አስመረት ብስራት
መቼም በዓል ሲነሳ ለድምቀቱ ሴቶች ግንባር ቀደሞቹ ናቸው። በበዓላት ወቅት ቤት ውስጥ የሚሰሩ ባህላዊ ምግቦችና መጠጦች የሴቶችን እጅ የሚሹ በመሆናቸው የስራ ጫናውን ከባድ እንደሚያደርገውም ይታመናል። በተለይ በስራ ኃላፊነት ላይ ያሉ ሴቶች፤ የቤትና የልጆች ኃላፊነት ታክሎበት በዓል ሲመጣ ደግሞ ተወርቶ የማያልቅ ድካምን ይዞ ይከሰትባቸዋል።
ሴትነት ተፈጥሮ የሚለግሰው ጥንካሬና አብሮ መኖሩ ይሄንን ድርብርብ ኃላፊነት ለመወጣት ጫንቃን ደንደን ቢያደርግም በዓል ሲነሳ ከቤት ፅዳት ጀምሮ፤ ለበአል ማድመቂያ የሚያስፈልገውን ሸቀጥ መግዛት፤ ቤት ያፈራውን መስራቱ፤ መስተንግዶው ሁሉም የሴት ኃላፊነት ነው። በተለይ በተለያዩ የስራ ዘርፎች ላይ ተሰማርተው የሚያሳልፉ ሴቶች ደግሞ የሚጠበቅባቸውን የስራ ኃላፊነት በተቋማቸው ካበረከቱ በኋላ የቤቱ ደግሞ እንዳይጎድል እንቅልፋቸውን አጥተው ሌሊቱን ሙሉ ሲሰሩ እንደሚያድሩ ያነጋገርናቸው በኃላፊነት ላይ የሚገኙ ሴቶች ይናገራሉ።
የሀገራችን ባህል ሴቶችን ለማጀት ወንዶችን ለአደባባይ ብሎ የማጀቱ ስራ ለሴቶች የተተወ ቢሆንም አሁን አሁን ግን ሴቶች የማጀቱንም የአደባባዩንም እኩል በማስኬድ ላይ ይገኛሉ። በተቻላቸው አቅም ተጣጥረው የሚደርሱበት ስኬት ላይ በርካቶች ኃላፊነታቸውን በአግባቡ የመወጣት ስኬታማ ስራዎች ይሰራሉ።
ከእነዚህ ሰኬታም የስራ ኃላፊዎች መካከል የብርሃን ባንክ የሰው ሀብት አስተዳደር ኃላፊነት ቦታ ላይ የሚሰሩት ወይዘሮ ትዝታ እስራኤል አንዷ ናቸው። ወይዘሮዋ ባለትዳርና የሁለት ልጆች እናት ሲሆኑ በማሰተርስ ዲግሪ ደረጃ የተማሩና በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች የሰሩ ሴት ናቸው። ወይዘሮ ትዝታ ማንኛዋም ድርብርብ ኃላፊነት ያለባት ሴት ኃላፊነቶቿን በፕሮግራም እያስተካከለች እንደምትሰራው ሁሉ እሳቸውም አኗኗራቸውን ከኃላፊነታቸው ጋር አመቻችተው መኖርን እንደተለማመዱት ይናገራሉ።
‹‹በአመት በአል ቀድሞ አስፈላጊውን ነገር መግዛት ትልቁ የቢሮ ሰራተኛ ሴት ፈተና ነው፤ ስራ ላይ ከሰኞ እስከ ቅዳሜ የምትውለው ሴት በተጨናነቀ ሰአት አስፈላጊውን ነገር በሙሉ ለሟሟላት ጭንቀት ላይ ትወድቃለች›› የሚሉት ወይዘሮ ትዝታ፤ በተለይ ቤት ውስጥ ረዳት ሳይኖር አድካሚና ረጅም ሰአት የሚወስዱ ለበአል የሚዘጋጁ ምግቦችን ማዘጋጀት አስቸጋሪነት ግን የማይቀር መሆኑን ይናገራሉ።
የበዓል ዋዜማን በሚሰሩበት አከባቢ የማክበር ልምድ መኖሩን የሚናገሩት ወይዘሮዋ፤ የስራ ቦታ በዓልን አጠናቀው ለቤቱ በዓል ማድመቂያ ለመገዛዛት ይወጣሉ። ምንም እንኳን የሚረዳ ሰው ቤት ውስጥ ቢኖርም እማወሪት ያለተጎማለለችበት ጓዳና ሙያዋን ያላከለችበት የባህል ምግብ ለበአል አይቀርብምና ውጤቱ አስደሳች የሆነውን የበአል ዝግጅት ለማጠናቀቅ እስከ እኩለ ሌሊት መንደፋደፍ ግድ የሚል መሆኑን ይገልፃሉ።
