እንዳሁኑ መረጃ እጃችን ላይ ባልሆነበት ጊዜ፤ ያኔ በሬዲዮ ዘመን ጥያቄ በመመለስ የሚታወቁ ስሞችን እንሰማ ነበር። ከነዚህም መካከል ማርታ ደጀኔ አንዷ ነበረች።ስሟን ውስጤ ያስቀመጥኩትን ልጅ በዳግማዊ ምኒልክ መሰናዶ ትምህርት ቤት አገኘኋት።ብዙም ባንቀራረብ በትምህርቷ ጎበዝ፤ ብርሁ አእምሮ ያላት ልጅ እንደነበረች አስታውሳለሁ። ለመሆኑ ማርታ ደጀኔ ማናት? የህይወት ውጣ ውረዶቿን እንዴት አለፈቻቸው ስል ጠይቄያታለሁ። ከምላሹ ጋር መልካም ቆይታ።
ማርታ ተወልዳ ያደገችው አዲስ አበባ ልዩ ስሙ “አራት ኪሎ”ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ነው። ገና የሁለት ዓመት ህጻን እያለች ነበር በፖሊዮ ምክንያት የአካል ጉዳተኛ የሆነችው።ቤተሰቦቿ “ትድናለች” በሚል ብዙ ሙከራ ቢያደርጉላትም ሊሳካ አልቻለም።ከባህላዊ እስከ ዘመናዊ ከመንፈሳዊ እስከ የባዕድ አምልኮ ሁሉንም ሞክረውላታል።ለአካል ጉዳተኝነት በወቅቱ ይሰጥ የነበረው አመለካከት የተዛባ በመሆኑና የማርታ ቤተሰቦች እንድትድን ካላቸው ጉጉት የተነሳ በየእለቱ አዳዲስ ነገርን በመሞከር ላይ ስለነበሩ ማርታ ቶሎ ወደ ትምህርት ቤት አልገባችም ነበር።
ማርታ ግን ከልጅነቷ ጀምሮ ብሩህ አእምሮ ስለነበራት ቤት ውስጥ ፊደል መቁጠር፣ መጻፍና ማንበብን ጠንቅቃ ለማወቅ ጊዜ አልፈጀባትም።የእህትና ወንድሞቿን መጻህፍት በማንበብ ከወንድሞቿ ሁሉ ልቃ መገኘቷን የተመለከቱት ቤተሰቦቿ መጻህፍት እየገዙ ያቀርቡላት ጀመር።ሌላው ቀርቶ ዕቃ ሲገዛ የተጠቀለለበት ጋዜጣን እንኳን “ቆይ እሷ ትየው!” ይባልና ይቀመጥ እንደ ነበር ታስታውሳለች።ትምህርት ቤት ውለው ከሚመጡትና ክፍል ከሚቆጥሩት እህት ወንድሞቿ ማርታ በብዙ እጥፍ የተሻለ የመቀበል ፍጥነት ነበራት።አንዳንድ ጊዜም ወንድም እህቶቿ የቤት ሥራ ሲሰጣቸው የማርታን እገዛ የሚፈልጉበት አጋጣሚም ነበር።ከዚያ በኋላ ነው እንግዲህ እሷም የመማር መብቷን ደጋግማ የመጠየቅ፣ ቤተሰቦቿም ድና እንደ እኩዮቿ ውላ ትገባለች የሚለው ውጤት አልባ ድካማቸው ተስፋ ስላስቆረጣቸው ማርታ ትምህርት ቤት እንድትገባ ውሳኔ ላይ የደረሱት፡፡
ከዛም ሰው ሰራሽ የአካል ድጋፍ እንድትጠቀም ሆኖ በአፄ ናኦድ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ከትምህርት ጋር ተዋወቀች፣ 2ኛ ደረጃ ትምህርቷን ደግሞ በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት ተከታተለች።አካል ጉዳተኛ በመሆኗ እንደእድሜ እኩዮቿ ተሯሩጣ ተጫውታ ባታድግም ከመጻህፍት ጋር ጥብቅ ቁርኝት የነበራት መሆኑን ትናገራለች። በማንበብ ፍቅር ታንጻ ያደገችው ማርታ ጎን ለጎን በኢትዮጵያ ሬዲዮ፣ ለገዳዲ እና ፋና ላይ የሚተላለፉ ዜናና ፕሮግራሞችን በትኩረት ከመከታተል ባሻገርም በጠቅላላ እውቀት ጠንካራ ተሳታፊም ነበረች፡፡
