የትምህርት ቤት ምገባ መርሐ ግብር ተማሪዎችን በተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ችግር ምክንያት የተጎዱ ተማሪዎች የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኙና በትምህርታቸው ውጤታማ እንዲሆኑ ያስችላል። የመማር ማስተማሩ ሂደት እና የተማሪዎች ተሳትፎ ከማሳደግ ባሻገር እንደ ሀገር ውጤታማና ንቁ ዜጎችን በፍትሃዊነት ለማፍራት የሚያግዝ እንደሆነም ይታመናልና። በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ሀገራት መርሐ ግብሩ ተግባራዊ ቢደረግ ውጤቱ ብዙ እንደሚሆን እሙን ነው።
የትምህርት ቤት ምገባ መርሐ-ግብር በሃገራችን ተግባራዊ መደረግ ከጀመረ አምስት አሥርት ዓመታትን እንዳስቆጠረ መረጃዎች ያሳያሉ። መርሐ ግብሩን በመጀመር ረገድ ደግሞ ግለሰቦች እና ድርጅቶች ግንባር ቀደም ቢሆኑም፤ በመንግሥት ደረጃ በ1987 ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ በዓለም የምግብ ፕሮግራም እንደተጀመረ ይነገራል።
በተለይም በአገሪቱ ድርቅ በተከሰተበት በ2009 ዓ.ም መንግሥት 570 ሚሊዮን ብር በጀት በመመደብ በስምንት ክልሎች ከሦስት ሚሊዮን በላይ ለሚጠጉ ዜጎች የተደረገው ምገባ በአብነት ይጠቀሳል። በሃገራችን የትምህርት ቤት ምገባ መርሐ ግብር ተግባራዊ መደረግ ከጀመረ ረጅም ዓመታት ቢቆጠሩም፤ በተለይ መንግሥት የሚፈለገውን ያህል ትኩረት ሰጥቶ እንዳልሰራ በርካቶች ሲናገሩ ይደመጣሉ። ነገር ግን መንግሥት ላለፉት በርካታ ዓመታት ለጉዳዩ የነፈገውን ተገቢ ቦታ የመስጠት አዝማሚያዎችን ያሳየ ስለ መሆኑ አብረው ይገልጻሉ። የትምህርት ቤት ምገባ መርሐ ግብር ለሃገራችን እንግዳ ባይሆንም፤ ተገቢውን ትኩረት ተሰጥቶት ባለመሰራቱ ለብዙዎች እንግዳ አድርጎታል።
የአዲስ አበባ መንገድ
በተለይ ከባለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህ የተጀመሩ ስራዎች የትምህርት ቤት ምገባ መርሐ ግብር እንደ አዲስ እንዲያንሰራራ ሆኗል። ለዚህ ደግሞ በዋነኝነት የአዲስ አበባ መንገድ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ሲሆን፤ የትምህርት ቤት ምገባን በሚፈለግ ደረጃ መስራት ከተቻለ ለትምህርት ዘርፍ ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ ለሀገር እድገት አበርክቶው ከፍተኛ የመሆኑን ሃቅ ያስመሰከረ ነበር።
በአዲስ አበባ ከተማ የተጀመረው የተማሪዎች ምገባ
መርሐ ግብር ተገቢውን ትኩረት ካገኘ ውጤት የሚያመጣ መሆኑን ከሃገር አልፎ ከሰሞኑ በጣሊያን ሮም ከተማ ተካሂዶ በነበረው የዓለም ስነ ምግብ ኮንፈረንስ ላይ በተሞክሮነት መቅረብ ችሏል።
“ከተማ አስተዳደሩ በምገባ ዘርፍ የጀመራቸው ስራዎች ለሌሎች ሀገራትም ምርጥ ተሞክሮ ነው” ተብሎ በዓለም ምግብ ኮንፈረንስ እንዲቀርብ መወሰኑን ተከትሎ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ የስነ ምግብ ዘርፍ አማካሪ ወ/ሪት ሜቲ ታምራት ለኮንፈረንስ ተሳታፊዎቹ ሲያቀርቡ፤”ከተማ አስተዳደሩ በባለፈው በጀት ዓመት ለትምህርት ምገባ ከ1 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ በመመደብ በከተማዋ እና በዙሪያዋ ለሚገኙ ከ600ሺህ በላይ ተማሪዎች የምገባ ፕሮግራም ተጠቃሚ ሆነዋል።
