በካናዳና በአሜሪካን ሀገሮች ባልተለመደ ሁኔታ ተከስቶ በነበረው የሙቀት መጨመር በነዋሪዎቹ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ጫና ከማሳደር በተጨማሪ ህይወትን አደጋ ላይ በመጣል ጉዳት ማስከተሉ በተለያየ የመገናኛብዙሃን መዘገቡ ይታወሳል። የሙቀቱን አሳሳቢነት በመግለጽና ዜጎች የሙቀት ወላፈንን መቋቋም እንዲችሉ ወደተዘጋጀላቸው ቀዝቃዛ መጠለያ እንዲዘዋወሩ በማድረግ ጭምር የሰው ልጅን ህይወት የመታደግ ሥራ እየተሰራ ይገኛል።
የአየር ሁኔታ ለውጥ በዓለም ላይ የሚያጋጥመውን እንዲህ አይነቱን እጅግ ከፍተኛ የሙቀት መጠን መከሰት ተደጋጋሚ ሊያደርገው እንደሚችልም ባለሙያዎች መግለፃቸውን በአየር ሁኔታ ለውጡ የተነሳም በጎርፍ፣ በከባድ አውሎ ነፋስ እና በከፍተኛ ሙቀት መጨመር የሰው ህይወት ሊጠፋ እንደሚችልና ብዙ ሰዎችም ተጋላጭ እንደሚሆኑ የመገናኛ ብዙሃኑ መረጃዎች ያመለክታሉ። እንደመረጃው ሰዎች በሀይቅ ዳርቻና ከቤታቸው ውጪ ለማሳለፍ የተገደዱበት አጋጣሚዎችም ተፈጥረዋል። ብዙ ፈሳሽ መውሰድ እንዳለባቸውና አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ምክረ ሀሳብ በመስጠት ጭምር ርብርብ ሲደረግ ቆይቷል።
በአየር ንብረት ለውጥ በአሜሪካና በካናዳ የተከሰተውን ከባድ የሙቀት መጠን መጨመር መነሻ በማድረግ በዓለምና በኢትዮጵያ ስላለው ተጨባጭ ሁኔታ ማብራሪያ እንዲሰጡን በአካባቢ፣የደንና የአየር ንብረት ለውጥ ኮሚሽን የደን ዘርፍ ትራንስፎርሜሽን ዩኒት ክፍል ሰራተኛ እና የአረንጓዴ አሻራ ብሄራዊ ቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ ዶክተር አደፍርስ ወርቁን ጠይቀናቸዋል።
እንደ ዶክተር አደፍርስ ማብራሪያ በዓለም ላይ ያለውን የአየር ለውጥ ነባራዊ ሁኔታ ከአፍሪካ፣ ከኤዢያና ከሌሎችም ሀገራት የተውጣጡ በሺዎች የሚቆጠሩ በጎ ፈቃደኞች ምሁራን ተመራማሪዎች የተሰባሰቡበትና ዓለምአቀፍ ቲንክታንክ በሚል ስያሜ የሚንቀሳቀሱ ቡድኖች የአጭርና የረጅም ጊዜ ጥናቶችን በማካሄድና የተለያዩ መረጃዎች በማሰባሰብ ለዓለምአቀፉ ማህበረሰብና መሪዎች በማቅረብ ሚናቸውን በመወጣት ላይ ይገኛሉ። ዩ ኤን ኤፍ ትሪፕልስ የሚባለውና ስለአየር ንብረት ለውጥ ዋና አጀንዳ አድርጎ በዓለም አቀፍ መድረክ የአየር ንብረት ለውጥ ጉዳይን የሚያስተባብረው ተቋም ምክር የሚያገኘው ከእነዚህ ምሁራን ነው።
