በኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ግቢ ውስጥ ቡናና ሻይ በማቅረብ ትታወቃለቸ። በጣም ቀልጣፋና ፈገግታ ከፊቷ የማይለያት ወጣት ናት። ማልዳ ከድርጅቱ ሰራተኞች ቀድማ በመገኘት ለመስተንግዶ የሚሆናትን ሻይ ቡና ለማደረስ ጠደፍ ጠደፍ ትላለች። በማንኛውም ሰአት ስትጠራ በአንድ እጇ ዘንቢሏን በሌላው ብርጭቆ የደረደረችበትን ሳህን ይዛ ከተፍ ስትል ከንፋስ ጋር ውድድር የገጠመች ትመስላለች።
ጥንካሬና ትጋቷ ከአመት አመት የማይቀንስ አይከፋሽ የምትባል አይነት ወጣት ነች። ጣአሙ የማይቀየረው ቆንጆ ቡናና ሻይዋ ደንበኞቿ እንዳይርቋት ቢያደርግም ለትኩስ ነገር ማዘጋጃ የሚሆነው ግብአት መጨመሩ እዚህ ግባ የማይባል ትርፍ እንድታገኝ አድርጓታል። በተለይም ስኳር እንደልብ አለመገኘቱ ትርፉ ልፋት እንዲሆን እንዳደረገው ትናገራለች። ነገር ግን በዚህ ሁሉ ውስጥ ፈገግታዋ አይቀንሰም።
ከዚህ ፍልቅልቅ ፊት ጀርባ ምን እዳለ ማንም ሰው አያውቅም። ኑሮ እንዳልሞላላት ፊቷ ላይ ቢታይም ማንም ግን ማነሽ? እንዴት ነሽ? ብሏት አያውቅም። ሙሉ ህንፃውን ከላይ እስከታች እያዳረሰች አገልግሎት ብትሰጥም ከተወዳጁ ቡናና ሻይዋ ውጪ የአለምን ማንነት ቀርቦ የጠየቃት የለም። የ28 አመት ወጣት ናት የአለም ዘርፈ ካሳሁን ትባላለች። ጎጃም ፍኖተ ሰላም አከባቢ ነው የተወለደችው። የኢትዮዽያ ፕሬስ ድርጅትን ደጃፍ የእንጀራ ቤቴ ብላ ሙጥኝ ካለች ስምንት አመታትን አስቆጥራለች። ለዚህ ሳምንት የሴቶቸ ገፅ እንግዳ እንድትሆን ጠየኳት። ከትንሽ ማንገራር በኋላ ነበር በሀሳቤ የተስማማችው።
̋አለም እስቲ ስለ ራስሽ አጫውችኝ” ካልኳት ሰአት ጀምሮ ፈገግታዋ ከፊቷ ላይ መጥፋቱን ተመልክቻለሁ። በፈገግታ የተሸፈነ ቁስል ስለመኖሩ ለመረዳት ነጋሪ አላስፈለገኝም ነበር። ̋አለም? ምነው ዝም አልሽ? ይቅር እንዴ?” አልኳት ̋አይ ቆይ” ብላ ትንሽ ከተረጋጋች በኋላ ነበር ወጋችንን የጀመርነው።
”በጎጃም ፍኖተ ሰላም ነበር ከ28 አመት በፊት የተወለደኩት፤ የተወለድኩበትን ቀን በትክክል አላውቀውም ነገር ግን የትምህርት ቤት ካርዴን አይቼ ነው እድሜዬን የምንግርሽ” አለችኝ። ለቤተሰቦቿ የመጀመሪያ ልጅ እንደሆነች የምትናገረው አለም ሶስት ታናናሽ እህትና ወንድሞች አሏት። አርሶ አደር ቤተሰቦቿ የትምህርት ጥቅምን ያወቁ ነበሩና ማልደው ነበር በማነኩሳ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ያስገቧት። በማንኩሳ እስከ ስምንተኛ ክፍል የተማረችው አለም በአጥጋቢ ውጤት ወደ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አለፈች። ለሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ከተወለደችባት መንደር ወጣ ማለት ግድ ሆኖባት እንደ ነበረ ትናገራለች።
ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ለመማር ፍኖተ ሰላም ከተማ መሄድን የግድ ያላት ይች ወጣት ዘጠነኛና አስረኛ ክፍልን በከተማይቱ ተማረች። በኋላ አስረኛ ክፍል ላይ ሁለት ነጥብ በማምጣት በአካባቢው በሚገኝ አንድ የጤና ሳይንስ ኮሌጅ የግል ኮሌጅ ትምህርቷን ትጀምራለች። የክሊኒካል ነርስ ተማሪ የሆነችው ልጅ ገና በማለዳ ተምራ የመለወጥ ጉጉት ያደረባት ስለነበር በመጀመሪያ አመት የኮሌጅ ትምህርቷ ውጤታማ እንደነበረች ታስታውሳለች።
