ደግነት ፊታቸው ላይ የሚነበበውን ወይዘሮ በስራ አጋጣሚ አገኝቼ የተመለከትኳቸው እለት ርህራሄ ፍታቸው ላይ ጎልቶ ይነበብ ነበር። በኦቲዝም ዙሪያ በተዘጋጀው መርሀ ግብር ላይ ሸብረቅ ደመቅ ብለው ከተሰብሳቢው መካከል ጎልተው ይታዩ ነበር። ቆንጆ በዛ ላይ ዘናጭ ብሎም ደግ ልብ የተጎናፀፉት ወይዘሮ ዘሚ የኑስ ለመናገር አንደበታቸው ሲከፈት ማር ይዘንባል ከአፏ የሚባሉ አይነት ነበሩ።
ወይዘሮ ዘሚ የኑስ ሚያዝያ 4 ቀን 2013 ዓ.ም የኮሮና ቫይረስ ምርመራ ሲያደርጉ ፖዘቲቭ መባላቸውንና ከቀናት በኋላም ለመተንፈስ ተቸግረው ኦክስጅን በማስፈለጉ ከቀናት በኋላ ሚሊኒየም ሆስፒታል ገብተው ሲታከሙ እንደነበርና ወደ መጨረሻም ቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ተዛውረው በፅኑ ህክምና ማዕከል ውስጥ ሲረዱ መቆየታቸውም ተሰምቷል። ደከመኝ ሰለቸኝ የማያውቁት ወይዘሮ ዛሬ በሽታ ክንዳቸውን አዝሎ ነጠቀን። ከዚህ ቀደም ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ጋር ካደረጉት ቃለ ምልልስ በመነሳትና ሌሎች ምንጮችን በመጠቀም ለዛሬው የሴቶች አምድ እንዲሆን አዘጋጅተነዋል። መልካም ንባብ!!
ወይዘሮ ዘሚ የተወለዱት የዛሬ ሃምሳ አምስት ዓመት በፊት ጥቅምት 7 ቀን 1951 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ጣሊያን ሰፈር በሚባለው መንደር ነው። የአቶ አህመድ የኑስና የወይዘሮ ድሐብ ፎሌ አምስተኛ ልጅ የሆኑት የዚያን ጊዜዋ ህፃን ዘምዘም በካቴድራል ሴቶች ትምህርት ቤት ትምህርታቸውን የጀመሩት ገና በስድስት ዓመታቸው ነበር። በልጅነታቸው ለሥነ ጥበብ (አርት) ዝንባሌ ነበራቸው።
የስምንተኛ ክፍልን ብሔራዊ ፈተና አልፈው ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሲገቡ ቤተሰቦቻቸው ልጃቸውን ናዝሬት ትምህርት ቤት ለማስገባት ያቅዳሉ የዚያን ጊዜዋ ተማሪ ዘምዘም ግን ከጓደኞቻቸው “አልለይም» በማለታቸው የእቴጌ መነን ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ ይሆናሉ። ይሁን እንጂ ተማሪ ዘምዘም በት/ቤቱ የቆዩት ለሦስት ወራት ብቻ ነበር።
በእቴጌ መነን ትምህርት ቤት የዘጠነኛ ክፍል የአማርኛ ቋንቋ መምህር የነበሩት “ሴቶችን የሚያንቋሽሹና የሚያዋርዱ» ምሳሌያዊ አባባሎችን እንዲነግሯቸው ወይም በጽሑፍ እንዲሰጧቸው ይጠይቋቸዋል። የመምህሩ ጥያቄ ያናደዳቸው የዛኔዋ ተማሪ ፊት ለፊት ለመቃወም እንደማይችሉ ያምናሉ። ጉዳዩን ለትምህርት ቤቱ ዳይሬክተር ቢከሱም ተደማጩ አስተማሪው ሆነ።