በእነዚህ ምሁራን፣ ተመራማሪዎች፣ግለሰቦችና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በጋራና በተናጠል በአየር ንብረት ለውጥ ዙሪያ የሚወጡ መረጃዎች የሚያሳዩት በዓለምአቀፍ ደረጃ የአየር ንብረት ለውጥ እና የሙቀት መጠን መጨመር ነው። በሳይንሱ ዝቅተኛ የሚባለው የሙቀት መጠን ከፍ ካለ ቀዝቃዛው እያነሰ ይሄዳል። ይህ ሲሆን ደግሞ የመሬት ሙቀት ይጨምራል። በነዚህና ሌሎችም ምክንያቶች የሙቀት መጨመር በዓለም ላይ ከፍተኛ ቀውስ እያስከተለ ይገኛል። ሙቀትን ለመከላከል የሚያስችል ሥራ ካልተሰራ ሥጋቱና ቀወሱ ተባብሶ ጉዳቱም እየቀጠለ ይሄዳል። ካናዳ ላይ የተከሰተው ከፍተኛ ሙቀትና ያጋጠመው ቀውስ የመጀመሪያው አይደለም። የአየር ንብረት ለውጥ ሲባል አብሮት የአየር ተለዋዋጭነት ይከሰታል። የአየር ተለዋዋጭነት ወቅታዊ ነው። የዝናብ ሁኔታና ሙቀት ባልተለመደ ሁኔታ ከፍና ዝቅ ሲል ተለዋዋጭ የአየር ፀባይ ተደርጎ ይወሰዳል።
የአየር ንብረት ለውጥ የሚባለው የአየር ንብረት ከሚቆጣጠሩ ሜትዎሮሎጂ ጣቢያዎች መረጃና ከሌሎች ምንጮች መረጃ በመሰብሰብ የሚገኘው ውጤት ነው ። በካናዳና አውሮፓ የታየውና ስጋት እየፈጠረ የመጣው የአየር ንብረት ለውጥ የሙቀት መጠን ድንገት ከፍ ማለት የሰዎችን ህይወት እስከማሳጣት የደረሰ ሆኖ ተገኝቷል።
በአየር ንብረት ለውጥ የተከሰተው ጉዳት አዲስ እንዳልሆነ ይናገራሉ። እርሳቸውም እኤአ 2016 እና 2017 ላይ ጀርመን ሀገር በነበሩበት ወቅት በተመሳሳይ ሁኔታ ችግሩን አይተውታል። ችግሩ ምን ያህል አሳሳቢ እንደሆነ የአይን እማኝ መሆናቸውን ዶክተር አደፍርስ ይጠቅሳሉ። ‹‹በወቅቱም የነበረው ሙቀት ጀርመን በዕድሜዋ ያላየችውን የሙቀት መጠን ያጋጠመ በ50 አመትና ከዚያም በላይ በሆነ ጊዜ ውስጥ ሲያጋጥማት የመጀመሪያው እንደሆነ በወቅቱ ሲነገር መስማታቸውን ያስታውሳሉ።
እንደ ዶክተር አደፍርስ ማብራሪያ፤ የሰዎች ሙቀትን የመቋቋም አቅም ውስን በመሆኑ ከፍተኛ የሆነ ሙቀት ሲያጋጥም ድጋፍና ዕርዳታ ካልተደረገ ችግሩ ህይወት እስከ ማጣት ይደርሳል። የሞት አጋጣሚው በሁሉም የዕድሜ ክልል ላይ የሚፈጠር ቢሆንም በዕድሜ የገፉ፣በመተንፈሻ አካላቸው ላይ የጤና መታወክና ሌሎች ተጓዳኝ የሆኑ የጤና ችግር ያለባቸው የህብረተሰብ ክፍሎች የበለጠ ተጋላጭ ያደርጋቸዋል። የጤና ችግር ያለባቸው የጤና ክትትል ላይ ካልሆኑና ድንገት በቤታቸው ሆነው ከተጋለጡ ችግሩን የከፋ ያደርገዋል። ሙቀት በተከሰተባቸው ሀገራትም እያጋጠመ ያለው ይኸው ነው። በዓለም ላይ እየተከሰተ ያለው የአየር ንብረት ለውጥ በሰው ህይወት ላይ ብቻ ሳይሆን፣በእፅዋቶችና በተለያዩ ልማቶች ላይም ተጽዕኖውን እያሳረፈ ይገኛል። በተለይም ኢትዮጵያን ጨምሮ በአፍሪካ ድርቅ በማስከተል ባደረሰው ተጽዕኖ በምግብ እጥረት ብዙዎች ህይወታቸውን አጥተዋል።
