ጽጌረዳ ጫንያለው
ከ50 በመቶ በላይ ለሚሆን የእናቶች ሞት ምክንያት ከወሊድ ጋር የሚያያዝ የጤና ችግር ነው፡፡ በተለይ በወሊድ ወቅት በሚከሰት የደም መፍሰስ ምክንያት የሚያልፈው የእናቶች ሕይወት ቀዳሚ ቦታን እንደሚይዝ ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡ እናም ይህንን ችግር ለመቅረፍ እናቶች የቅድመ እና ድህረ ወሊድ የሕክምና ክትትል ማድረግ ግድ ይላቸዋል፡፡ እንደ ሀገር 72 በመቶ የሚሆኑ እናቶች በቤት ውስጥ እንደሚወልዱ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ ይህም ከመጠን በላይ ለሆነ ደም መፍሰስ ስለሚያጋልጣቸው ለኅልፈት የሚዳርጉበት አጋጣሚ በርካታ ነው፡፡ ለዚህ ታዲያ መፍትሄ ሰጪ ነገር ከማህበረሰቡ ብቅ ማለቱ የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡ ይህም በገጠር ጤና ተቋማት የሚገነቡ የነፍሰ ጡር እናቶች ማቆያዎች ሲሆን፤ የቤት ውስጥ ወሊድን ለማስቀረትና የእናቶችን ሞት ለመቀነስ ሁነኛ መፍትሄ ሰጥቷል፡፡
በአብዛኛው የሀገሪቱ ክፍሎች አንዲት እናት ከቤቷ ወደ አቅራቢዋ ያለ ጤና ጣቢያ ለመሄድ ሰዓታትን መጓዝ ይጠበቅባት ይሆናል፤ በወሊድ ወቅት የትራንስፖርት አገልግሎት የማይደርስባቸው አካባቢዎች እናቶች ደግሞ ወደ ጤና ጣቢያ ከመሄድ ይልቅ በቤት ውስጥ እንዲወልዱ ይገደዳሉ፡፡ ይህን ችግር ለመቅረፍ መኖሪያ ቀያቸው ከጤና ጣቢያ ሩቅ ለሆኑ እናቶች የመውለጃ ወራቸው ሲደርስ በጤና ጣቢያ ማረፊያ ቤት ተዘጋጅቶላቸው እንዲቆዩ መደረጉ ደግሞ ይህንን የሚፈታ ነው፡፡ እነዚህ ማቆያዎች ውስጥ የሚቆዩ እናቶች ከቤት ውስጥ ከሚኖራቸው የሥራ ጫና አረፍ ብለው ሙሉ አገልግሎት እንዲያገኙም ያግዛል፡፡ የሕክምና ባለሙያዎችን ተገቢ ድጋፍና ክትትልም በቅርበት ያገኛሉ፡፡ ለዚህም በኢላላ ጤና ጣቢያ ያገኘናቸው ፋጡማ ሼፖታ አንዷ ናቸው፡፡
እርሳቸው እንደሚሉት፤ ከርቀት በልየታ የህክምና አገልግሎታቸውን ለመከታተል ነው በቦታው የተገኙት፡፡ ከገቡ 13ኛ ቀናቸውን አስቆጥረዋል፡፡ የወሊድ አገልግሎቱን ወደ ኋላ ከሚጎትቱት አንዱ ማቆያ አለመኖሩና ምቹ ሁኔታዎች አለመፈጠራቸው ነው፡፡ ስለዚህም እነዚህ አገልግሎቶች መሟላታቸው በተለይ ከርቀት ለሚመጡ እናቶች መፍትሄ ሆኗል፡፡ የመብራትና የውሃ ችግር በየአካባቢው አለ፡፡ እነዚህ ተቋማት ላይ መውለድ መቻላችን ይህንን ችግራችንን አስወግዷል፡፡ በተለይ ደግሞ የህክምና አገልግሎቱ ሳይቆራረጥ እንዲቀጥል ረድቶናል፡፡ ከዚህ ቀደም በነበረው ሁኔታ የእናቶች ማቆያ ማህበረሰቡ የገነባው ነበር። ማቆያው በመኖሩ ምክንያት እናቶች የወሊድ ጊዜያቸው ሲቃረብ ያርፉበታል። ነገር ግን ስፋትም ሆነ ጥራት የለውም፡፡ በዚያ ላይ ከመጸዳጃ ቤት ጋር ያለው ችግር ከፍተኛ ነው፡፡ ይህ አዲሱ ማረፊያ ግን ሀይማኖት ጭምር ግንዛቤ ውስጥ የገባበት ነው፡፡ በተለይ ለእኛ ለእስልምና እምነት ተከታዮች በየሰዓቱ ለመታጠብ ጥሩ እድልን ያመቻቸ ነው፡፡