“ማርታ ደጀኔ ከአራት ኪሎ” የሚለው ስም በብዙ የሬዲዮ አድማጮች ዘንድ ጎልቶ ታወቀ።“ማን ትሆን?” የሚለውን የአድማጮችን ጥያቄ ምላሽ ያገኝ ዘንድም ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ከታሜሶል ኮሚኒኬሽን ጋር በትብብር በሚያቀርበው የሐሙስ ማታ የጥያቄና መልስ ውድድር ላይ ከአንዴም ሁለት ጊዜ ተወዳድራ በማሸነፍ ማንነቷን ለማስተዋወቅ ተጠቅማበታለች።ሁለተኛው ውድድር ላይ ስትሳተፍ ግን ማርታ ዓላማ ነበራት።12ኛ ክፍል አጠናቅቃ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም የሚያስገባትን ውጤት በመጠባበቅ ላይ እያለች ለወራት ያለሥራ መቀመጥ አልፈለገችም።
እናም የግል ጋዜጣ ጀምራ ለመስራት ፍላጎት አደረባት፤ ግን ገንዘብም ሆነ ሥራውን ለመስራት የሚያስችሏት ቁሳቁሶች አልነበራትም።ፈቃድ ለማግኘት ደግሞ በባንክ አካውንቷ ብር 10,000 የተሟላ ቢሮ ኮምፒውተርን ጨምሮ ማሟላት ግዴታዋ ነበር።ገንዘቡን ከማይክሮ ፋይናንስ በብድር ስታገኝ፣ በጠቅላላ እውቀት ተሳትፎ ደግሞ ኮምፒውተሩን አሸንፋ የጋዜጣ ማሳተም ህልሟን እውን አደረገች።ያሰበችውን ለማሳካት ምንም ነገር እንቅፋት እንዳይሆንባት የምትጥረው ማርታ፣ የጋዜጣዋን ስም “እውን” አለችውና በሥነ-ጽሑፍ የምታውቃቸው ጓደኞቿን በማሰባሰብ በተከራየቻት አንዲት ጠባብ ቢሮ ውስጥ ሥራቸውን ጀመሩ።ነገር ግን የተበደረችውም ገንዘብ ሲያልቅ ‹‹እውን›› ጋዜጣ በዚያው ቆመች።የማርታ የጋዜጠኝነት ፍቅር ግን አልቀነሰም፤ ጥረቷንም አላቋረጠችም።የከፍተኛ ተቋም መግቢያ ውጤትም ይፋ ሆነና ማርታ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ-ጽሑፍ ዲፓርትመንትን ተቀላቀለች።
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሁለተኛ ዓመት ተማሪ እያለች በዛሚ 90.7 ኤፍ.ኤም ላይ ተወዳድራ በመግባት ለ4 ዓመታት በጋዜጠኝነት አገልግላለች።ከዩኒቨርሲቲው በኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ-ጽሑፍ የመጀመሪያ ዲግሪዋንም ተቀበለች። ለማርታ ትምህርትና ጥረት ወደ ስኬት ማማ የሚያወጧት ነገሮች በመሆናቸው ትጋቷ ከልብ ነበር።
እንደሚታወቀው በሀገራችን ህንፃዎች አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ አድርገው የማይሰሩ መሆናቸው ማርታን አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ከቷት እንደነበር ታስታውሳለች። በዛሚ ኤፍ ኤም የነበራትን የጋዜጠኝነት ሥራዋን እንድታቆም ያስገደዳት በተቋሙ መወጣጫ አሳንሰር ከሦስተኛ ፎቅ ስለሚጀምር በነፍሰጡርነቷና አካል ጉዳተኝነቷ ምክንያት ደረጃ መውጣትና መውረድ ሲያስቸግራት ስራዋን ማቆም ግድ ሆኖባት እንደነበረ ታስታውሳለች።
የመጀመሪያ ልጇን ካቀፈች ከቆይታ በኋላ “እውን የማስታወቂያ ሕትመትና ፕሮሞሽን ሥራ ድርጅት”ን በ2000 ዓ.ም በማቋቋም ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ጋር በመተባበር በአካል ጉዳተኝነት ላይ ትኩረት ያደረገ “ማዕዶት” የተሰኘ ሳምንታዊ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ለ5 ዓመታት ያህል ስታቀርብ ቆይታለች።ከመደበኛ ፕሮግራሟ ባሻገር ሃይማኖታዊና ብሔራዊ በዓላትን የቴሌቪዥን የአየር ሰዓት በመውሰድ ማስታወቂያ የሚያስነግሩና ስፖንሰሮችን በማሳተፍ አዝናኝ ፕሮግራሞችን በመሥራት ትታወቃለች።ከፕሮግራሙ አዝናኝነት ባሻገር የአካል ጉዳተኝነትን ጉዳይ በማካተት ፕሮግራሙ እያዝናና የሚያስተምርበትን ይዘት በመቅረፅ ረገድ ብርቱ ጥረት አድርጋለች፡፡