እንዲህ ያሉ ክስተቶች እውነት በአየር ንብረት ለውጥ ነው? ወይንስ ሌላ ተፈጥሮአዊ የሆኑ ምክንያቶች የሚለው በኢትዮጵያ ውስጥ መረጃን መሠረት ባደረገ ምላሽ ለመስጠት ጥረቶች መደረጋቸውን የጠቆሙት ዶክተር አደፍርስ፣የሙቀት መጠን ከፍ እያለ፣የዝናቡ ሁኔታ ደግሞ ተለዋዋጭነቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሆኑ ተረጋግጧል። ለአብነትም በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ግንቦት ወር የፀሐይ ወር ነው። ፀሐዩ ሐምሌና ነሐሴ ላይ ለሚከናወነው የግብርና ሥራ በጣም አስፈላጊና ለአዝመራው ምቹ ነው። የኢትዮጵያ የግብርና ሥራ የተቃኘው በነዚህ ወራቶች ነው። ገበሬው ግንቦት ወር ላይ መሬቱን ይገለብጣል። የዚህ ጥቅሙ በወቅቱ ያለው የአየር ፀባይ በሰብል ውስጥ የሚፈጠሩ አረሞች ይገላቸዋል። በፀሐይ ሐይል የአረም ሥር ስለሚደርቅ የአረም ሥራን ያቃልላል። በመሆኑም ሐምሌ ወር ላይ ሳይቸገር ዘር ይዘራል። ለአረም ማጥፊያ ኬሚካል አይጠቀምም። ለግዥ የሚያወጣው ወጪም ይቀንስለታል። ቀደም ሲል በዚህ መልኩ ይከናወን የነበረው የግብርና ሥራ አሁን ላይ እየሆነ አይደለም። ምክንያቱም የግንቦት ወር የክረምት መጀመሪያ ወይም የዝናብ ወቅት እየሆነ መምጣቱ ነው። የግብርናውን ሥራ በከፍተኛ ሁኔታ እያዛባው መምጣቱ በምርትና ምርታማነት መጨመር ላይ ተጽዕኖ እያሳደረ ነው። በአንዳንድ የሀገሪቱ አካባቢዎች የዝናብ መለዋወጥና የሙቀት መጠን መጨመር፣የዝናብ መጠን መቀነስ እየተስተዋለ ነው። በተለይም የበልግ አምራች በሆኑ አካባቢዎች ወቅቱን ጠብቆ ዝናብ ካልዘነበ ምርት አይኖርም። ከመኸር የምርት ጊዜ በተሻለ በበልግ ወቅት የሚያመርቱ አካባቢዎች ወቅታዊ ዝናብ ባለማግኘታቸው አለማምረታቸው ለድርቅ ሊያጋልጣቸው ይችላል።
እነዚህ ምልክቶች አደጋቸው እየከፋ ሳይሄድ ከወዲሁ መሰራት ያለባቸው ሥራዎች እንዲሰሩ ትኩረት ተሰጥቶ መከናወን ይኖርበታል። የአየር ንብረት ለውጥን ማዕከል ያደረገ ሥራም ተጀምሮ በመጠናከር ላይ ሲሆን፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐብይ ተነሳሽነት በቁርጠኝነት እየተከናወነና የህዝብ ንቅናቄን የፈጠረው አረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ይጠቀሳል። በዚህ መልኩ ከተጠናከረ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ተጋላጭነቷን መቀነስ ይቻላል። ለዓለምአቀፉ ማህበረሰብም የሚደረገው አስተዋጽኦ ከፍ ይላል።
ለአየር ንብረት ለውጥ ተጋላጭነት ለመቀነስ እስካሁን በተሰሩት ሥራዎች የተገኙ መልካም ጎኖች እንዴት ይታያሉ ለሚለው ጥያቄ ዶክተር አደፍርስ በሰጡት ምላሽ፤ጉዳዩ በሁለት መልኩ ሊታይ ይችላል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ከመቀነስ አንጻር ከፍተኛ የሚባል ዕቅድ ነድፋ በመንቀሳቀስ ላይ ትገኛለች። እኤአ 2011 ላይ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር በአንድ በኩል፣በሌላ በኩል ደግሞ አረንጓዴ ኢኮኖሚ የሚል ሰነድ የያዘ ለዓለም ማህበረሰብ ያስተዋወቀች ጊዜ በዓለም ማህበረሰቡ ላይ የፈጠረችው ተጽዕኖ በቀላል የሚታይ አልነበረም።
