የሰው መገናኛው በአንድም በሌላም ነውና ለሥራ ጉዳይ ቀጠሮ ይዤ ወደ አንድ ቢሮ ጎራ ባልኩበት ወቅት ወደ ቀጠሩኝ ሰው ቢሮ ከመግባቴ በፊት በፀሃፊዋ ቢሮ ውስጥ እያለሁ ቀይ ረዘም ያለች በፈገግታ የተሞላች ሴት ተመለከትኩኝ። ጉዳዬ ከሌላ ሰው ጋር ቢሆንም የቀጠርኳቸው ሴት እስከሚመጡ አንድ ሁለት እያልን ጨዋታ ጀመርን። ወይዘሮዋ አንደበተ ርቱእ በዛ ላይ ንግግሯ የቋንቋ ለዛ ያለው ሲሆን ስለማንነቷና ስራዋ ስታጫውተኝ ቆይታ ሌላ ጊዜ በሰፊው እንደምንገናኝ ተቀጣጥረን ተለያየን።
በተቀጣጠርነውም መሰረት ወይዘሮዋ ከቀጠሯችን ሰአት ቀደም ብላ ተገኝታለች:: ሰዓት አክባሪነቷን፣ ጨዋነቷን ተገነዘብኩ:: ወይዘሮ አባይዳር ከተማ የህይወት ልምዷን ልታካፍለን ፍቃደኛ ስለሆነች አመስግኛት በዚህ መልኩ ቆይታ አድርገናል። መልካም ንባብ።
̋ወይዘሮ አባይ ዳር ማን ናት?” ስል ላቀረብኩላት ጥያቄ ወይዘሮዋ እንዲህ ብላ ትጀምራለች። ”አባይ ዳር ኩሩ ኢትዮዽያዊት ሴት ናት። ኢትዮዽያዊነት ከፈጣሪ የተሰጠ በረከት ነው። ማንም ልሁን ብሎ የማይሆነው፣ ለኢትዮዽያዊያን ብቻ የተለገሰ መሆኑ ሁሌም ደስታ ይሰጠኛል። የተወለድኩት በድሮ ስሙ ሲዳሞ ክፍለ ሀገር ዲላ ከተማ ላይ ነው። ያደኩት ደግሞ ሊሙ ገነት የምትባል በቀድሞ አጠራር ከፋ ክፍለ ሀገር ውስጥ ነው::”
እድሜዬ ለትምህርት እንደደረሰ በዛው በሊሙ ገነት ሀሁ ቆጥሬ እስከ ስምንተኛ ክፍል በዛው ቆየሁ። ከዛ በኋላ አዲስ አበባ በመምጣት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን በመድሀኒኣለም ትምህርት ቤት ተማረኩ። የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ፈተና ውጤት አምጥቼ በወቅቱ ታዋቂ በነበረው የንግድ ስራ ትምህርት ቤት ገባሁ።
ኮሜርስ በዲፕሎማ ከጨረስኩ በኋላ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብቼ የመጀመሪያ ዲግሪዬን በአካውንቲንግ አገኘሁ፤ ከዛ በኋላ ታይላንድ /ባንኮክ/ በቢዝነስ አድሚንስትሬሽን ሁለተኛ ዲግሪዬን ከሰራሁ በኋላ አሁን ዶክትሬት ድግሪዬን አሜሪካን ሀገር ዳላስ የሚገኝ ባኬ ግራጅዌት ስኩል የተባለ ተቋም እየተማረኩ ነው ያለሁት ” ትለናለች።
መጀመሪያ ከኮሜርስ እንደተመረቀች ስራ የተዋወቀችበት መስሪያ ቤት ድሮ እርሻ ምርምር የነበረ አሁን ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት በሚባል የመንግስት ተቋም ውስጥ ነበር። የመጀመሪያ የስራ ቦታዬን “እንደልጅነት ቤቴ ነው የምወደው።” የምትለው የዛሬ ባለታሪካችን በዚህ መስሪያ ቤት ከጁኒየር አካውንታንት እስከ ፋይናንስ ስፔሻሊስት የሚባሉ የስራ እርከኖች ድረስ በመመደብ ማገልገሏን በትዝታ ወደኋላ መለስ ብላ ታስታውሳለች።
