ሀገሬ ኢትዮጵያ ማህፀነ ለምለም ለመሆኗ ማጠየቂያ የሆኑ በርካታ የቁርጥ ቀን ልጆች አፍርታልች። ሙያቸው ምንም ይሁን ምን “ስለሀገራችን ክፉ ነገር ከምንሰማና ከምናይ እውነቱን ተናግረን እንሞታለን” ያሉ ልጆች ሞልተዋታል። እውነታውን ለተቀረው የዓለማችን ህዝብ ያሳዩ፣ በአዓም አደባባይ ቆመው ሀገራችን እንዲህ ናት ያሉ፣ የእሷ እውነት ይህ ነው በማለት እየመሰከሩ ያሉ፣ ከራስ ማንነት ይልቅ ኢትዮጵያዊነት ውስጣቸው ያደገና የጎለበተ ብዙ ልጆች አሏት – ኢትዮጵያ።
አባይን መውቀስ ትተን የሀገር አድባርነቱን ሲሳይነቱን እንድንቀበል ያደረገን፣ የሀገር ሸማ የሀገር ልብስ የሆነውን አባይ እንደ መጎናፀፊያ እንለብሰው ዘንድ ተስፋ የሰነቅንበት የህዳሴ ግድባችን ሲጀመር የታችኛው ተፋሰስ ሀገሮች ከወሬ አልፈው አይተገብሩትም በሚል ሀሳብ ብዙም ቅር ባይሰኙም እንኳን በተባበረው ክንዳችን ግድቡን ጀምረን ከፍ…ከፍ እያለ ሲሄድ ዓይናቸው ደም መልበስ ጀመረ።
ያኔ መርዘኛ ሀሳባቸውን ለሀገራቸው ህዝቦችም ይሁን ለተቀረው ዓለም የተሳሳተ ግንዛቤ መስጠት፤ በዋናው መገናኛ ብዙሃኖችም (ማህበራዊውን ጨምሮ) “ግብፅ ውሃ ልታጣ ነው፣ ድርቅ ሊመጣ ነው” በሚል የሐሰት ወሬ ሽብር ከመንዛትም በላይ የሀገራችንን ስም የማጠልሸት ስራቸውን ሲሰሩ ቆይተዋል። ኢትዮጵያዊያን በሀገር ውስጥ ቋንቋዎች ብቻ በመስራታቸው፤ በእነሱም ቢሆን ተደራሽነታቸው ውሱን በመሆኑ ይህንን የሐሰት ፕሮፓጋንዳ ማምከን ሳይቻላቸው ቀርቷል።
ምንም እንኳን በወቅቱ የተሰማራችበት የስራ ዘርፍና እየተማረች ያለችው ትምህርት ህክምና ቢሆንም የሀገር ጉዳይ ሲነሳ ከፍቅር በላይ ምንም የለምና አቀላጥፋ መናገርና መፃፍ በምትችለው አረብኛ ቋንቋ አማካኝነት በማህበራዊ ሚዲያው ስለአባይ እውነቱን እንካችሁ ማለት ጀመረች።
የጀመረችው ሀሳብ በጥቂቱም ቢሆን ውጤት ሊያመጣ እንደሚችል የተረዳችው ይህች ሴት በተለያዩ የግድብ፣ የድንበር፣ የሠላም ስምምነቶች ወዘተ…ላይ የተፃፉ ጽሑፎችን፤ እንዲሁም በአባይ ላይ የተደረገውን የቀኝ ገዥዎች ስምምነት / ውል በማንበብ በቂ ግንዛቤ ለማግኘት ችላለች። በዚሁ መሰረትም ከተለያዩ አካላት ለሚቀርቡ ጥያቄዎች በቂ መልሶችን በመስጠትና እውነቱን አንድ ሁለት ብላ በማስረዳት በማህበራዊ ሚዲያዎች አደባባይ አርበኛ ለመሆን በቃች።
ይህ በተናጥል የሚከናወነው የዘመኑ አርበኝነት ተግባር አቶ ሱልጣን አባ ጊሣ በተባሉ ሰው አሰበሳቢነት በአንድ ላይ ሆነው አባይን በተመለከተ ለአረብ ሀገራት በቂ ግንዛቤን በማስጨበጥ ለሀገራቸው ያላቸውን አጋርነት አሳይተዋል። የዚህ ሁሉ ታሪክ ባለቤትና የማህበራዊ ሚዲያው አርበኛ ኢትዮጵያ ትወለድ እንጂ ከአንድ ዓመት እድሜዋ አንስቶ በሱዳን ያደገች መሆኗን ትናገራለች። ይህችን ታላቅ የዘመኑ አርበኛ ለዛሬ የሴቶች ገፅ አምዳችን እንግዳ አድርገናታል፤ መልካም ንባብ።