̋ሁልጊዜ ተምሬ የራሴንም ሆነ የቤተሰቤን ህይወት መቀየር ነበር ትልቁ ህልሜ። ̋ የምትለው ወጣት በግብርና የሚተዳደሩት ቤተሰቦቿ እሷን ከፍሎ ለማስተማር እጅ ሲያጥራቸውና ሲቸገሩ ትመለከታለች። ቶሎ ደርሳ የወላጆቿ ተስፋ ለመሆን ፅኑ ፍላጎት ነበራት፤ የእነሱን ሸክም ሊያቃልል የሚችል ሀሳብ በውስጧ ሰንቃ የነበረችው አለም አንድ የአክስቷ ልጅ አንቺ በጉልበትሽ እኔ በገንዘቤ እንጣመርና ምግብ ቤት ከፍተን እንስራ፤ እዛ እየሰራሽ ትማሪያለሽ የሚል ሀሳብ ታቀርብላታለች። ይህን ሀሳብ ተቀብሏ ወላጆቿን ሳታስቸግር የመማር ተስፋ ሰንቃ ወደ ጅጅጋ ታቀናለች።
ከዛ በኋላ በጅጅጋ የምግብ ቤት ስራውን አጣደፉት። ሲሳካና ውጤታማ መሆን ሲጀምሩ ባለገንዘቧ የአክስቷ ልጅ እሷን ወደ ጎን ገሸሽ በማድረግ የተወሰነ ገንዘብ ሰጥታ ትሸኛታለች። የያዘቻትን ይዛ ወደ ቤቷ ስትመለስ ወይ ከትምህርቷ አልሆነች ወይም ገንዘብ አልያዘች ግራ በተጋባ መንፈስ ውስጥ አንዱን ስታወጣ አንዱን ስታወርድ ለህመም ትዳረጋለች። በዚህ ጭንቀት መካከል ሆና ለመረጋጋት በማሰብ ወደ አንድ ገዳም ሄደች።
̋ወደ ፍኖተ ሰላም ስመለስ ጓደኞቼ የሶስተኛ አመት ተማሪ ሆነው ነበር፤ እኔ ወደ ኋላ መቅረቴ ሲያንገበግበኝ ሳዝን ታመምኩ፤ ከቤተሰቦቼ ጋር መቆየት አልቻልኩም ነበር” የምትለው አለም የገዳም ቆይታዋን ካጠናቀቀች በኋላ ወደ አደስ አበበ መጣች።
እንደመጣች ያረፈችው አጎቷ ቤት ነበር። አጎቷ ቤት ተጠግታ ስትኖር የማይከፈላት የቤት ሰራተኛ እንደነበረች ታስታውሳለች። ̋ ከማለዳ እስከ ምሽት ደፋ ቀና ስል ነበር የምውለው፤ ያኔ የአጎቴ ሚስት አስተምርሻለሁ ብላኝ ስለነበር ለትምህርቴ ስል ሁሉንም ለመቻል ቆርጬ ስለነበር ጥርሴን ነክሼ ነበር የምሰራው” የምትለው ወጣቷ ቃል የተገባላት ትምህርት ግን ሳይጀመር ወራት ወራትን ወለዱ፤ ካልተማርኩ ምን አደርጋለሁ በማለት ከአጎቷ ቤት ትወጣና በሶስት መቶ ሃምሳ ብር አንዲት አነስተኛ ቤት ተከራይታ የቀን ስራ ትፈልግ ጀመር።
ግንባታ ባለባቸው አካባቢዎች እየተዘዋወረች ስራ ስትጠይቅ በወቅቱ ባልደራስ ኮንዶሚኒየም እየተሰራ ስለነበር በአንድ ሺ ብር ደሞዝ እስቶር ኪፐር ሆና ተቀጠረች፤ ለስራ ደከመኝ ሰለቸኝ የማታውቀው ወጣት ትንሽ ሰርቼ ገንዘብ ከያዝኩ በኋላ እማራለሁ በሚል ተስፋ ስራዋን በስነ ምግባር ታከናውናለች። ስራዋን ለመስራት የምትታትረውን ወጣት ግን አሰሪዋ በክፉ አይኑ ተመለከታት። ለስራ ዋስትናዋ የፆታ ጥያቄ ቀረበላት። አላማዋ ትምህርት እንጂ ተራ ፍላጎት ያልነበረው አለም ስራዋን ለቃ ሌላ ቦታ መፈለግ ጀመረች።
ከዛ ሽሮሜዳ አካባቢ የሚገኘው ጴጥሮስ ወፓውሎስ ሆስፒታል የማስፋፊያ ግንባታ ነበረውና እዛም ስራ አግኝታ በተመሳሳይ ሁኔታ መስራት ጀመረች። አሁንም ተደላደልኩ ብላ ሳትጨርስ የተለመደው ጥያቄ ቀርቦ ከስራዋ ያፈናቅላታል። ክፉ እድሏን እያማረረች በተቀመጠችበት አንድ ጓደኛዋ እንዲህ ከሰው ጋር ከምትጣይ የራስሽ አለቃ ሆነሽ ሻይ ቡና ለምን አትሰሪም የሚል ሀሳብ ታነሳላታለች።