በዚሁ ተቋም በወርልድ ባንክ የሚደገፉ የተለያዩ ፕሮጀከቶች ነበሩ። ወይዘሮ አባይዳርም በእነዚህ ፕሮጀክቶች ላይ የሂሳብ ስራዎችን ትሰራ ነበር። አንድ አግሪካልቸራል ሪሰርች ትሬኒንግ ፕሮጀክት የሚባል ፕሮጀክት ላይ በምትሰራበት ወቅት ሁለተኛ ዲግሪዋን የመማር እድል አግኝታ በታይላንድ ባንኮክ ተምራ መምጣቷን ትናገራለች።
ከታይላንድ ከተመለሰች በኋላ በዚያው መስሪያ ቤት የተወሰነ አመታት በማገልገል ወርልድ ቪዥን ኢትዮዽያ በተባለ ግብረሰናይ ድርጅት ውስጥ ለአመታት መስራቷን ታስታውሳለች። የቅጥር ህይወት ይብቃኝ በማለት የግል ስራ መስራት ከጀመረች የተወሰኑ አመታትን አሳልፋለች።
“ልዩ ፍላጎቴ መፅሀፍ ማንበብና ተፈጥሮን መጎብኘት ነው። ተፈጥሮ እጅግ በጣም ታስደንቀኛለች፤ ተፈጥሮን መመልከት ነፍሴ ሀሴት እንድታደርግ ይረዳታል። ከሀገር ውስጥም ከሀገር ውጪም የተለያዩ ታሪካዊ ቦታዎችን እጎበኛለሁ።” የምትለው ወይዘሮ አባይ ትውልዷና እድገቷ የተፈጥሮ ገፅታቸውን ጠብቀው በኖሩት ዲላና ሊሙ ገነት አካባቢ በመሆኑ ተፅእኖ አንዳሳደሩባት ትናገራለች።
ስለ ትዳር ህይወቷ ለጠየቅናት ጥያቄ መልሷ “በጣም የማከብረው፣ የምወደው የትዳር አጋር ነው ያለኝ፤ ለኔ ለእያንዳንዷ ስኬቴ ምክንያት የእሱ እጅ አለበትና አመሰግነዋለሁ” በሚል ንግግር የጀመረችው ወይዘሮ አባይ በትዳር የተገናኙት ሁለቱም የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች እያሉ እንደነበር ታስታውሳለች።
“ተማሪዎች ሆነን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አብረን እናገለግል ነበር። የልጅነት ጓደኛሞች ነበርን። ይህ ጓደኝነት እያለ እኔ ወደ ኮሜርስ እሱ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብተን እየተማርንም ጓደኝነታችንም አልተቋረጠም ነበር። እሱ ትምህርቱን ጨርሶ ተመርቆ ወደ ወለጋ ክፍለ ሀገር ሄደ። እኔ ደግሞ አዲስ አበባ እርሻ ምርምር የሚባል መስሪያ ቤት ስራ ጀመርኩ። በየሶስት ወሩ ለእረፍት ይመላለስ የነበረው የልጅነት ጓደኛዬ ሲመጣ ፍቅሩን ገልፆ ለመጋባት ጠየቀኝ። እንዲህ የተጀመረው የፍቅር ህይወት 28 አመታትን ብዙም መንገራገጭ ሳይከሰትበት እዚህ ደርሰናል።” ትለናለች።
ባለቤቷን የህይወት መምህሬ ፤ መንገድ መሪዬ እያለች የምትጠራው ወይዘሮ ባለቤቷ የቤቱ ራስ እንደሆነ በማመንና በመከባበር የምትኖር መሆኑን ነው የምትናገረው። እድገቷና ስኬቷን የሚመኝ ለስኬቷ ቀኝ እጅ ከሆነላት የትዳር አጋሯ ሶስት ወንድ ልጆችን አፍርታለች።
“የሰው ህይወት ያለመሰናክል አይቀጥልም። እኔ ከልጅነቴ ጀምሮ በአያቶቼ እጅ በፍቅርና በእንክብካቤ ነው ያደግኩት፤ ከአያቶቼ በኋላ በፍቅር በቤተ ክርስቲያን ነበር ያደግኩት። ፍቅርና ሰላም ጠግቤ ነበር የኖርኩት። ባገባሁ በመጀመሪያዎቹ አመታት አከባቢ ከትዳር በኋላ የሚጠበቀውን ልጅ እንዳረገዝኩ እጅግ በጣም በሚባል ደረጃ ታመምኩ። ሆስፒታል ውስጥ እየተረዳሁ እርግዝናው እንዲቀጥል ቢሞከርም ለህይወቴ አስጊ የሚባል ደረጃ በመድረሱ የመጀመሪያው እርግዝና ተቋረጠ። ያ ልቤን ክፉኛ ሰብሮት ነበር።” የምትለው ወይዘሮ እርግዝና አይመከርም እየተባለች እንኳን ከጉጉቷ የተነሳ ለሁለተኛ ጊዜ አርግዛ ለስቃይ ተዳረገች።
