገም፣ ምንጮቹ ከዚህ ቀደም ስለነበራቸው ልምድ/ታሪክ ማጣራት፣ የመረጃዎቹ ዓላማዎች ምን ሊሆኑ እንደሚችሉ ማሰላሰል፣ የታወቀ የመንግሥት አካል ማረጋገጫ እስከሚሰጥ ድረስ መረጃዎቹን ለሌሎች አለማጋራት እንዲሁም አደገኛ የሐሰት መረጃዎችን በሚያሰራጩ አካላት ላይ መንግሥት ተገቢውን ሕጋዊ እርምጃ እንዲወስድ ግፊት ማድረግ ከሕዝቡ የሚጠበቁ ኃላፊነቶች ናቸው።እነዚህ የመፍትሄ እርምጃዎች ሐሰተኛ መረጃዎቹ ሊፈጥሩ የሚችሏቸውን አደጋዎች ሙሉ በሙሉ ማስቀረት ባይችሉ እንኳ አደጋዎቹን ለመቀነስ ግን ያስችላሉ፤ ሌሎች አገራዊ ጉዳዮችም ትኩረት እንዳይነፈጋቸው ለማድረግ ያግዛሉ።
በእርግጥ ስለግብርናም ሆነ ስለኑሮ ውድነት ማሰብ የሚቻለው ሰላም ሲኖርና የአገር አንድነት ሲጠበቅ እንደሆነ አይካድም። እርሻንም ሆነ ሌሎቹን የስራ እንቅስቃሴዎች ያለሰላም ማሰብ አይቻልም።የግብርና ስራን ተረጋግቶ ማከናወንም ሆነ ስለኑሮ ውድነት መፍትሄ መፈለግ የሚቻለው ሰላም ሲኖር ነው። ነገር ግን ሁሉም ጉዳዮች የየራሳቸው ትኩረት ሊሰጣቸው ይገባል።ለዚህም ስራን ተከፋፍሎ ማከናወን ያስፈልጋል።የሕግ ማስከበር እርምጃው ሲጠናቀቅ ሕዝቡ ስለምርት እጥረት ጉዳይ እንዳይጨነቅና አገሪቱም ቀደም ሲል ትኩረት ተነፍጓቸው የቆዩ ጉዳዮች በሚፈጥሯቸው አደጋዎች ምክንያት እንዳትፈተን ከወዲሁ ማሰብ ተገቢ ነው።
አንተነህ ቸሬ
አዲስ ዘመን ሐምሌ 26/2013