የመምህሩ ፀረ-እኩልነት አስተሳሰብ ያስቆጣቸው ወይዘሮ ዛሚ ጉዳዩን ለአባታቸው በመንገር የሚወዱትን የአማርኛ ትምህርት በአግባቡ ይከታተሉ ዘንድ ሌላ ትምህርት ቤት እንዲያስገቧቸው ይጠይቋቸዋል። በልጃቸው መልካም አስተሳሰብ የተስማሙት አባትም በመኖሪያ ቤታቸው አካባቢ በሚገኘው ንፋስ ስልክ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እንዲገቡ ያደርጓቸዋል። በዚሁ ትምህርት ቤት እስከ አስራ አንደኛ ክፍል ድረስ ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ እያሉ ያልጠበቁት ሁኔታ ይከሰታል።
ወቅቱ የአብዮት ጊዜ ስለነበር ወጣቱ በተለይም ተማሪው እንደወንጀለኛ ተቆጥሮ በፀረ-ሕዝብነት ተፈረጀ። እናም ተማሪ ዘምዘም በወጣቶች ላይ የሚደርሰው ወከባ አስፈሪ ይሆንባቸዋል። የትምህርት ቤታቸው መዘጋትና መከፈት ያበሳጫቸዋል። ተማሪዎች እየተያዙ ወደ እስር ቤት ሲወሰዱ በማየታቸው ስጋት ውስጥ ይገባሉ። በወጣቱ ላይ ያንዣበበውን ዕልቂት የተገነዘቡት ተማሪ ዘምዘም ወደ ውጭ ሀገር ለመሄድ ታላቅ እህታቸው በፈጠሩላቸው ምቹ ሁኔታ ከቤተሰቦቻቸውና ከሚወዷት አገራቸው ተለይተው በ1969 ዓ.ም ወደ ኢጣሊያ በረሩ።
በአስራ ሰባት ዓመት ዕድሜያቸው የስደት ኑሮን ሀ ብለው የጀመሩት ወጣቷ ዘምዘም ምንም እንኳ ታላቅ እህታቸው ወደ ጣሊያን እንዲገቡ ምቹ ሁኔታ ቢፈጥሩላቸውም ምግብና መጠለያ እንዲሁም አልባሳትን ለማግኘት የግድ መሥራት እንዳለባቸው ያስገነዝቧቸዋል።
በቤተሰብ ቤት ለዚያውም በምቾት ያደጉት ልጅ በምግብ አብሳይነትና በሞግዚትነት ለማገልገል የቤት ሠራተኛ ሆነው ይቀጠራሉ። በዚሁ ስራ ላይ ተሰማርተው በትርፍ ጊዜኣቸው ታይፕ እና አረፍተ ነገርን ወይም ቃላትን በአጭር የመጻፍ (shorthand) ትምህርት መከታተል ይጀምራሉ። በቤት ሠራተኛነትና በሞግዚትነት በሚያገኙት ገንዘብ እራሳቸውን በፀሐፊነት ከአሰለጠኑ በኋላ ለአንድ ዓመት ያህል የቆዩበትን ሥራ በማቋረጥ በአንድ የስደተኞች ዕርዳታ ድርጅት ተቀጣሪ ይሆናሉ።
በአጭር ጊዜ ውስጥም የፀሐፊነት ሥራቸውን በብቃት በመወጣታቸውና በሥራቸው ያሳዩትን ቅልጥፍናና ትጋት የተመለከቱ የድርጅቱ አመራሮችም የድርጅቱን ሥራ በጉዳይ አስፈፃሚ መኮንንነት እንዲሰሩ የደረጃ ዕድገት በመስጠት ከጣሊያኖች እኩል ደመወዝ እንዲከፈላቸው ያደርጋሉ። በአሥራ ዘጠኝ ዓመታቸው የዕርዳታ ድርጅቱን ከፍተኛ ኃላፊነት ስራ ላይ በመሆን ጠንካራ ሰራተኛ ይሆናሉ።
በልጅነታቸው ጥለዋት የወጡት ሀገራቸውና ቤተሰቦቻቸው ናፍቆት አላስቀምጥ ሲላቸው ቤተሰቦቻቸውን ለመጠየቅ አገራቸው ይመለሳሉ። ልክ እንደተመለሱ አስደንጋጭ ችግር ይጋረጥባቸዋል። ቀደም ሲል ፈርተውት የወጡት ደርግ “ኢጣሊያን አገር በምትሠራበት የዕርዳታ ድርጅት ለወንበዴዎች ቪዛ እያዘጋጀች ትሰጣለች» በማለት ፓስፖርታቸውን ይነጥቋቸዋል።