‹‹ልጆች ይዞ ስራ መሰራት በጣም ከባድ ነው። ሴት መሆን በራሱ ሁሉን መቻል ስለሆነ ሁሉን እችላለሁ። ባለቤቴ በብዛት የፊልድ ስራ ላይ በመሆኑ በአብዛኛው ኃላፊነቴን እወጣለው፡፡ በተለይ ልጆች ማስጠናት የበአል ስራ መስራት ሁሉ ነገር የኔና የረዳቴ ነው›› ይላሉ።
በአል ሲመጣ የስራም የቤትም ኃላፊነቱ ሴቶች ላይ ቢከብድም ያንን በአግባቡ የመወጣት አቅም በተፈጥሮ በመታደሉ ቀለል ይላል የሚሉት ወይዘሮ ትዝታ፤ መልካም ምኞታቸውን በማስተላለፍ ውይይታችንን አብቅተናል። ‹‹ለመላው የአትዮዽያ ህዝብ እንኳን አደረሳችሁ። ለሀገሪቱ ህዝቦች በሙሉ መልካም ነገር ይገጥማቸው ዘንድ እመኛለሁ። መላው የክርስትና እምነት ተከታይ እንኳን ፆመ ልጓሙን ፈታላችሁ። በአሉ የሰላም የደስታ የፍቅርና የመተሳሰብ ይሁንላችሁ›› ብለዋል።
ሌላዋ በአል አንቺ ቤት ምን ይመስላል ያልናት ሴት ወይዘሮ ብረክታዊተ ጥጋቡ ትባላለች። ይች ሴት የህፃናት ፊልሞችንና መፅሃፍቶችን የምታዘጋጅ በበርካታ የስራ ጫና ውስጥ ቀኖቿን የምታሳልፍ ሴት ናት። ወይዘሮ ብሩክታዊት ቤተሰብ መስርታ ወልዳ ከብዳ ብትኖርም የቤት ወስጥ የበዓል ጉድጉድ ብዙም የሚያሳስባት አትመስልም። በዓል ለሷ ከቤተሰብ ጋር ጥሩ ጊዜ እንደማሳለፊያ መልካም አጋጣሚ ነው የምትቆጥረው።
‹‹በዓል ልጆች አያቶቻቸውን የሚጠይቁበት ከቤተሰብ ጋር ሰብሰብ ብሎ ብዙ ቁም ነገር የሚቀሰምበት፤ ልጆችን ከሰፊው ቤተሰብ ጋር የምናስተሳስርበት፤ ለህይወት ዘመናቸው የህይወት ስንቅ የሚያስቀመጡበትን ገጠመኝ የሚፈጠርበት በመሆኑ በዓልን ሳስብ ደስታ ይሰማኛል›› የምትለው ወይዘሮዋ፤ እሷና ቤተሰቧ በራቸውን ዘግተው ወላጆቻቸው ጋር ስለሚያሳልፉ የቤት ውስጥ ውጣ ውረድ በአብዛኛው ለበአል ጫና እንደማይሆንባት ታስረዳለች። ምንም እንኳን ሁሉም ሴቶች በሚባል ደረጃ የቤት ውስጥ ኃላፊነቶች ቢበዙባቸውም ስራቸውን ያለምንም መዘናጋት ስለሚሰሩ ኃላፊነቶችን በአግባቡ መከወን አይከብዳቸውም የምትለው ወይዘሮ ብሩክታዊት፤ ሴት ካሰበችና ለመስራት ከወሰነች መስራት የሚከብዳት ነገር የለም ትላለች።
ይህ ሲባል ግን ሁሉንም ነገር ለሴቶቹ ብቻ በመተው የስራ ጫና እንዲጎዳቸው ከማደረግ ይልቅ ህይወት የጋራ ናትና በመተጋገዝ ደስታችን ያለድካም ሙሉ እንዲሆን ማድረግ የሚገባ መሆኑን ታሳስባለች። ‹‹በአሉ የሰላም የፍቅር የፀጋ የበረከት እንዲሆን አመኛለው። በዚህ በአል ማህበራዊ ትስስራችን ጎልብቶ የሚጠብቅበት፤ ሰላምና እርቅ ወርዶ የአንድነት አየር የምንትነፍስበት ይሁንልን›› በማለት መልካም ምኞቷን አስተላልፋለች።