በዚህ ሁሉ ስቃይ ውስጥ አሁን የመጀመሪያ ልጄ እያለች የምትጠራው ልጅ በማህፀኗ ባደረ ጊዜ በእምነቷ ፈውስ እንዳገኘች ተነግሯት እነሆ የሶስት ልጆች እናት ሊያውም እጅግ በጣም ስኬታማ የሆኑ ልጆች እናት ሆነች፤ ̋የተባረከ ቤተሰብ ስለሰጠኝ ፈጣሪዬን እጅግ በጣም አመሰግናለሁ። ምንም ልጅ አይኖርም የተባለበት ቤት በሶስት ቆንጆ ወንድ ልጆች እንዲሞሉ ስለሆነ ፈጣሪን አመሰግናለሁ።” የምትለው ወይዘሮ አባይዳር ስለ ልጆቿ ስታወራ ፊቷ ላይ የሚታየውን ኩራት ለተመለከተ ማንም እናት ልጆቿ ለወግ ማእረግ ደርሰው የሚሰማት ስሜት ነፀብራቅ እንደሆነ መገንዘብ አያዳግተውም።
ልጆቿን በተገቢው መንገድ በስርአት እንዳሳደገች የምታምነው እናት ለውጤቷም መለኪያ ልጆቿ በትምህርታቸው፤ በስነ ምግበራቸውም የተመሰገኑ ስኬታማ የሆኑ ልጆች መሆናቸው ነው። የመጀመሪያ ልጇ የማስተርስ ዲግሪውን የያዘ ሲሆን ሁለተኛው ልጅ የመጀመሪያ ዲግሪውን ጨርሷል፤ ሶሰተኛውም ልጅ በዩኒቨርሲቲ የሶሰተኛ አመት ተማሪ ነው። ሁሉም በአሜሪካን ሀገር የሚማሩ ሲሆን በትምህርት ራሳቸውን ካበለፀጉ በኋላ ሀገራቸው ገብተው የመስራት እቅድ አላቸው።
ሴቶች በተለያየ አይነት ፈተና ወስጥ ሊያልፉ ይችላሉ። ማንም ሰው ቢሆን ግን የቆመበትን መሰረት ኣስተካክሎ ማወቅ ይገባዋል። የሰው ልጅ ሊመሰረትበት የሚገባው ነገር ፍቅርና እምነት ላይ ነው። በማለት እያንዳንዱን ፈተና በፍቅርና በእምነት መሻገሯን የምትናገረው ወይዘሮ አባይዳር ሰው በህይወቱ ይፈተን ዘንድ ግድ ነውና በትእግስትና በእምነት ከፈተናዎች ትምህርት እየወሰዱ መሻገር ሴቶች ማድረግ ያለባቸው ተግባር መሆኑን ትናገራለች።
በሰፊ ቤተሰብ ውስጥ ነው ያደግኩት የምትለው ወይዘሮ ያደገችበት አከባቢ ሙስሊሞችም ክርሰቲያኖችም የሚኖሩበት ነው:: አያቷ ደግሞ ለአከባቢው እንደ ትልቅ አድባር የሚታዩ ነበሩ። አያቷ ቡና ቤት ነበራቸውና ቡና ቤቱ በር ላይ ትልቅ ዋርካ እንደነበር ታስታውሳለች። እዛ ዋርካ ስር አምልኮ ይደረግ ነበር። በእምነት ልዩነት ሳይሉ ያንን የባህል አምልኮ ያደርጉ ነበር። ያ አንድ ዛፍ ያን ሁሉ ሰው መሰብሰብ ከቻለ ከአንድ ዋርካ የምትልቀው ሰፊዋ ኢትዮዽያስ ሁሉን ባንድ ጥላ ስር መሰብሰብ ይሳናት ይሆን? ስትል ትጠይቃለች።
የፒ.ኤች.ዲ ማጠናቀቅያ ጥናት እየሰራች ያለችው ወይዘሮ ጥናቷ ሀገራችን ላይ ላሉ ችግሮች መፍትሄ ሊሆን የሚችል ሀሳብን የሚያነሳ ነው ትላለች። የሴቶች ተሳትፎ ግጭትን በማስቀረት እንዴት ሰላምን ማስፈን ይቻላል የሚል ሀሳብ ያለው ሲሆን በርእሰ ጉዳዩ ከሚዳሰሱት ውሰጥ የሰውን ህይወት የሚዳስሱ ጉዳዮችን አካቷል:: ጦርነት በማንኛውም ማህበረሰብ ውስጥ ይከሰታል፤ ሰላም ማጣት ግን በአብዛኛው ሲጎዳ የሚታየው ሴቶችን ነው። የማህበረሰብ እኩሌታ የሆኑት ሴቶች ታዲያ ለምን የመፍትሄ አካል አይሆኑም? የሚል መነሻ እንዳለው ታስረዳለች።
