የዛሬው የጠይቁልኝ አምድ ርዕሰ ጉዳያችን የጥሞና ጊዜን ይመለከታል። አቶ አበበ አድማሱ የተባሉ የአዲስ ዘመን ጋዜጣ አንባቢ ስለጥሞና ጊዜ ምንነትና በዚህ ወቅትም ስለሚተገበሩና ስለሚከለከሉ ተግባራት ዝርዝር መረጃ እንድንሰጣቸው ባቀረቡልን ጥያቄ መሰረት የተለያዩ ሰነዶችንና ከምርጫ ቦርድ የተገኙ መረጃዎችን ዋቢ በማድረግ እንደሚከተለው ለንባብ አብቅተነዋል።
ብሄራዊ የምርጫ ቦርድ ከትላንት ጀምሮ ያሉት ቀጣይ 4 ቀናት የጥሞና ወቅት እንደሆኑ አሳውቋል። በዚህም የተነሳ የፖለቲካ ፓርቲዎችም ሆኑ መገናኛ ብዙሃን በነዚህ 4 ቀናት ውስጥ የተለመደውን አይነት ቅስቀሳ ማድረግ እንደማይችሉ አሳውቋል። ቦርዱ እንዳለው ከሆነ የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ እጩዎቻቸውና ደጋፊዎቻቸው ቦርዱ በሚያወጣው መመሪያ መሠረት የሚያካሂዱት የምርጫ ውድድር እንቅስቃሴ ድምጽ መስጠት ከመጀመሩ ከአራት ቀን በፊት መጠናቀቅ አለበት። በዚህም መሰረት የፖለቲካ ፓርቲዎች ምርጫው አራት ቀን ሲቀረው ማንኛውም አይነት የምርጫ ቅስቀሳ ማድረግ አይፈቀድላቸውም። ይህም ማለት በኢንተርኔት፣ በማህበራዊ ሚዲያ፣ በግንባር፣ ቤት ለቤት፣ በአደባባይ ፣ በአዳራሽ ስብሰባ ምንም አይነት ቅስቀሳ ማከናወን በጥብቅ የተከለከለ ነው። ፓርቲዎች በምርጫ ጉዳዮች ዙሪያ አስተያየት መስጠት እንዲሁም ቃለ-መጠይቆችን ማድረግም አይፈቀድላቸውም። መገናኛ ብዙሀንን በተመለከተም ቦርዱ ባስተላለፈው መመሪያ የመገናኛ ብዙሀን ተቋማት በጥሞና ወቅት ማንኛውንም ምርጫ ተኮር እንቅስቃሴዎችን ማሰራጨት አይፈቀድላቸውም። በተጨማሪም የፖለቲካ ፓርቲ እጩዎችን አግኝተው ቃለ መጠይቆችን መስራት አይፈቀድላቸውም ብሏል።
ይህ አይነቱ የምርጫ ልማድ በምርጫ ወቅት የተለመደ ሲሆን በሌሎች ሀገራትም በስፋት ይተገበራል። ለምሳሌ ያህል ፈረንሳይ ከምርጫው ቀን ጥቂት ስአታት ቀደም ብሎ የምርጫው ውጤት በይፋ እስኪገለጽ ድረስ ምንም አይነት ቅስቀሳ ማድረግ የከለከለች ሲሆን የምርጫ ውጤትን ቀድሞ መተንበይም ሆነ መዘገብም የተከለከለ ነው። ለምሳሌ ያህል በ2017ቱ የፈረንሳይ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ወቅት በነዚህ ሰአታት ስለ ምርጫው ውጤት ትንታኔ መስጠት፤ ዳሰሳ መስራት፤ ቅድመ ትንበያ ማስቀመጥ፤ ግምት መገመት እና መሰል ተግባራት በየትኛውም ሚዲያ የተከለከሉ ነበሩ። ከምርጫው በኋላም የመጨረሻው የምርጫ ጣቢያ ውጤት እስኪታወቅ ድረስ ስለ ምርጫው ውጤት መዘገብ ክልክል ነበር። ተመሳሳይ ህጎች በበርካታ ሀገራት የሚተገበር ሲሆን የጥሞና ጊዜው ርዝማኔ እንደየሀገሩ ይለያያል። እንደ ሩሲያ፤ ቡልጋሪያ፤ ክሮሺያ፤ ፖላንድ እና ሌሎች በርካታ ሀገራት ከምርጫው ቀን 24 ሰአት ቀደም ብሎ የሚጀምር ሲሆን በህንድ ደግሞ 48 ሰአት የጥሞና ጊዜ አለ።