ለዚህ ፅሁፍ የመጨረሻዋ እንግዳችን ወይዘሮ አልማዝ ተስፋዬ በኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጀት የፋይናንስና የግዢ ዳይሬክተር ናቸው። ወይዘሮ አልማዝ አመት በአል በኃላፊነት ላይ ለሚገኙ ሴቶች እጅግ ከባድ ነው ይሉናል። ወንዶችና ሴቶች ሲወዳደሩ ወንዱ ቤት ሄዶ ለመዝናናትና ተዘጋጅቶ የሚጠብቀውን ለመመገብ ሲዘጋጅ ሴቷ ግን ገና የቤቱ ውስጥ ኃላፊነትን ለመወጣት ወደ ጓዳዋ ጎራ እንደምትል ይገልፃሉ፡፡
ሀላፊነት ላይ ያሉ ሴቶች በሚያገለግሉበት ተቋም ትልቅ ሀላፊነት በመወጣት ሲሰሩ ከዋሉ በኋላ የቤቱን ማስከተላቸው ሴቶች ድርብርብ ሀላፊነቶችን በብቃት ለመወጣት ተፈጥሮ እንዳደላቸው ይናገራሉ። በአብዛኛው ወንዶች ስራ አያግዙም፤ አስተዳደጋቸውም በዚህ አይነት የአኗኗር ሁኔታ እንዳይኖሩ አድርጓቸዋል የሚሉት ወይዘሮ አልማዝ ሴቶች ግን የባህሉንም ተፅእኖ በትግል አሳልፈው ውጤታማ ስራ ሲሰሩ መታየታቸው የሚያኮራ መሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡ ሴቶች በልጅነታቸው ሲያድጉ እንኳን ቤተሰቦቻቸውን በስራ እየደገፉ ሀላፊነትን ከልጅነታቸው ጀምረው እየተለማመዱ ስለሚያድጉ ሀላፊነትን መወጣት ባይከብዳቸውም ቤት ውስጥ ልጆችም ባሎችም መንከባከብ በጣም ከባድ ሀላፊነት እንደሆነ ያስረዳሉ።
‹‹በማንኛውም ኃላፊነት ቦታ ላይ ያሉ አለቆች ሴቶች ትውልድ እያሳደጉ መሆኑን መረዳት ይኖርባቸዋል።›› የሚሉት ወይዘሮ አልማዘ፤ ድርብርብ ኃላፊነቶቻቸውን በመወጣት ሂደት ውስጥ ጫና እንዳይበዛባቸው እገዛ ሊደረግላቸው እንደሚገባ ይናገራሉ።
‹‹በአል በእኔ ቤት አቅም በፈቀደው ነገር በሙሉ ተሟልቶ ይከበራል፤ ያንን ለማድረግ ደግሞ ባገኘሁት ትርፍ ጊዜ በሙሉ ቀደም ብዬ በመዘጋጀት ጫናዎችን ለመቀነስ እሞክራለሁ፤ እንደዚህም ሆኖ ግን በዋዜማው ያለው ዝግጅት በአሉ ደምቆ ሲታይ የሚያረካ ቢሆንም እጅግ አድካሚ ነው›› ይላሉ። እንደ ወይዘሮ አልማዝ ገለፃ፤ በአሉም ኑሮውም የሚደምቀው በመደጋገፍ ነውና ወንዶቻችን የቤት ራስ መሆናችሁን አውቀው ድጋፍ ማሳየት ይኖርባቸዋል።
‹‹እንኳን ለጌታችን ለመድሃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የትንሳኤ በአል በሰላም አደረሳችሁ። መላው ህዝበ ክርስቲያን በአሉ የሰላም ያደርግላችሁ፤ ለሀገራችን ህዝቦች ሰላም መከባበር ፍቅርና መረዳዳት የሚታይበት በእምነቱ የደህነት በአል በመሆኑ ለሀገራችን ፈውስ የሚመጣበት ያደርግልን ዘንድ ምኞቴ ነው።›› በማለት የመልካም ምኞታቸውን ገልፀዋል።
ሴትነት ውበትም ድምቀትም መሆኑ በሚታይበት አመት በአል እናቶቻችንን፤ እህቶቻችንን፤ ሚስቶቻችንን፤ ሴት ልጆቻችንን ባለማድከም በአቅም በመተጋገዝ ጫናን የቀነሰ በአል ይሆን ዘንድ እኛም ምኞታችን ነው። በአሉ ለሁሉም ሰላም ደስታን የሚያመጣ የፍቅርና የመከባበር የመተሳሰብ ይሆን ዘንድ መልካም ምኞታችን ነው።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 24/2013