እጩ ዶክተር መካ አደም አሊ ትባላለች። ሁመራ ተወልዳ ሱዳን ያደገችው ወይዘሮ መካ ገና በአንድ ዓመቷ (በደርግ ጊዜ) ቤተሰቦቿ በስደት ወደ ሱዳን ከሄዱ በኋላ የእሷም እድገት በዚያው ይሆናል። የመጀመሪያና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን በገዳሪፍ የተማረች ሲሆን፤ የዩኒቨርሲቲ ትምህርቷንም በካርቱም (ሱዳን ዩኒቨርሲቲ) በመከታተል የመጀመሪያ ድግሪዋን በላብራቶሪ ሳይንስ አግኝታለች። ከዚያም ወደ እምትናፍቃት ትውልድ ሀገሯ በመምጣትም በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ስራ ጀመረች።
የተወሰኑ ዓመታትን በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ከሰራች በኋላ ሁለተኛ ድግሪዋን በማይክሮ ባዮሎጂ ለመስራት ወደ ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ አቀናች። ፕሮግራሙን እንዳጠናቀቀችም በሚዛን-ቴፒ ዩኒቨርሲቲ ለሶሰት ዓመታት አስተማረች። በአሁኑ ወቅትም በይርጋለም ሜዲካል ኮሌጀ በመምህርነት በማገልገል ላይ ትገኛለች።
እንደ አውሮፓዊያን አቆጣጠር በ1978 የተወለደቸው ወይዘሮ መካ ባለትዳርና የአንድ ልጅ እናት ስትሆን ከስራዋ በተጓዳኝ የፒኤች.ዲ ትምህርቷን በመከታተል ላይ ስትሆን፤ ለማጠናቀቅም የመመረቂያ ጥናቷን (ዲዘርቴሽን) በመስራት ላይ ትገኛለች። መካ በአዲስ አበባና ሉንድ ዩኒቨርሲቲ ትብብር የሚካሄደውን ፕሮግራም እየተከታተለች መሆኗን የገለፀች ሲሆን፤ የምርምር ስራዋንም ሀንሰን ሪሰርች ኢንስቲትዩት ስፖንሰር እንደሚያደርገው ታስረዳለች።
ለዶክትሬት ዲግሪዋ ማሟያ እየሰራች ያለችው ጥናት ካንሰር በተለይም የደም ካንሰር ላይ መሆኑን፤ በአገራችን የደም ካንሰርን የመንከባከብና መከላከል ስራው (አቅም) ምን ደረጃ ላይ ይገኛል? በሚሉ ዋና ዋና ሀሳቦች ላይ እንደሚያተኩር የገለፀች ሲሆን፤ በህይወቷ ለውጥ የሚያመጡ ስራዎችን መስራት የሚያስደስታት መሆኑንም ትናገራለች።
አማርኛ፣ ዓረቢኛ፣ እንግሊዝኛና ትግሪኛ ተናጋሪ የሆነችው መካ እንደምትናገረው ከሆነ ምንም እንኳን በስደት ሱዳን ቢኖሩም ቤተሰቦቿ አንድም ቀን ሀገራቸው ኢትዮጵያ መሆኗን ዘንግተው አያውቁም። ሁልጊዜ “ሀገራችን ሄደን ይኼንን እናደርጋለን፤ የሀገራችን አኗኗር ይኼን ይመስላል፤ ሀገራችን ፍቅርና መተሳሰብ የሞላባት ናት” ከማለትና በፍፁም ኢትዮጵያዊነት ከመፅናት በስተቀር አንድም ቀን ስለብሄርና መከፋፈል ሲያወሩ ተሰምተው አያውቁም፤ ልጆቻቸውንም ያሳደጉት በዚሁ ፍፁም ኢትዮጵያዊነት ስሜት ነው።