ይሁንና ይህን ህግ በተለይ በማህበራዊ ሚዲያዎች ለማስተግበር አስቸጋሪ ሆኖ ተገኝቷል። የማህበራዊ ሚዲያው ባህሪ ብዙውን ጊዜ ግለሰባዊ መሆኑ እና በሚሊየን የሚቆጠሩ ሰዎች በየግላቸው የየራሳቸውን የማህበራዊ ሚዲያ ስለሚጠቀሙ ትግበራውን ከባድ አድርጎታል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ዩሮባሮሜትር በ2018 እ.ኤ.አ እንግሊዝ ውስጥ ባደረገው የዳሰሳ ጥናት 75 በመቶ እንግሊዛውያን በመደበኛ መገናኛ ብዙህን ላይ የሚተገበረው የጥሞና ጊዜ በማህበራዊ ሚዲያ ላይም ተፈጻሚ እንዲሆን ፍላጎት እንዳላቸው አሳውቀዋል። በእርግጥም ማህበራዊ ሚዲያ በምርጫዎች ላይ እየፈጠረ ካለው ጫና አንጻር ቁጥጥሩ አስፈላጊ ይመስላል። ለምሳሌ ያህል ባለፈው አመት ከተደረገው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ጋር በተያያዘ ፌስቡክ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሀሰተኛ መረጃዎችን በምርጫው ሰሞን ከገጹ ላይ ማስወገዱን መስራቹ እና ባለቤቱ ማርክ ዙከርበርግ አሳውቆ ነበር። ይህም በ2016 እ.ኤ.አ በተካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ወቅት የውጭ ሀይሎች የአሜሪካንን ምርጫ ውጤት ለማወክ ፌስቡክን ተጠቅመዋል በሚል ድርጅቱ ከደረሰበት ከፍተኛ ነቀፋ በኋላ የተወሰደ ማስተካከያ ነበር።
የሆነ ሆኖ ይህ የጥሞና ጊዜ ፋይዳው ምንድን ነው የሚለውን ስንመለከት ፋይዳው ከፍተኛ ሆኖ እናገኘዋለን። ከጠቀሜታዎቹ ዋነኛው ለመራጮች ማሰቢያ ጊዜ መስጠቱ ነው። ምርጫ ካለ መራጮች ሊመርጧቸው የሚገቡ ቢያንስ ሁለት ነገሮች አሉ። እንደ ኢትዮጵያ ባሉ የመድብለ ፓርቲ ስርአት ባለባቸው ሀገራት ደግሞ ከሁለት በላይ አማራጮች ለመራጮች ቀርበዋል። ስለዚህም መራጮች ከቀረቡላቸው አማራጮች አንዱን ለመምረጥ ማሰላሰል ይጠበቅባቸዋል። በተለይም በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ተፎካካሪ ፓርቲዎች በብዙ ጉዳዮች ላይ ብዙ አይነት አማራጭ ምክረ ሀሳቦችን ከማቅረባቸው የተነሳ መራጮች ያለምንም ግራ መጋባት ይሆነኛል የሚሉትን እንዲመርጡ ማሰላሰያ ጊዜ ያስፈልጋቸዋልና የጽሞና ጊዜው ወሳኝ ነው።
ሌላኛው የጽሙና ጊዜ ጠቀሜታ በምርጫ ሰሞን የሚሰራጩ ሀሰተኛ መረጃዎችን መግታት ነው። ይህ በሁለት መልኩ ሊታይ የሚችል ነው። በአንድ ጎን ተወዳዳሪዎች አንዳቸው በሌላቸው ላይ የሚሰነዝሩት የስም ማጥፋት እና መራጮችን በመጨረሻ ሰአት ሀሳብ ለማስቀየር የሚለቋቸው ማስታወቂያዎች እና መረጃዎችን መግታት ነው። በሌላ መልኩ ደግሞ ባላንጣ ሀገራት የምርጫ ሂደቶችን ለማወክ እና መራጮች በምርጫው ላይ እምነት እንዳይኖራቸው ለማድረግ የምርጫውን ሰሞን ታክከው በመደበኛ መገናኛ ብዙሀንም ሆነ በማህበራዊ ሚዲያ የሚያሰራጯቸው መረጃዎችን ለመግታት የጥሞና ጊዜ አስፈላጊ ነው።