በዚህም ተማሪዎች የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኙ ከማድረግ ባለፈ የተማሪዎችን ውጤት በማሳደግ ፤ የመድገምና የማቋረጥ ምጣኔን በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ ተችሏል”ሲሉ የአዲስ አበባ ተሞክሮ ከሃገር አልፎ ለዓለም አርአያ ሆኖ የሚጠቀስ ተግባርን የተከማቹ ችግሮች ቢኖሩም በአጭር ጊዜ በማሳካት ተሻጋሪ ስራ መሰራቱን አብራርተዋል።
የአዲስ አበባ ስኬት ወደ ሀገር
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በዓለም ዓቀፍ ደረጃ እንደ ተሞክሮ መነሳቱ ትልቅ ደስታና መነቃቃትን ከሰሞኑ ይፍጠር እንጂ ፤ በሃገር አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ መነሳሳትን ከፈጠረ ሰንበትበት ብሏል። ከአዲስ አበባ ስኬት እንደ ሀገር የተለያዩ ቁምነገሮችን የተወሰዱበት የነበረ ሲሆን ፤በአንድ ወገን ቀደም ሲል የነበሩትን ክፍተቶች በማረቅ በቁርጠኝነት መስራት ከተቻለ ፕሮግራሙ ውጤታማ የሚያደርግ መሆኑን እንዲታይ አድርጓል።
በሌላ ወገን ደግሞ የተማሪዎች ምገባ መርሐ ግብር ልዩ ትኩረት ሰጥቶ ተግባራዊ ቢደረግ በሃገር አቀፍ ደረጃ ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ የሚቻል ስለመሆኑ ከተወሰዱ ቁምነገሮች መካከል ይገኙበታል።በተለይ ደግሞ በመርሐ ግብሩ ግለሰቦች፣ ድርጅቶች እንዲሁ መንግሥት ራሱ በሚያደርገው ተሳትፎ የሚደረገው እንቅስቃሴ ብዙም የሚያራምድ እንዳልሆነ በተጨባጭ አሳይቷል። ስለዚህ ፕሮግራሙን በባለቤትነት የሚመራ አንድ አካል እንዲኖረው ማድረግ እንዲሁም ሁሉም ባለድርሻ አካላት የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርጉ የሚያስችል ሥርዓት መዘርጋት የሚያስፈልግ መሆኑን መንግሥት አምኖ እንዲሰራ ያደረገም ነበር።
ይሕ ደግሞ በግል ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ግለሰቦች በተደጋጋሚ ሲያነሱት የነበረውን “ሃገር- አቀፍ የትምህርት ቤቶች ምገባ ፖሊሲ” ወጥቶ ተግባራዊ ይደረግ የሚለውን የተራዘመ ሙግት ተቀባይነት ከማግኘት ባሻገር እውን እንዲሆን መንገድ መክፈቱን ሲናገሩ ተመልክተናል።
መንግሥት ፕሮግራሙ በሃገር አቀፍ ደረጃ ውጤታማ በሆነ መልኩ ተግባራዊ ለማድረግ የነበሩትን ችግሮች ለመፍታት ከሰባት ዓመት በፊት ዝግጅቱ የተጀመረው የምገባ ፖሊሲ ሰነድ እና ማስፈፀሚያ ስትራቴጂን በፍጥነት አጠናቆ አጸድቋል።
ሐምሌ 1 ቀን 2013 ዓ.ም የጸደቀው ይሕ ፖሊሲና ማስፈጸሚያ ስትራቴጂ ፕሮግራሙን በሃገር አቀፍ ደረጃ በስፋት እና በተጠናከረ መልኩ ተግባራዊ ማድረግ በሚያስችል መልኩ እንደተዘጋጀ ከኢ.ፌ.ዲ.ሪ ትምህርት ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።በፖሊሲ ሰነዱ ላይ ፕሮግራሙን በውጤት ለማጀብ የሚያስችሉ ፍሬ ነገሮች በውስጡ መያዙን አስታውቋል።
ፖሊሲና ማስፈፀሚያ ስትራቴጂ በውስጡ ምን ይዟል?
ለመሆኑ ሐምሌ 1ቀን 2013 ዓ.ም ይፋ የተደረገው ፖሊሲና ማስፈፀሚያ ስትራቴጂ በውስጡ ምን ይዟል? የሚል ጥያቄ በማንሳት ምላሹን ከሰነዱ እስቲ እንመልከት። ሃገር- አቀፍ የትምህርት ቤቶች ምገባ ፖሊሲ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ መደረጉ ፕሮግራሙን በተናጥል ሳይሆን በተቀናጀ መልኩ ተግባራዊ የማድረግ አቅም የሚፈጠር መሆኑን የምገባ ፖሊሲ ሰነዱ ያመላከታል።
ይሕን ሁኔታ ሲያብራራው፤ ስለ መርሐ ግብሩ ከአራቱ ተቋማት በተጨማሪ በርካታ ሴክተር መስሪያ ቤቶች የሚመለከታቸው መሆኑን እና ኃላፊነት ይወስዳሉ። ለምሳሌ ገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር፣ የሴቶችና ህጻናት፣ ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር፣የትራንስፖርት ሚኒስቴር በተለያየ መልኩ ድርሻ ይኖራቸዋል። በመሆኑም እያንዳንዱ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት የምገባ ፕሮግራምን ከመተግበር አንጻር ሚና ይኖራቸዋል፤ኃላፊነታቸውን በዝርዝር ተቀምጦ ይገኛል። ስለዚህ ሁሉም አካላት በፖሊሲው በተቀመጠላቸው ኃላፊነትና ተግባራት መሰረት እንዲፈጽሙ የሚደረግይሆናል። የበጀት ምንጩን በተመለከተ ደግሞ የተለያዩ የበጀት ምንጮችን የሚኖሩ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ መንግሥት በዋነኝነት የሚጠቀስ መሆኑንም ሰነዱ ይገልጻል።
መንግሥት የምገባ ፕሮግራሙን በኃላፊነት ወስዶ እንዲሰራ ሃገር አቀፍ የትምህርት ቤቶች ምገባ ፖሊሲ ሆኖ እንዲዘጋጅ አንዱ ገፊ ምክንያት እንደመሆኑ ፤ዋናው የበጀት ምንጩ መንግሥት እንደሆነ ያስቀምጣል።በዚህ መሰረት መንግሥት በሂሳብ መደቦች ውስጥ የትምህርት ቤት ምገባ እንደ አንድ የበጀት ኮድ ተይዞ ማስቀመጥ ይኖርበታል። ዋነኛው የበጀት ምንጩ መንግሥት ይሁን እንጂ፤ ተጨማሪ የበጀት ምንጮች የሚኖሩ መሆኑን ሰነዱ ያብራራል።
“በኢትዮጵያ ውስጥ በርካታ ተማሪዎች ናቸው ያሉት ፤ከቅድመ መደበኛ እስከ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ድረስ እድሜያቸው ደርሷል የሚባሉት ልጆች የሀገሪቱን አንድ ሦስተኛ የህዝብ ብዛት ይሆናሉ ።ይህ ማለት በአሁኑ ወቅት የህዝብ ቁጥሩ 110 ሚሊዮን የሚደርስ ቢሆን ፤34 ሚሊዮን ገደማ የሚገኙት ትምህርትን የሚፈልጉ ልጆች አሉ ።ስለዚህ እነዚህ ሁሉ ተማሪዎች የምገባ መርሐ ግብሩ ተጠቃሚ ለማድረግ በመንግሥት አቅም ብቻ ስለማይቻል ሌሎች አማራጮች ይኖራሉ “ሲል የፖሊሲ ሰነዱ ያስቀምጣል።
በዚህ መሰረት ሁለተኛ የበጀት አማራጭ አጋር አካላት በዚህ ጉዳይ ላይ የሚሳተፍ ሲሆን፤ በሦስተኛ ደረጃ ደግሞ ኮ-ፋይናንሲንግ ስትራቴጂን የፋይናንስ ምንጭ መሆኑን ሰነዱ ይገልጻል። ኮ-ፋይናንሲንግ ሥርዓትን ሲያብራራ፤ይሕ ስትራቴጂ ሴክተር ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶችም ለምገባ ላይ በጀት በጅተው እንዲሳተፍ የሚያደርግ ስርዓት ነው። ሴክተር መስሪያ ቤቶች ለምገባ በጀት ይመድባሉ ሲባል ግን፤ ትምህርት ሚኒስቴር ሦስት ሚሊዮን ተማሪዎችን የሚመግብ ከሆነ አንድ ሚሊዮኑን ሌላኛው ሴክተር የሚል አይደለም።
የምገባ ፕሮግራሙ የሚፈልጋቸውን እንቅስቃሴዎች ለመደገፍ ውስን በጀት በጅተው እንዲሄዱ የሚያደርግ ይሆናል። እነዚህን ዋና ዋና አካላት በማሳተፍ ሂደት ባለው መልኩ በአንድ ጊዜ 20 ሚሊዮን ተማሪዎችን መመገብ ስለማይቻል በሂደት መጀመሪያ ላይ ቅድመ መደበኛ ፣በመቀጠል የመጀመሪያ ደረጃ፣ መካከለኛ ደረጃ እየተባለ የምገባ ፕሮግራሙን እንዲሰፋ የሚደረግ ይሆናል።
ዳንኤል ዘነበ
አዲስ ዘመን ሐምሌ 26/2013