አሁን ላይ በአገራችን በየአቅጣጫ እየተስተዋለ ያለው ሁኔታ ሰከን ብሎ ማሰብን ይጠይቃል:: አንዳንድ የፖለቲካ ቁማርተኞች አገሪቱን በአራቱም ማዕዘናት ችግር ውስጥ ለመክተት አልመው እየተቀሳቀሱ መሆኑን መገንዘብን ይሻል:: በአቋራጭ ወደ ሥልጣን ለመምጣት የሚሹ ኃይሎች አገር የማተራመስ አጀንዳን ቀርጽው እየሰሩ እንደሆነ ነጋሪ የማያሻው መሆኑን እኩይ ተግባራቸው በግልጽ እየታየ ይገኛል:: እነዚህ ኃይሎች በአገራችን በአራቱም ማዕዘን እሳት እየለኮሱ ብሔርን ከብሔር፣ ሃይማኖትን ከሃይማኖት ጋር በማጋጨት የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት የሚሯሯጡ ናቸው:: እንዲሁም አገርን በማበጣበጥ ኢትዮጵያን ለማዳከም የሚያደርጉት እኩይ ድርጊት መገለጫቸው ነው::
አሁን ላይ በአገራችን እየተከሰቱ ያሉትን ግጭቶችና ጥቃቶች በመመልከት የፖለቲካ ቁማርተኞች በሰላም፣ በፍቅር፣ በመተሳሰብና በአንድነት የኖርን ሕዝብ፣ በብሔርና በሃይማኖት በመከፋፈል እርስ በእርሰ ግጭት ውስጥ እንዲገባ ለማድረግ የማይሸርቡት ሴራና ተንኮል የሌለ መሆኑን ማንም ሳይነግረን መገንዘብ ችለናል:: እነኝህ ኃይሎች የራሳቸውን ዓላማ ከብሔር ወይም ከሃይማኖት ጋር በማስጠጋት አገርን ለማበጣበጥና ለማፍረስ የሚፈጸሙት እኩይ ድርጊት መገለጫቸው ነው:: ዘር እየመረጡ እኩይ ድርጊት የሚፈጸሙት የጥፋት ኃይሎች የህወሓት አገር የማፍረስ የዛር ውላጅ የተዋረሳቸው፤ ለሰላም፣ ለሕዝብ አንድነትና ወንድማማችነት ደንታ የሌላቸው መሆኑን ላፍታም መዘንጋት የለበትም::
እነዚህ ኃይሎች ለሕዝቡ አሳቢ በመምሰል አገርን ወዳልተፈለገ አቅጣጫ ለመምራት የሚፈልጉ ናቸው::
እነዚህ ኃይሎች ለእራሳቸው በሚበጅ የፖለቲካ መንገድ ለመጓዝ በወገኖቻቸው ደም ላይ መረማመድ ይሻሉ:: እኩይ ተግባራቸው ለበርካታ ዓመታት በእቅድ ሲሰራበት የቆየ የፖለቲካ ደባ ነው:: ይህ ደባ ውስጥ ውስጡን ሲቀጣጠል ቆይቶ ዛሬ ላይ በአገራችን ምድር እየተንሰራፋ የምናየውን ግጭትና ጥቃት አሁን ያለውን መልክ እየያዘ ይገኛል::
አገራችን እንደ ሸረሪት ድር በተሸረበው የሤራና ደባ ፖለቲካ ቢሆንማ ኖሮ እስከ ዛሬ አገራችንም እንደሶሪያና የመን ፈራርሳ እንዳልነበረች ትሆን ነበር:: ሆኖም የኢትዮጵያውያን የቆየው የመተባበርና የወዳጅነት እሴት ጠብቆን እስካሁን አዝልቆናል::