ቆፍጣናዋ ወጣት ግን ጥርጣሬው መሠረተ ቢስ መሆኑንና ሰላማዊ ሰው መሆናቸውን የጣሊያን ኢምባሲ ከመሰከረላቸው በኋላ ፓስፖርታቸው ተመልሶ በአዲስ አበባ የመቆያ ጊዜያቸውን በማሳጠር ወደ ሮም ይመለሳሉ። እንደተመለሱም ከኢጣሊያ እርቀው ለመሰደድ ይወስናሉ። “ዘምዘም» የሚለውን መጠሪያ ስማቸውን ቤት ውስጥ ይጠሩበት በነበረው ስማቸው በሕጋዊ መንገድ አስቀይረው “ዘሚ» በሚል አዲስ ስም ወደ አሜሪካን አገር ተሸጋገሩ።
ከአምስት ዓመት የሮም ቆይታ በኋላ በሃያ ሁለት ዓመት ዕድሜያቸው አሜሪካን አገር የሎስ አንጀለስ ከተማ ነዋሪ ለመሆን ይበቃሉ። ኮዝሞቶሎጂስቷ ወጣት ዘሚ የኑስ ዳግም ለስደት ቢዳረጉም የአገረ አሜሪካ የኑሮ ዘይቤ እምብዛም እንግዳ አልሆነባቸውም። የካቴድራል ተማሪ ስለነበሩም የእንግሊዝኛ ቋንቋ ችግር ስላልነበረባቸው ከሕዝቡ ጋር ለመግባባትም አላዳገታቸውም።
ከሁሉም በላይ ደግሞ ኢጣሊያን አገር ይሰሩበት በነበረው ድርጅት ተባባሪ በነበረው የካቶሊክ ወጣት ማዕከል በፀሐፊነት እንዲሰሩ ምቹ ሁኔታ ስለተፈጠረላቸው በሥራ ፍለጋም አልተንገላቱም። በዚህ ሁኔታ ውስጥ እንዳሉ ከልጅነታቸው ጀምሮ በውስጣቸው ከሰረፀው ዝንባሌያቸው ጋር መገናኘት እንዳለባቸው ይወስናሉ፤ ከራሳቸው ጋርም ትግል ይገጥማሉ። ከዛም በዝንባሌያቸው የሥነ-ውበት የትምህርት ተቋም በመግባት የሙሉ ጊዜ ተማሪ ይሆናሉ። ፍላጐታቸውን ለማሳካት በፅናትና በትጋት ትምህርቱን በመከታተላቸውም ሦስት ዓመት የሚፈጀውን ትምህርት በአንድ ዓመት በማጠናቀቅ በዲፕሎማ ይመረቃሉ።
ከውስጣዊ ዝንባሌያቸው ጋር በመገናኘት በተግባራዊ ሥራውም አቅማቸውን ያጐለበቱት ወጣቷ ዘሚ በሁለት እግራቸው በሚገባ መቆማቸውን ካረጋገጡ በኋላ “ኒያና ኢንተርናሽናል» የሚባል የውበት ሳሎን በሎሳንጀለስ ይከፍታሉ። (“ኒያ» የአረብኛ ቃል ሲሆን “መልካም መንፈስ፣ መልካም ዕቅድ…» የሚል ትርጓሜ አለው) በከፈቱት የውበት ሳሎንም ለስምንት ሰዎች የሥራ ዕድል ይከፍታሉ።
በልጅነት የሙያ ዝንባሌያቸው በዕውቀት የታነጹትና በኢኮኖሚ አቅማቸው ያጠናከሩት ወይዘሮ ዘሚ የኑስ “ማን እንዳገር» በማለት ከአስራ ዘጠኝ ዓመት የስደት ህይወት በኋላ ጓዛቸውን ጠቅልለው በ1987ዓ.ም ወደ አገራቸው ይመለሳሉ።
ከዛም በሥነ-ውበት (ኮስሞቲክስ) ሙያ በአገራችን የመጀመሪያ የሆነውን “ኒያና የውበት ሥራ የሥልጠና ማዕከል» የተባለ ትምህርት ቤት በመክፈት ለሰባ አምስት ወገኖቻቸው የሥራ ዕድል ከመክፈታቸው ባለፈም ትምህርት ቤቱን ለጊዜውም ቢሆን እስከ አቋረጡበት 2004 ዓ.ም ድረስ ከስድስት ሺህ በላይ ባለሙያዎችን ማፍራት ችለዋል።