̋እኛ ቤት ስለብሄር አይደለም ሙስሊም ክርስቲያን የሚለውን ሀሳብ እንኳን አናውቅም ነበር” የምትለው ወይዘሮ መካ ሱዳን ውስጥ ካሉ ኢትዮጵያዊያን ጋር አንድ በመሆን ስሜት ውስጥ ይኖሩ እንደ ነበርም ትናገራለች።
አጎት፣ አክስት፣ አያት፣ የአጎት ልጆች፣ እህት ወንድሞቿ አንድ ላይ ሆነው ያደጉባት ጋዳሪፍ ለመካ የልጅነት ትዝታዋ ደማቅና ሙሉ ኢትዮጵያዊነትን የተጎናፀፈ እንዲሆንላት ማድረጉን በፈገግታ ትናገራለች። ወደ ትውልድ ሀገሯ ከገባች አስራ አምስት ዓመታተን ያስቆጠረችው ይህች ጠንካራ ሴት ለሀገሯ ካላት ፍቅር የተነሳ አማርኛን በቀላሉ ለመልመድ ጊዜ እንዳልወሰደባትም ነው የምታስረዳው።
ለዩኒቨርሲቲ ትምህርት ወደ ካርቱም ባቀናችበት ወቅት አባይ በመሀል ከተማው ሲገማሸር ስታይ፤ አባይ ዙሪያ ላይ የተገነቡ መዝናኛዎችን ስትመለከት፤ ትልልቅ እርሻዎች በአባይ ውሃ ሲለሙ ስታይ ”አባይ የሀገሬ ውሃ የሀገሬ ህዝብ እየተራበ አፈሩን ይዘህ እየመጣህ ሌሎችን ታጠግባለህ̋ የሚል ከፍተኛ ቁጭት ስሜት ውስጧ ሲብከነከን እንደነበር ነው መካ የምትናገረው።
̋እንዲያውም በልጅነቴ አንዲት የጂኦግራፊ መምህርት ኢትዮዽያ ተራራማ ሀገር ስለሆነች ወንዙን ብትገድበው አጥለቅልቆ ያጠፋታል። ለዚህም ነው ግድብ ለመስራት የማትደፍረው ስትል ሰማኋት።” ትላለች። በወሬ ብቻ የምታውቃት ውድ ሀገሯ ውሃውን እንኳን ለመገደብ ምንም አቅም እንዳልነበራት ስታስብ የልጅነት ልቧ ሰርቶ የመለወጥን ተስፋ ሰንቆ ችግርን መሻገር እንደሚቻል እያሰበ፤ እሷም ጠንክራ ለሀገሯ ማድረግ የሚገባትን ለማድረግ አስፈላጊውን ዝግጅት ሁሉ ስታደርግ መቆየቷን ትናገራለች።
እጩ ዶክተር መካ በተለይም ስለኢትዮ-ሱዳን ድንበርና ስለ ህዳሴው ግድብ በዓረብኛ በምትፅፋቸው ምሁራዊ አርቲክሎቿ ትታወቃለች፤ መካ አደም በአሁኑ ወቅት በኢትዮ-ሱዳን ድንበር ጉዳዮች በአማርኛ የተፃፉትን መፅሀፎች ወደ ዓረብኛ በመተርጎም የኢትዮጵያን እውነታ ለዓረቡ ዓለም ለማስተዋወቅ እየሰራች ትገኛለች። ይህች ብርቱ ሴት የቤተሰብ ሀላፊነት፣ ትምህርትና ሌሎች የተለያዩ ድርብርብ ስራዎች ቢኖሩባትም ከሀገር የሚበልጥ የለምና ለሀገሯ ዋስ ጠበቃ ሆና እየሰራች ነው።
ከእናት ሀገሯ ማህፀን የሚወጣው ውሃ ሀገሯ ባለመብት እንዳልሆነች ሁሉ ከተጠቃሚነት መገለሏን በተመለከተም በተለያዩ መድረኮች ስትሰማ፥ ግብፃዊያኑ ምንም አያደርጉም በሚል ንቀት የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ሁሉ ስታይ እንደ ክፉ ቁስል ሲቆጠቁጣት ኖሯል። ይህም በተቻላት መጠን ይህ ስህተት መሆኑንና እውነታዎችን ለዓለም ለማሳየት እንድትተጋ እድሉን ፈጠረላት፤ ወደ ተግባርም እንድትገባ አደረጋት።