በተለይ ኢትዮጵያ ብዙ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በአንድነት፣ በፍቅር፣ በመተሳሰብና በመቻቻል የሚኖሩባት ሀገር ናት:: በዚህም በዓለም አደባባይ እንደ ተምሳሌት የምትቆጠር አገር አድርጓታል:: በመሆኑም በተለያዩ ምክንያቶች ይህቺ አገር ለማፈራረስ ጥረት በሚያደርጉት ኃይሎች ጥርስ ውስጥ ገብታለች:: የኢትዮጵያ ማደግና መልማትን እንደ ስጋት የሚያዩ አገራት ሁሌም ቢሆን የኢትዮጵያን ሰላምና ብልጽግናን አይመኙም::
በተለይ አገራችን ታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ለመገንባት በተባበረ ክንድ ታጥቃ ከተነሳችበት ጊዜ ጅምሮ ዓይናቸው የቀላ ብዙ አገራት አሉ:: በግልጽ አቋማቸውን የገለጹት ግብፅና ሱዳንም ቢሆንም የህዳሴው ግድብ ግንባታ ጉዳት እንደማያስከትልባቸውም እያወቁ የራስ ምታት አድርገው እንደቆጠሩት በሦስትዮሹ የህዳሴ ግድብ ድርድር ከሚያሳዩት አቋም መለዋወጥ መረዳት ይቻላል::
ከጅምሩ ጀምሮ እስካሁን ድረስ በተለይ ግብጽ የግድቡን ግንባታም ለማጓተትና ለማስተጓጎል ያላደረገችው ጥረት የለም፤ አልተሳካላትም እንጂ:: ሱዳን በሦስተኛ ወገን ግፊትና ፍላጎት የኢትዮጵያን ድንበር ጥሳ ገብታለች:: ድርድሩ ፍሬ አልባ እንዲሆን ተለዋዋጭ አቋም ያሳያሉ::
በተለይ ግብጽ በዚህ ብቻ አልቆመችም በኢትዮጵያ የእጅ አዙር ሴራ ጠንሳሽነት በኢትዮጵያ የእርስ በእርስ ግጭት ለመፍጠር ሞክራለች፤ አሁንም አላረፈችም:: ለዚህም የእሷ ምሁራና ማህበራዊ ሚዲያ አንቂዎች የሚሰጧቸው አስተያየቶች ህያው ምስክሮች ናቸው:: በደካማ ጎናችን በመግባት የኢትዮጵያውያን ሰላምና የሕዝቦቿ ደህንነት እንዲናጋ መሻታቸውን የሚያሳዩ ናቸው:: ታዲያ በአገራችን አሁናዊ ትኩሳት ውስጥ እጃቸው እንደሚኖርበት ምንም ጥርጥር የለውም:: በተለይ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ሁለተኛ ዙር የውሃ ሙሌትን ለማስተጓጎል የማይፈነቅሉት ድንጋይ እንደማይኖር ከዚህ ቀደም ሲያደርጓቸው ከነበሩ ዲፕሎማሲ ጫናዎችና ስውር እንቅስቃሴዎች መረዳት አያዳግትም::
‹‹ነገርን ከሥሩ ውሃን ከጥሩ›› እንዲሉ አበው ግብጽ በኢትዮጵያ ላይ በእጅ አዙር እጇን እያስገባች መሆኑን መገንዘብ ያሻል:: ያም ሆነ ይህ እነዚህ በውስጥና በውጭ አገር ያሉ የጥፋት ኃይሎች የሚሰሩት እኩይ ተግባርን ከወዲሁ መከላከልና መቆጣጠር አንገብጋቢ ጉዳይ ነው:: በአንድነትና በአብሮነት ላይ የተጋመደው መሠረታችን እንዲህ በቀላሉ እነሱ እንዳሰቡትና እንዳለሙት በአንዴ ጊዜ ሊንዱትና ሊያደፈርሱት ባይችሉም የሚፈጥሩት ተጽዕኖ ግን በቀላሉ ሊታይ አይገባውም:: በተለይ አሁን አሁን እየተቀየሰ ያለው ስልት ደግሞ እጅግ የባሰና የከፋ ነው:: የንጹሃን የወገኖቻችንን ደም በማፍሰስ አንዱን ብሔር ከሌላው ብሔር ለማጋጭት የሚያደርጉት የፖለቲካ ሴራ እጅግ የሚያሳምምና የአገርን ህልውና የሚፈታተን ነው::