የሥልጠና ማዕከሉ ተግባራዊ እንቅስቃሴ በአደረገባቸው ዓመታት በተለይ ችግረኛ ወጣት ሴቶችንና በሴተኛ አዳሪነት ለተሰማሩ ወገኖች ነፃ የትምህርት ዕድል በመስጠት ከችግራቸው እንዲላቀቁ በማድረግ የወገን አለኝታነታቸውን አረጋግጠዋል። በተጨማሪም ከሚሰጡት ሙያዊ ሥልጠና ባለፈ ኤች አይ ቪን በመከላከሉ ረገድ አቅማቸው የፈቀደውን ሁሉ አስተዋፅኦ አድርገዋል።
በተጨማሪም ወቅታዊ በሆኑ አገራዊ ችግሮች ላይ በንቃት በመሣተፍ በጐ ተግባራትን ፈጽመዋል። ይህ በዚህ እንዳለ የሙያው አፍቃሪዎችን በሥነ-ውበት ሙያ ከማነፅ ባሻገር የውበትን ማራኪነት በመጠቀም “… በአይነቱ የተለየ በአገራችንም የመጀመሪያ የሆነ የብሔር፣ ብሔረሰቦችንና ሕዝቦችን ባህልና አልባሳት የሚያስተዋውቅ አውደ ርዕይ በ1997 ዓ.ም አዘጋጅተው በኤግዚቢሽን ማዕከል በሕዝብ እንዲታይ አደረጉ።”
ባለትዳርና የሁለት ልጆች እናት የሆኑት ወይዘሮ ዘሚ ልጃቸው የኦውቲዝም እክል እንዳለበት ያረጋግጣሉ። በዚህ ምክንያት ሕብረተሰቡ ስለኦቲዝም ማወቅ እንዳለበት ያስባሉ። እናም በተደራጀ መልክ ለዛ በአለው የአነጋገር ብቃታቸው ስለኦውቲዝም ያወቁትን ያሳውቃሉ። መገናኛ ብዙኃንም የኦውቲዝሟን “አምባሳደር» ተከትለው ስለ ኦውቲዝም አስተጋቡ።
በእርግጥ ወይዘሮ ዘሚ የኑስ የኦቲዝም እክል ያለበት ልጃቸው ከመሰል አቻዎቹ ጋር በአገሩና በወገኑ መካከል እንክብካቤና ትምህርት ማግኘት አለበት በሚል “…ልዩውንና ፈታኙን የኦቲዝም መጋረጃ በመግለጥ ለምን የብርሃን ጮራ እንዲፈነጥቅ አላደርግም…?» በማለት ወላጆች ለልጆቻቸው ትልቅ ነገር እንደሚመኙላቸው ሁሉ በኦቲዝም ምክንያት ልጅን በእግር ብረት ማሰር ምን ያህል ዘግናኝና ኢ-ሰብአዊ መሆኑን በየአጋጣሚው ማስተማሩን በትጋት ተያያዙት።
ጥረታቸው ፍሬ አፍርቶም የሕዝብ ንቅናቄ እንዲፈጠር ያደርጋሉ። መንግሥትም ድጋፉን ቸራቸው። እናም የሥነ ውበት ሥራ ሥልጠናውን እያካሄዱ በነበረበት ወቅት በተጓዳኝ የኦውቲዝምን ጉዳይ ወደ አንድ ታላቅ ታሪካዊ ምዕራፍ ያሸጋግሩታል።
በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የሆነ “ጆይ የኦውቲስቲክ ልጆች ማዕከል» የተባለ ተቋምም አቋቋሙ። በዚህም የበርካታ ኦውቲስቲክ ልጆችን የወደፊት ዕጣ ፈንታ የሚለውጥ፤ የእርሳቸው ቢጤ እናቶችን የሕይወት ዘመን ሰቀቀንና ሐዘን የሚቀርፍ ማዕከል በማቋቋም የሀገር ባለውለታነታቸውን አረጋገጡ። ማዕከሉ እ.ኤ.አ በ2002 ሥራውን የጀመረው የወይዘሮ ዘሚን ልጅ ጨምሮ በሌሎች ሦስት የኦውቲስቲክ ልጆች ነበር።