ዘጠነኛ ወር ስለሞላቸው በጤና ጣቢያው አቅራቢያ ቆይተው በባለሙያዎች እገዛ ወልደው ወደ ቤት ለመመስ አቅደዋል፡፡ በቆይታቸው ጠዋት ቁርስ፣ ምሳና እራት እንዲሁም የሕክምና አግልግሎት በሚያስፈልግ ጊዜ እያገኙ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ‹‹ቀበሌያችን መኪና አይገባም፤ ስመጣም እያረፍኩ ነው የመጣሁት፤ ምጥ ላይ ስሆንማ በጣም እቸገራለሁ ብዬ ነው ወደ ማቆያው በጊዜ የመጣሁት፡፡ ከዚሁ እርፍ ብዬ የሕክምና ክትትል እያደረኩ የምወልድበትን ቀን እየተጠባበኩ ነው›› ብለውናል፡፡
እናቶቹ አስቀድመው በእናቶች ማቆያ ቤት ሲገቡ ከመውለዳቸው በፊት ቤተሰባቸው ተሰብስቦ “ፋጢማ ቆሬ” ያከብሩላቸዋል ያሉን ደግሞ ባለቤታቸውን ለመንከባከብ የመጡት አባት ናቸው። እርሳቸው እንደሚሉት፤ “ፋጢማ ቆሬ” ማለት በባህላችን ሴቶች መውለጃቸው ሲቃረብ አስቀድሞ ገንፎ በማገንፋት እና ቡና፣ ጫት የመሳሰለውን በማዘጋጀት እየተመገቡ ነብሰጡሯን ሴት በሰላም እንድትገላገል አምላካቸውን የሚለምኑበት ስነ ስርዓት ነው። የገንፎ እና የዱአ ጸሎት ስነስርዓቱ ከወለዱም በኋላ ይቀጥላል፡፡ ይህ ወጪ እስከዛሬ በህብረተሰቡ ተሳትፎ ላይ የተመሰረተ ቢሆንም አሁን በዚህ ወረዳ ላይ ሙሉ ወጪዉን እነርሱ ሸፍነው አስተናግደውናል፡፡
ቀደም ያሉት ልጆች ሲወለዱ የነበረው ሁኔታ በጣም አሳሳቢ ነበር። እናትዬው ከጸነሰች ጀምሮ እንዴት ትገላገል ይሆን የሚለውን ጭንቅ ዛሬ ላይ ሳስበው እጅግ ይዘገንናል። በመውለጃ ሰዓትም ትሙት ትኑርም ማወቅ አይቻልም።
በቃ እግዜር እንደፈቀደ ብሎ መተው ብቻ ነበር። አሁን ግን ሐኪሞቹ በቅርብ እየተከታተሉ፣ እሱዋም የሀኪም ሀሳብ እየተቀበለች እራቀኝ ብትል ማቆያ ቤት አስቀድማ እያረፈች፣ ገንፎው፣ ቡናው፣ ጫቱ ተዘጋጅቶላት … ቤተሰቡ አብሮአት እየመጣ … እንዲያው ልጁን በአለም መጠበቅ ሆኗል።›› ይላሉም፡፡
ስለሁኔታው ሲያስረዱም እንዳሉት፤ አሁን ያለው የእናቶች እንክብካቤ ጊዜው መለወጡን የሚያሳይ ብቻ ሳይሆን ነፍሰጡሮቹ መታደላቸውንም የሚያመላክት ነው፡፡ ምክንያቱም “ፋጢማ ቆሬ”ን ሆነ “የማሪያም መሸኛ” በዚያው በሐኪም ቤቱ ገንፎ እያገነፉ ቤተሰቡ ተሰብስቦ እልል እያለ ልጅም እናትም ተደስተው ይከበራል፡፡ አምቡላንስ፣ ሐኪም፣ መድሀኒቱ በነጻ እየተሰጠ ሀሳብም ሒሳብም ቀንሷል፡፡ እናም ይህንን የሚሰሩ አካላት ይክበሩ ይመስገኑ ሳልል አላልፍም ብለውናል፡፡