የቆየውን የሕዝቦች የመተሳሰብ፣ አብሮ የመኖር መልካም እሴትና አገራዊ አንድነትን ለማላላት የሚሰሩ የጥፋት ኃይሎች የኋላ ኋላ የተጋረዱበት መጋረጃ ተገልጦ ማንነታቸው ይፋ መውጣቱ አይቀሬ ነው:: ለብዙ ዓመታት ታልሞበትና ታስቦበት እየተሰራ ያለን ደባና ሴራ ማጋለጥና እነዚህ አካላት አደብ ማሲያዝ የሚችለው ደግሞ የመንግሥትና ሕዝቡ የተባበረ ክንድ ነው:: ከሕዝብ ዓይንና ጆሮ የሚያመልጥ ምንም ዓይነት ነገር የለም፤ አይኖርምም::
ለጥፋት የተሰማሩ በአገር ውስጥ ሆነ በውጭ ያሉ ኃይሎች ዘር ለይተው በወገን እየፈጸሙት ያለው ግፍ ዛሬ ለማስቆም ከሁላችንም ከእያንዳንዳችን የሚጠበቅ ኃላፊነት ነው:: ዛሬ ደማቸው በከንቱ እየፈሰሰ ያለ ወገኖቻችን ላይ መታደግ ባንችልም ለነገ ግን ተመሳሳይ ድርጊቶች እንዳይከሰቱ መትጋት ይጠበቅብናል:: ምክንያቱም ዛሬ በአንድ ዘር ላይ አተኮሩ እንጂ ቀስ በቀስ ወደ ሌሎቹ ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ላይ መዞሩ የማይቀር ጉዳይ ነው:: እንዲሁም በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ የአገር ሰላምና ጸጥታ መናጋት በኢኮኖሚያችንና በኑሮችን ላይ የሚፈጥረው ጫና ቀላል አይደለም::
አገር ለማፍረስ የሚጥሩ ኃይሎች ድብቅ አጀንዳ ማጋለጥ ያስፈልጋል:: ሲፈልጉ በብሔር ሲያሻቸው ከሃይማኖት ጋር ዓላማቸውን በማጣመር ኢትዮጵያን አኪልዳማ ለማድረግ የሚሰሩ ኃይሎችን በጋራና በቁርጠኝነት ካልተጋፈጥናቸው ነገ ልንቆጣጠረው የማንችለው ጦስ ሊያስከትል እንደሚችል መገንዘብ ያሻል:: መንግሥት ለግጭት መንስኤ ሊሆኑ የሚችሉ ጉዳዮችንና አካባቢዎችን በማጥናት ዘላቂ መፍትሄ መስጠት አለበት:: እንዲሁም የጥፋት ኃይሎቹን ደግሞ ዱካቸውን እየተከታተለ የማያዳግም እርምጃ መውስድ ይኖርበታል::
አገር እንደአገር እንድትቀጥል ለማድረግ መንግሥትና ሕዝብ ተቀራርበው በአንድነት በመስራት ጥፋተኞችን ወደ ፍርድ አደባባይ በማምጣት አስተማሪ ፍርድ እንዲያገኙ የማድረግ ጉዳይ ጊዜ የሚሰጠው አይደለም፤ ሁላችንም ለምንኖርባት አገር የሚጠበቅብንን ኃላፊነት ለመወጣት በአንድነት መቆም አለብን::
እየሩስ አበራ
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 20/2013