ኢትዮጵያ ብክለትን በማስከተል ከሌሎች ሀገራት አንጻር እጅግ ያናሰ ነው። ይልቁንም ሌሎች ሀገራት በሚያስከትሉት ብክለት ተጎጂ ናት። ሆኖም ግን ተጎጂ ነኝ ሳትል ብክለቱን ለሚያመነጩትም በብክለቱ ተጎጂ ለሆኑ ሀገራትም መፍትሄ ይሆናል ብላ የነደፈችውን የዕቅድ ሀሳብ ይዛ በዓለም አቀፉ መድረክ ያቀረበችው በከፍተኛ ሁኔታ ተቀባይነትን አስገኝቶላታል። የዕቅድ ሀሳቡ በወረቀት ላይ ብቻ የቀረ ሳይሆኑ፣ መሬት ላይም ወርዶ እንዲተገበር ጥረት ተደርጓል። ለአብነትም ለአየር ንብረት ለውጥ ተብለው ከተለዩት ምሶሶዎች ዘላቂ የደን ልማት አንዱ ነው። አረንጓዴ አሻራም መርሃግብርም የዚሁ አካል ነው። በዚህ እንቅስቃሴ ኢትዮጵያ ያላትን ደን በመጠበቅ፣ የደን ምንጣሮንና ጭፍጨፋን በመቀነስ፣ደን ከጉዳት በመከላከሉና በልማቱም የማህበረሰቡን ግንዛቤ ከፍ የሚያደርግ ሥራዎች በመሰራታቸው የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ ተችሏል። ይህ ሥራ መሰራቱ እምቅ ካርበን ይዞ ለመቆየት ይረዳል። ጎን ለጎን ደን እና ተፋሰስ እንዲለማ ማህበረሰቡን በማሳተፍ ኢትዮጵያ ከፍተኛ በሚባል ደረጃ የአየር ስትራቴጂ ለውጥ ነው የምትገኘው።
በዚህ መልኩ ሥራዎች ቢቀጥሉም ውጤቱ ደግሞ በሂደት የሚጠበቅ ይሆናል። በተለይም ዘላቂ የሆነ ዓለማቀፋዊ ለውጥ ለማምጣት የተጠናከረ ሥራ ይጠበቃል። ዛሬ የሚተከሉ የዛፍ ችግኞች እንደችግኞቹ በውስጣቸው የካርበን መጠን አላቸው። ነገር ግን እያደጉ ሲሄዱ ብዙ ቅርንጫፍና ቅጠል በያዙ ቁጥር በውስጣቸው የሚይዙት የካርበን መጠን እየሰፋ ይሄዳል። አሁን ጀምረነዋል። ይሄ ሥራ ተጠናክሮ መላው ኢትዮጵያ በደን ሲሸፈን በካይ የሆኑ ጋዞችን በአትሞስፌር ውስጥ ለማመቅ ወይንም ለመያዝ ያስችላል።
በሌላ በኩል ደግሞ የተፋሰስ ልማቱን በማሳለጥ በወንዞች ውስጥ በቂ ውሃ ለመያዝ ያስችላል። ኢትዮጵያ ውስጥ በቂ ዝናብ ሲኖር በጅረቶች ውስጥም በቂ ውሃ ሲፈስ፣ ከአየር ንብረት ለውጥ ባሻገር በቂ ውሃ ወደ ጎረቤት ሀገሮች ለመላክ ይረዳል።
‹‹የኢትዮጵያን የደን ልማት ከአየር ንብረት ለውጥ ባሻገር ልናየው ይገባል የምንለው ከእኛ ውሃ የሚጠብቁ ጎረቤት ሀገራት አሉ። ከኢትዮጵያ ወደ ጎረቤት ሀገራት የማይሄድ ውሃ የለም። ወደ ሶማሌ፣ ኬኒያ፣ ሱዳን፣ ኤርትራና ሌሎች ሀገሮች በተፈጥሮ ውሃ ይፈሳል። በተፈጥሮ ውሃ የማይሄድባት ጅቡቲ እንኳን በሰው ሰራሽ ውሃ ወደ ሀገሪቱ እንዲሄድ እየተደረገ ነው። ኢትዮጵያ ለታችኛው ተፋሰስ ሀገራት በቂ ውሃ መላክ እንድትችል የኢትዮጵያ ተራሮች በደን መሸፈን ይኖርባቸዋል። ደን ሲለማ የጎረቤት ሀገሮችንም ተጠቃሚነት ታሳቢ ያደረገ መሆኑ መዘንጋት የለበትም። ዓለምም የካርበን ልቀትን በመከላከል ተጠቃሚ ያደርጋል። የደን ውጤቶችን በመሸጥ ገቢ ይገኛል። በደን ልማቱ ምርትና ምርታማነት ይጨምራል። በዚህ መልኩ የኢኮኖሚ አቅም ሲፈጠር ኑሮውን ለመቀየር ሲል ወደተለያዩ ሀገራት የሚሰደደውን ዜጋ ማስቀረት ያስችላል። ከአቅማቸው በላይ ስደተኞችን በመቀበል ለተቸገሩና ስደትን እንደትልቅ አደጋ ለሚያዩ ሀገራትም ጫና ለመቀነስ አስተዋጽኦ ይኖረዋል።
ኢትዮጵያ የ10 አመት ዘላቂ የደን ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ስትራተጂ ነድፋ በመንቀሳቀስ ላይ መሆኗን የጠቆሙት ዶክተር አደፍርስ፤ ስትራተጂውን በሰው ኃይልና በገንዘብ አቅም የተደራጀና የፖለቲካም ጭምር ድጋፍ ያለው ጠንካራ ተቋም በማቋቋምና መሬት የወረደ ሥራ ሲሰራ ውጤቱም ያማረ ይሆናል። በዚህ ረገድ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐብይ አሕመድ የደን ልማት ሥራውን አጀንዳ እንዲሆን ማድረጋቸው ትልቅ ተስፋ ይሰጣል። በወረቀት ላይ የሰፈረው ዕቅድም በተግባር ላይ ውሎ ለመታየት ይበቃል።
የደን ልማቱ በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ እየተከተለችው ካለው የኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ ጋር የተናበበ ሊሆን እንደሚገባ ዶክተር አደፍርስ ይናገራሉ። በጋራ ቢሰራ የተሰሩ ልማቶች ሳይፈርሱ ባነሰ ወጪ ውጤታማ ማድረግ ይቻላል። በተለይ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና የአየር ንብረት ለውጥን የተመለከቱ ሥራዎች ከአንድ ተቋም የዘለለ ሥራ ነው። ደን በማልማት በካይ ጋዞችን እንቀንሳለን ስንል ኢንደስትሪው ደግሞ በካይ የሆኑ ኬሚካሎችን ወደ አፈርና ወንዝ ውስጥ የሚጨምሩ ከሆነ ድምሩ ዜሮ ነው ። ይሄ እንዳይሆን በጋራ ተነጋግሮ መንቀሳቀስ ግድ ይላል። የዘርፍ ተቋማት ሁሉም በጋራ የሚሰሩበት አደረጃጀት ተፈጥሯል። ይሁን እንጂ አሁንም አደረጃጀት የመፍጠር ችግር ሳይሆን ተግባራዊ ማድረግ ነው። በጋራ ሲሰራ የተለያየ ዕውቀት፣አቅም፣የገንዘብ ስብስብ ይገኛል። ችግርም ጥቅምም የጋራ በመሆኑ ይሄን ተገንዝቦ ጠቃሚ በሆነው ነገር ላይ በጋራ መረባረብ ያስፈልጋል። ብክለትን ኢንዱስትሪዎች ብቻ ሳይሆኑ ግለሰቦችም የተጠቀሙባቸውን የፕላስቲክ የውሀ መያዣና ሌሎች በካይ ቆሻሻዎች በአግባቡ በማስወገድ ብክለትን በመከላከል ኃላፊነታቸውን ሊወጡ እንደሚገባም ነው ያስገነዘቡት።
ለምለም መንግሥቱ
አዲስ ዘመን ሐምሌ 15/2013