ኢትዮጵያ «…ባልተጠራችበት የቅኝ ግዛት ውል ላይ» ተቀምጣ ልትደራደር አትችልም። ይህ ውል ሲፈርም በወቅቱ የነበሩትን የሀገሪቱን መሪ ያላማከለ፣ ያልጋበዘ የነበረ መሆኑ ንቀት የተሞላ አካሄዳቸው እንደሚያናድዳት የምትናገረው መካ ሀገሪቱ ያላትን የተፈጥሮ ሀብት እንዳትጠቀም የሚያደርጉ በርካታ ድርጊቶች ቢኖሩም ግን ኢትዮዽያዊያን እያንዳንዱን የክፋት ሀሳብ ወደ ጎን በመተው በተባበረ ክንድ ስራ ላይ ማተኮር የሚገባቸው መሆኑን በአንክሮ ታሳስባለች።
እጩ ዶክተር መካ ሱዳኖች በመስኖ የሚያለሟቸው ትልልቅ እርሻዎች፤ አባይን እየተከተሉ የሚመሰረቱ በርካታ ከተሞች፤ በሱዳን መዲና ካርቱም ላይ ስመጥር የሆኑ በርካታ ቱሪስቶች የሚጎበኛቸው ሆቴሎች የተሰሩት እናት ሀገሩን አልፎ በሚሄደው አባይ ላይ ሆና ሳለ እኛ የኛ የሆነውን፤ ለዚያውም በአቅማችን ገንብተን ፍፃሜው ላይ ልንደርስ ባቀድነው ወንዛችን እንዳንጠቀም በርካቶች ተቀናቃኞቻችን መሆናቸውን እያወቅን ለምን አንድ መሆን አልቻልንም ስትልም ትጠይቃለች።
ሁሉም ሀገራት ለራሳቸው የሚመቻቸውን ነገር ነው ቅድሚያ የሚያስቀምጡት። ይህንን መረዳት ያስፈልጋል። ለኢትዮዽያ ችግር ከኢትዮጵያዊያን በላይ ማንም መፍትሄ የማይሰጥ መሆኑንም እንዲሁ። ኢትዮጵያዊያን የውስጥ ችግሮችን በሰከነ መንፈስ በመወያየትና በመፍታት አንድነት መፍጠር በውጭ የሚያንዣብቡ ጠላቶች እድል እንዳያገኙ ማድረግ የሚቻል መሆኑንና እንደሚገባም ጠቁማ ቀጠሮ ሳያስፈልግ ከዛሬ ጀምሮ ህዝቡ በአንድ መንፈስ ስለሠላምና ስለፍቅር ማሰብ እንደሚገባው ደጋግማ ታሳስባለች።
”ጠላት በድፍረት አፉን ሞልቶ የሚናገረው፤ የሚፎክረው፤ በገዛ የሀገራችን ወንዝ ሊያስፈራራ የሚፈልገው መከፋፈላችንንና መበታተናችንን ተመልክቶ ነው። ሁሉም እንደፈለገ እየተነሳ አፉን የሚያላቅቅባት ሀገራችን የስጋት ሀገር ለመሆኗ ተጠያቂዎቹ ራሳችን ነን” የምትለው እጩ ዶክተሯ ህዝቡም ይኼንን ተገንዝቦ ወደ አንድነት መምጣት ያለበት መሆኑን ነው የምታሳስበው።
በጥንካሬ የፈለጉትን ነገር ለመስራት መታተር፤ የፈለጉት ደረጃ ላይ ለመድረስ ፆታን የማይጠይቅ መሆኑን፤ ፍፁም የልብ ቅንነትና ፍላጎትን፣ ያላሰለሰ የግል ጥረትን ብቻ የሚፈልግ መሆኑን በወይዘሮ (እጩ ዶክተር) መካ ታሪክ አይተናል። ልክ እንደ ዶክተሯ ሁሉ ሁላችንም የየራሳችንን ጡብ እያስቀመጥን ሀገራችንን በከፍታው ላይ እናስቀምጣት የሚለው የሁላችንም ቃልና እምነት ሊሆን ይገባል።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ግንቦት 1/2013