̋ሰላም ለሴቶች ወሳኝ ጉዳይ ነው:: ሰላም የማይኖር ከሆነ ሴት ልጅ ህይወቷን መምራት አትችልም፤ ሰላም የማይኖር ከሆነ ልጆቿን ማሳደግ ማስተማር በወግ በማእረግ መዳር መኳል አትችልም። ስለዚህ እነዚህ ግማሽ የህብረተሰብ ከፍሎችን ያላካተተ ሰላም ትክክለኛ ሰላም አይሆንም” ትላለች።
ሁሉም ሴቶች ተፈጥሮ የለገሰቻቸው መሪነት ውስጣቸው አለ። ሴት ልጅ ያላትን ጥንካሬ እና አቅም በመጠቀም ሰላምን ማምጣት ትችላለች። ሴቶች ሰለማዊ፤ በጣም ጠቃሚ ነገሮችን በመስራት ይታወቃሉና ይህን እድል እንዴት እንጠቀም በሚለው ሀሳብ ለመስራት ያሰበችው ወይዘሮ ሴቶችና ልጃገረዶች ላይ ከሚሰራ አንድ ድርጅት ጋር እንደተነጋገረች ትገልጻለች:: ̋እነሱ እኔ በማስበው አይነት ሳይሆን ሴቶችን የማብቃት ስራ ላይ የሚሰሩ ሲሆን ሴቶች ከበቁ ለዓለም መቆም ይችላሉ ብለው ያስባሉ። ሴት በሁሉም ነገር ስትበቃ ሀገር ማስተዳደር፣ ዓለምን መቀየር ትችላለች።” በሚል እሳቤ የጥናቷን ሀሳብ ከድርጅቱ አላማ ጋር በማጣጣም አቅም የመፍጠር ሀሳብን ይዘው እየተንቀሳቀሱ እንደሆነ ወይዘሮ አባይዳር ትናገራለች።
ሁሌም ሰው ከራሱ ከጀመረ ለውጥ ያመጣል በሚል ሀሳብ ̋እኔ ነኝ” በማለት በጎውንም ጥሩውንም ነገር ወደ ራስ በመውሰድ ለሰላም ራስን ተጠያቂ አድርጎ ይቅርታን በመጠየቅ ስለ ሰላም በመስበክና በመናገር የለውጥ አካል ለመሆን የእናቶች የፀሎት የይቅርታ መርሃ ግብሮች በማዘጋጀት እናቶች ልጆቻቸውን ስለሰላም እንዲያስተምሩ፤ የሚያሳድጓቸው ልጆች ለሀገር የሚተርፉ ትውልዶች እንዲሆኑ የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ያደርጋሉ።
ትውልድ የሚወጣው ከቤተሰብ ነው፤ ከቤተሰብ የወጣ ትውልድ ነው የሀገር መሪም፣ የሀገር አጥፊም የሚሆነው። ስለዚህ ትውልድ ላይ መስራት ይኖርብናል የምትለው ወይዘሮ አባይ ዳር በመጨረሻም እንዲህ የሚል መልእክት በማስተላለፍ ጭውውታችንን አብቅተናል።
”ለኢትዮዽያዊያን መልእክት አለኝ። እንደማመጥ!!! ሁላችንም ተናጋሪ ከሆንን የምንፈልግበት ቦታ አንደርስም። የሰላም የእድገት ፍላጎታችን ከአንደበት የዘለለ ስራ አይሰራም። እያንዳንዱን ያደመጥነውን ነገር በተናጋሪው ጫማ ውስጥ በመሆን መስማት ይኖርብናል። አንደበት እሳት ነው የሚል አባባል አለ። ከመናገራቸን በፊት ስለምንናገረው ነገር በደንብ አብላልተን ከመናገራችን በፊት ሊመጣ የሚችለውን ሊደርስ የሚችለውን ማሰብ የግድ ነው።”
የምናጭደው የዘራነውን ነው:: በአፋችን የዘራነው ክፋት አሁን ከምድራችን የሰው ህይወትን እያሳጨደን ሰለሆነ ከሞትና ከሰቆቃ ለመዳን አንደበታችንን የሚገዛ አእምሮ ይኑረን በሚል መልእክት የዛሬውን ፅሁፍ አበቃን።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ግንቦት 15/2013