አለም እንዴት ልትሰራ እንደምትችል በማብሰልሰል ግራ በተጋባችበት ወቅት የቤት አከራይዋና ጓደኛዋ እቃ ገዝተው ስራ እንድትጀምር አመቻቹላት። ሰማይ የተደፋባት መስሏት የነበረው አለም ትንሽ የተስፋ ጭላንጭል በመመልከቷ ደግ ልቦች ያላቸው ሰዎች ይበርክቱልኝ አያለችም የእለት ጉርሷን የምታገኝባትን ስራ በማለዳ ከድርጅቱ መጥተው ጋዜጣ ለሚረከቡ ሰዎች ሻይ በማቅረብ አንድ ብላ ጀመረች።
̋ምንም መነሻ ካፒታል የምለው ሳይኖረኝ የተገዛልኝን እቃ ይዤ ጉልበቴን ብቻ ተማምኜ ልሰራ ያሰብኩት ስራ ከእለት ጉርሴና ከቤት ኪራይ አልፎ እንድማር አላደረገኚም።” የምትለው አለም ትምህርት እየናፈቃት ከዛሬ ነገ ተለውጬ ጥሩ ህይወት እመራለሁ በሚል ተስፋ ህይወት በመራቻት መንገድ ላይ እያዘገመች ትገኛለች።
ወደ ትውልድ ሀገሯ እንዳትመለስ ጓደኞቿ ትምህርታቸውን ጨርሰው ወደ ስራ መሰመራታቸው በቁጭት እንድትንገበገብ አድርጓታል፤ በሷ እድሜ ያሉ ሴቶች ለመማር ጠደፍ ጠድፍ ሲሉ መመልከት ሰቀቀን ሆኖባት የአርባ ቀን እድሏን እየረገመች መሸሸጊያ ያለችው ስራዋ ውስጥ ራሷን ደብቃ ትኖራለች።
̋ስራ ሳይኖር ቀርቶ ቤት የምውልባቸው ቀናት ለእኔ የመከራ ቀናት ናቸው” የምትለው አለም በእረፍት ቀኗ አጣሁት የምትለውን በማሰብና በመቆጨት እንደምታሳልፍ ትናገራለች።
̋መማር በጣም እፈልጋለሁ፤ በየእለቱ እየጨመረ ያለው ኑሮ፤ የቤት ኪራይ በየቀኑ ይጨምራል፤ እድሜ ቆሞ አይጠብቅም፤ ትምህርት እንደ ምግብ እየራበኝ እንደ ውሃ እየጠማኝ እንደ ሰማይ ርቆኝ ተቀምጫለሁ፤ በህይወቴ በጣም የምመኘው ነገር የተሻለ አገኝ ብዬ ያቋረጥኩትን ትምህርት መቀጠል ነው” የምትለን ወጣቷ እንባ ባቀረሩት አይኖቿ እየተመለከተችኝ ነበር ምኞቷን ያጫወተችኝ።
በዚህች ከእጅ ወደ አፍ በሆነች ኑሮዋ ታግላ ሳንቲም ማጠራቀም ጀምራ እንደነበር ታስታውሳለች። ከዚያም መታወቂያ ስላላት እንደ ሰው ዋስ ሆና ስራ ታስገባለች፤ ዋስ የሆነችለት ሰው ባጠፋው ጥፋት የተነሳ የእርሱን እዳ ሃያ አምስት ሺ ብር እንደከፈለች የምትናገረው አለም በሌላ ጊዜ ደግሞ ኑሮ ፈቀቅ አልል ሲል አረብ ሀገር ሄዳ ጥሪት ለመያዝ አስባ እሷንና ሁለት ጓደኞቿን እናስጨርስላችሁ ላሏቸው ህገወጥ ደላሎች በነፍስ ወከፍ 20ሺ ብር ተቀብለዋቸው እንደጠፉ ትናገራለች።
አንዱን ሽንቁር ስትደፍን ሌላው እየተቀደደ ከህልሟ መድረስ የሰማይ ያህል የራቀባት ወጣት መማር እየፈለገች ሊያውም ጥረት ሳይለያት ችግር አላንቀሳቀስ ያላት ይች ወጣት ወይ እንደ ሰው የስራ ቦታ አግኝቼ ስራዬን በስፋት አልሰራሁ፤ ወይ ደግሞ ከትምህርቴ አልሆንኩ፤ ቤተሰቦቼ ላይ ላለመሆን ስል የእለት የእለቱን እያሰብኩ ብቻ እኖራለሁ ትለናለች።
እንደ አለም አይነት ህልማቸውን በጥረታቸው ሊጨብጡ የተነሱ ነገር ግን የተሳሳተ አቋራጭ በመጠቀማቸው ወደ ኋላ የቀሩ ወጣቶችስ ስንት እንደሆኑ ቤት የቁጠራቸው። ለዛሬ ግን ያወቅናትን አለምን ለማገዝ እንነሳ። ሰው ለመርዳት ሰው መሆን ብቻ በቂ ነውና አለምን ከህልሟ ለማገናኘት ደጋግ ልቦች አስቡ ብዬ የዛሬውን አበቃሁ። በቸር ያሰንብተን።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ሰኔ 6/2013