የአካል ጉዳተኞች ዘመናዊ ዳንስና ባህላዊ ውዝዋዜን በፕሮግራሙ መካከል በማስገባት አድማጭ ተመልካቹ ስለ አካል ጉዳተኞች የተሻለ ዕይታ እንዲኖረው ጥረት ስታደርግ ቆይታለች።በዚህም ትልቁን አስተዋፅኦ ያበረከተው በሃገራችን የአካል ጉዳተኞችን ውዝዋዜ በማሰልጠን ፈር ቀዳጅ የሆነው የዳንስ ባለሙያ (ኬሮግራፈር)ታደሰ ገብሬ (ጃክሰን) በቀዳሚነት ይጠቀሳል።አካል ጉዳተኛ የሆኑ ወጣቶችም ሳይሸማቀቁ ችሎታቸውን በመድረክ በማሳየት ረገድ ለፕሮግራሙ መሳካት የላቀ ሚና ነበራቸው፡፡
ማርታ ከዚህ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ጎን ለጎንም “ተምሳሌት” እና “ጠብታ” የተሰኙ መጽሔቶችንም በማሳተም ለአንባብያን በነጻ በማድረስ ላይ ነች።ተምሳሌት መጽሔት በማስታወቂያ ድርጅቷ አማካይነት የሚታተም ሲሆን፤ አካል ጉዳተኝነታቸውን በምክንያትነት ሳያስቀምጡ ችሎታቸውን አውጥተው ከራሳቸው አልፈው ለሌላውም መትረፍ የቻሉ በሀገር ውስጥም ይሁን በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና የተቸራቸውን ምሳሌ የሆኑ ግለሰቦች የሕይወት ተሞክሮ የሚስተናገድበት ነው።
ጠብታ መጽሔት Ewin Charitable Association ሥር የሚታተምና የማኅበሩ ልሳን ሲሆን፤ በየዓመቱ ህዳር ወር ላይ ተከብሮ የሚውለውን ዓለም አቀፉን የአካል ጉዳተኞች ቀንን ምክንያት በማድረግ የሚታተም ዓመታዊ መጽሔት ነው።
ስለህመሙ የሚያውቀው የታመመው ሰው ራሱ በመሆኑ እሷ ካለፈችበት የአካል ጉዳተኝነት ውጣውረድ ብሎም የሴትነት የሕይወት ጫና እንዲሁም በሙያዋ ከገጠሟት በመነሳት “እውን የበጎ አድራጎት ማኅበርን” በማቋቋም አካል ጉዳተኞች በእጅጉ የሚቸገሩበትን ሰው ሰራሽ የአካል ድጋፍ (ዊልቸር) ሀገር ውስጥ በመገጣጠም ተደራሽ በማድረግ እንዲሁም የውጭ ምንዛሪን በማዳን ረገድ አስተዋጽኦ የሚኖረውን የበጎ አድራጎት ሥራ በመሥራት ላይ ትገኛለች።
አካል ጉዳተኝነት በራሱ የሚፈጥረው ጫና እንዳለ ሆኖ በተለይ ሴት አካል ጉዳተኞች ላይ የሚደርሰው ተፅዕኖ ቀላል የማይባል መሆኑን ማርታ ተናግራለች። ለዚህም በጤናና ሥነ-ተዋልዶ ዙሪያ ያልተዳሰሱ ጉዳዮች ላይ ትኩረት በማድረግ የድርሻዋን ለመወጣት ጥረት በማድረግ ላይ ትገኛለች።በአሁኑ ወቅት ሁለት ድርጅቶችን በማስተዳደር ላይ ትገኛለች።
አካል ጉዳተኝነትና ሴትነት ተደማምሮ የተለያዩ የህይወት ተግዳሮቶችን እንድትጋፈጥ እንዳደረጋት ማርታ ትናገራለች። ከሁሉም በላይ በማህበረሰቡ ውስጥ የሚታየው በአካል ጉዳት ላይ ያለው የተዛባ አመለካከት በአካል ጉዳተኞች ላይ የሚፈጥረው ጫና ገፈት ቀማሽ መሆኗን ትናገራለች።