በሶስተኛ ደረጃ የጽሞና ጊዜ በምርጫው የመጨረሻ ቀናት ሊፈጠሩ የሚችሉ ቅድመ ምርጫም ይሁን ድህረ ምርጫ ሁከቶች ለማቀዝቀዝ እና ለመቆጣጠር እድል ይሰጣል። ምርጫ በባህሪው ሁለት እና ከዚያ በላይ የሆኑ ተቃራኒ ሀሳቦች እና ርእዮች |የሚቀርቡበት መድረክ እንደመሆኑ መጠን ዜጎች በዚያ ሰሞን ወደ ጽንፍ የሚሳቡበት እና ዋልታ ረገጥነት ጫፍ የሚደርስበት ሰሞን ሊሆን ይችላል። ይህም ሰዎችን ስሜታዊ የማድረግ አቅም አለው። ይህም በምርጫው ሰሞን ሰዎች ወደ አካላዊ ግጭት ሊገቡበት የሚችሉበትን እድል ያሰፋዋል። ታዲያ በዚህን ጊዜ ፓርቲዎች ሰላማዊ ሰልፍ ቢጠሩ ወይም በመገናኛ ብዙሀን ቀርበው ስሜት ቆስቋሽ ንግግር ቢናገሩ አልያም በማህበራዊ ሚዲያ ብቅ ብለው መልእክት ቢያስተላልፉ ተጽእኖው ቀላል አይሆንም። ስለዚህም ሲግል የከረመውን ስሜት ለማብረድ እና መራጮች በተረጋጋ እና በጠራ አእምሮ ወደ ምርጫው ቀን እንዲደርሱ ለማድረግ ይህ በቅስቀሳው እና በምርጫው መሀከል ያለው የጥሞና ጊዜ ወሳኝ ነው።
በመጨረሻም የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ያስተላለፉት መልእክት ከሁሉም በላይ የዘንድሮውን 6ኛው ብሄራዊ ምርጫ በጥሩ መልኩ የሚገልጽ ነው እና እሱን ብለን እንውጣ። ሰብሳቢዋ በማህበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባስተላለፉት መልእክት ተፎካካሪ ፓርቲዎችን በሚከተለው መልኩ አመስግነዋል። ”ብዙ ጥላቻን ባንፀባረቀ አልተወዳደራችሁም፤ በአደባባይ ዘለፈኝ፥ ስሜን አጠፋ አልተባባላችሁም፤ ወይም እኔ አገልጋያችሁ አልሰማሁም። እንደ አምና ካችአምናው ይቅርታ ካልጠየቀኝ ሞቼ እገኛለሁ፥ ከሱ ጋር ሁለተኛ አልቆምም ያለም የለም። ለመልካም ፉክክራችሁ ምስጋናዬ ብዙ ነው፤ ቀጣዮቹ የፅሞና ቀናት የበጎነት እና የመልካምነት ጊዜ እንዲሆንላችሁ ስል ይቺን የልቤን መቃተት ላካፍላችሁ ወደደድኩ። ለሞከርናት ትንሽ የጋራ ሙከራ የጎን ውጋት ሆናችሁ ለከረማችሁትም ጭምር፤” ብለዋል ሰብሳቢዋ። የወ/ሪት ብርቱካን መልእክት የእስካሁኑ የምርጫው ሂደት እስከዛሬ ከነበሩት ምርጫዎች ሁሉ ሰላማዊ እንደሆነ የሚያመለክት ሲሆን ከጥሞናው ወቅትም በፊት ሂደቱ እርጋታ እንደነበረው አመላካች ነው። በዚህ እርጋታ ላይ ደግሞ ቀጣዮቹ የጽሞና ቀናት ሲደመሩ ደግሞ ኢትዮጵያ ባልተለመደ መልኩ በሰላም ወደ ምርጫ ደርሳ በሰላም ልትሻገር እንደሆነ ምልክት ነውና ለሰላም ወዳድ ኢትዮጵያውያን ትልቅ እፎይታን ይሰጣል።
በዚህ ገፅ ላይ አንባቢያን በሚፈልጉት ጉዳይ ላይ ጥያቄ የሚያቀርቡበት እና እኛም የሚመለከተውን አካል መልስ ጠይቀን የምናስነ ብብበት ሲሆን፤ ማንኛውም ሰው በስልክ ቁጥር 0111264326 በመደወል ጥያቄ እና አስተያየት ማቅረብ ይቻላል።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ሰኔ 11/2013