ያልታዩትን ተመልካች፤ አፍ ለሌላቸው አፍ ሆነው ቤታቸው ውስጥ ተዘግቶባቸው የእናት እዳ የሀገር ሸክም የተባሉትን ልጆች ለማስተማር በዘርፉ መምህራንን ከማሰልጠን ባለፈ በአዲስ አበባ አስር የመንግሥት ትምህርት ቤቶች አንድ አንድ ክፍል በማዘጋጀት የኦውቲስቲክ ልጆች በትምህርት ገበታ ላይ እንዲገኙ ማድረግ ችለዋል።
በኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ ዙሪያ በሚገኙ አምስት ትምህርት ቤቶችም የኦውቲዝም እክል ያለባቸው ሕፃናትም ከቤት ወጥተው የትምህርት ቤት ደጃፍን እንዲረግጡ ያደረጉት ወይዘሮ ዘሚ ለኦውቲስቲክ ልጆች ብቻ ሳይሆን እንደ እርሳቸው ልባቸው በልጆቻቸው ምክንያት ለተሰበረ እናቶችም አለኝታ ሆነዋል።
አሁን እጅ ያሰጣቸው ኮቪድ ወረርሽኝ ወደ ሃገራችን ከገባ ጊዜ ጀምሮ በሚሊኒየም የኮቪድ ህክምና ማእከል የተለያዩ ድጋፎችን ሲያደርጉ መቆየታቸው ታውቋል። ቅን ደግ ፍፁም የእናቶችን ልብ ጠጋኝ ለተቸገሩት ደራሽ በጎነትን የማይጠግቡት ጀግና እናት ክንዳቸው ታጠፈ፤ እስከ መቼ ይሆን ወገኖቻችንን በሽታው እያሳጣን የሚቀጥለው?
ታናሽ ታላቅ የማይመርጠው የስንቱን በር አንኳኩቶ ይሆን? ዛሬ ከጓዳ ያወጧቸው ልጆች እንባስ በምን ይታበስ ይሆን? የደጓን እናት ነፍስ በቀኙ ያኑርልን፤ ከደጋጎቹ ጎን ያስቀምጥልን እንጂ ምን ይባል ይሆን? ስለወይዘሮዋ ሞት የተለያዩ አካላት ካስተላለፉት የሀዘን መልእክቶች መካከል ጥቂቶቹን በመጥቀስ እንጨርስ።
የሴቶች፣ ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስትር ፊልሰን አብዱላሂ “ የኒያ ፋውንዴሽን እና የጆይ ኦቲዝም ማዕከል መሥራች ወይዘሮ ዘሚ የኑስ ከዚህ ዓለም በሞት መለየት ምክንያት የተሰማኝን ልባዊ ሃዘን እየገለፅኩ ለቤተሰቦቿና ወዳጅ ዘመዶቿ መፅናናትን እመኛለሁ!” ብለዋል።
የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ዶክተር ሊያ ታደሰም “ የሁለት ልጆች እናት ብትባልም የብዙ ሺዎች እናት በመሆን የእናቶችን እንባ በማበስ ደከመኝ የማትል ታለቅ ሰው፤ ታላቅ ጀግና፤ ታላቅ እንቁን፤ ዛሬ አጥተናል ሀዘኑ ከባድ ቢሆንም ለወዳጅ ዘመዶቿ መፅናናትን እመኛለሁ!” ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
“ያስፈራል! ያቺ ድምጽ ለሌላቸው ድምጽ ለመሆን የቆረጠች የብዙዎች ተስፋ — የእናትነት ቁንጮ፣ በእናቶች ቀን ሳናስበው እስከወዲያኛው አሸለበች፡፡ ውሸት እንዲያደርገው የተመኘሁት መርዶ — ከሞቶች ሁሉ የከፋው ሞት ሆነ!” ሲል ጋዜጠኛ እሸቱ ገለቱ ሀዘኑን ገልጿል።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ግንቦት 8/2013