ከሁሉም በላይ በተለያዩ ጊዜዎች የሚሰሩ መሠረተ- ልማቶች አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ አለማድረጋቸውን እንደ ችግር ታነሳለች። (መንገድ፣ ት/ቤቶች፣ የጤና ተቋማት፣ የመዝናኛ ሥፍራዎች፣የተለያዩ ህንፃዎች ወዘተ.) አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ አድርገው ባለመገንባታቸው እንደሌላው ውሎ ለመግባት አስቸጋሪ መሆኑን ትናገራለች።
ጋዜጠኛ ማርታም የዚህ ማኅበራዊ ችግር ቀማሽ ሆና አልፋዋለች።የጋዜጠኝነት ሙያም ለአካል ጉዳተኞች የማይሆን እንደሆነና ፈጽሞ ይህንን ሥራ እንዳትሞክረውም ቢነገራትም እንኳን ሙያ በልብ ነውና በጽናት ታግላ አሸንፋዋለች።ለአካል ጉዳተኞች ትዳር መመሥረት፣ ልጆችን መውለድና ቤተሰብ ማፍራት ከባድ ስለሆነ እንዲህ አይነት ሃሳብ ካላት ቢቀርባት መልካም እንደሆነ ብዙ አስተያየቶች ተሰጥቷት የነበረ ቢሆንም ያንን ተሻግራዋለች።
መልካም የትዳር አጋርነቷን፣ በፈጣሪ የተቸራትን የእናትነት ጸጋዋን ከላይ ከሚታየው የአካል ጉዳት ሁኔታዋ ጋር እያስተያዩ በጎ ያልሆነ አስተያየት የሰጧትም ነበሩ።ሌላው ቀርቶ ጋዜጣ በምታሳትምበት ወቅትም ይሁን የቴሌቪዥን ፕሮግራሟን ስታዘጋጅ “የአካል ጉዳተኞች ጉዳይ እኔንም ይመለከተኛል!!” ባይ ተቆርቋሪ አለመኖሩና የሚደግፋት ማጣቷ አሳዝኗትም ያውቃል።ነገር ግን ሁሌም የምትሞክር፣ የማትሰለችና ትእግስትን የህይወት መመሪያዋ አድርጋ የምታምን በመሆኗ ሁሉንም ታግላ አሸንፋለች።
ለኛ ለኢትዮጵያውያን ቤተሰብ ከመመስረት ከማግባት ከመውለድ የበለጠ እንደ ትልቅ ስኬት የሚጠቀስ ነገር አለመኖሩ የሚታወቅ ነው፤ ማርታ በትዳር ዓለምም የተሳካላት ናት።ከባለቤቷ ከአቶ ዮሐንስ አለማየሁ ጋር በትዳር ከተጣመሩ ከአንድ አስር ዓመታት በላይ ያስቆጠሩ ሲሆን የልጆች እናትም ናት።በበርካታ ቤተሰቦች መካከል የምትገኘው ጋዜጠኛ ማርታ እርሷም ቤተሰባዊ ኃላፊነቷን ጠንቅቃ የምታውቅና ይህንንም አቅም በፈቀደ መጠን ለመወጣትና ሁሉንም ለማስደሰት የምትታገል ጠንካራ ሴት ናት።አካል ጉዳት መልካም እናት ጥሩ ሚስት ከመሆን አላገዳትም።
ለማርታ መኖር ትግል ነው፤ ታግሎ ማሸነፍ ከትግል በኋላ ወደከፍታ መራመድ ነው፤ ለማርታ ህይወት እሷ ያለፈችበትን መከራ ሌሎች እንዳያልፉ መታገል ነው፤ ለማርታ መኖር ማለት ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ መሆን ላልተሳካላቸው የስኬትን መንገድ መጥረግ ነው። የፅናት ተምሳሌት የአልበገርም ባይ እናት የሆነችው ይች ሴት በቀጣይም የአካል ጉዳተኞችን ችግር የተገነዘበ ማህበረሰብ እንዲፈጠር ጠንክራ የምትሰራ መሆኑን ትናገራለች።
ሴትነት እግር ከወርች ሳያስራት፤ አካል ጉዳተኝነት ከአላማዋ ሳያናጥባት ትልቅ ደረጃ የደረሰች ሴት በቤተሰባዊ ህይወትም ሆነ በስራ እንቅስቃሴ የተሳካላት ይችን አይነት የጥንካሬ ተምሳሌት ያበርክትልን ብለን ከማርታ ጋር የነበረንን ቆይታ አጠናቀናል። በቸር ያሰንብተን።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ግንቦት 22/2013