በጅማ ዞን ጤና ጥበቃ ጽህፈት ቤት በተላላፊ በሽታዎች የአጣዳፊ በሽታዎች ቁጥጥር ውስጥ የሚሰሩት አቶ በቀለ ደሴ በበኩላቸው እንደሚናገሩት፤ ሥራው በጅማ ዩኒቨርስቲ፣ የጅማ ዞን ጤና ጥበቃ ጽህፈት ቤትና የኮርያ ዓለምአቀፍ የጤና ጥበቃ ድርጅት በጋራ የሚሰሩት ነው፡፡ በሦስትዮሽ ፕሮጀክት ይከናወናልም፡፡ በዚህም በአካልም ወስደው ከማስጎብኘት ባለፈ የተሰሩትን ሥራዎችም ዘርዘር አድርገው ነው ያስረዱን፡፡ በዚህም ፕሮጀክቱ በአራት ጅማ ዞን ወረዳዎች ላይ እየተተገበረ የሚገኝ ሲሆን፤ በእነዚህ ወረዳዎች ላይ ከአቅም ግንባታ የጀመረ ስራ ይከናወናል፡፡
የመደሀኒትና የህክምና መሳሪያዎችንም ማቅረቡንም ተግባር በስፋት ይሰራል፡፡ ከዚያ ሻገር ሲል ዛሬ ልናነሳ የወደድነውን ለነፍሰ ጡር እናቶች እፎይታን የሚሰጠውን ቤት በዘመናዊ መንገድ አሰርቶ አገልግሎት እንዲሰጥ መደረጉም ይበል የሚያሰኝ ሥራቸው እንደነበር ከአየነው ለመረዳት ችለናል፡፡ ተግባራቸውን የሚያከናውኑት የነብሰ ጡር እናቶች ፎረምን በመደገፍም ሲሆን፤ አወያይ ባለሙያም በየጊዜው በየወረዳው እንዲገኝ ለማድረግ የትራንስፖርት አገልግሎት ሳይቀር ሰጥተው ይሰራሉ፡፡ ለአብነት በዞኑ ባሉ 25 ጤና ጣቢያዎች ላይ የሞተር ሳይክል አቅርቦት አድርገዋል፡፡
በተጨማሪ ለወረዳ ጽህፈት ቤት ላሉ እነርሱን ለሚከታተሉ ባለሙያዎች ሞተር ሳይክል ሰጥተዋል፡፡ የሦስትዮሽ ሥራውም አላማ እናቶች ወደ ጤና ጣቢያ ሄደው እንዲወልዱና እናትም ልጅም ጤና እንዲሆኑ ማድረግ ነው፡፡ በወሊድ ጊዜ እናቶች ላይ ሊፈጠር የሚችለውን ችግርም ቀድሞ መከላከል ለማስቻል ነው፡፡ ይህ ሁኔታ በተለይ ከርቀት ለሚመጡና በወሊድ ጊዜ ችግር ሊያጋጥማቸው ይችላል ተብሎ ለሚታመንባቸው ነፍሰ ጡር እናቶች ትልቅ እፎይታን የሰጠ እንደሆነ አቶ በቀለ ይናገራሉ፡፡ ለዚህም ምክንያታቸው በመጀመሪያ በማህበረሰቡ ተሳትፎ የተሰራ ቢኖርም ብዙ ነገሮቹ ምቾት የላቸውም፡፡ ጊዜያዊ መፍትሄም ነው የሚሰጥባቸው፡፡ ወረዳው ሰፊና ብዙ እናቶች አገልግሎቱን የሚፈልጉ ቢኖሩም በርከት ያለ ሰውም አያስተናግድም፡፡ በዚህም የሶስቱ ጥምረት የተሻለና ምቾቱ የተጠበቀ ቤት አሰርቶ በማስረከቡ ይህንን ሁሉ ችግር ፈቷል ስለሚያስብላቸው ነው፡፡
በእያንዳንዱ ጤና ጣቢያ ለክትትል የሚመጡ እናቶች በርከት የሚሉ ሲሆን፤ በአንድ ጊዜ ቢያንስ ስምንት እናቶችን ማቆየት ይችላል፡፡ ለ15 ቀን የመቆየት እድሜ ይሰጣቸዋልም፡፡ ይህ ደግሞ እናት አባት ቤት ከሚደረግላት በተሻለ መልኩ በህክምና ባለሙያዎች ጭምር ክትትልና እንክብካቤ እየተደረገላት እንድትቆይም ያግዛታል፡፡ በዚያ ላይ ብዙ አንቡላንስ የማይገባባቸው ቦታዎች ላይ የሚኖሩ ሊሆኑ ይችላሉና ቀድመው በመምጣታቸው ያለምንም ችግር እንዲገላገሉም ይሆናሉ ይላሉ፡፡
እዚህ ቦታ ላይ የመጣች እናት ሙሉ ጤናዋ ይጠበቅላታል፡፡ ሪፈር እንኳ ሲኖር ሳትንገላታ ተፈላጊው ቦታ በአንቡላንስ የምትወሰድበት ምቹ ሁኔታ አለ፡፡ በአንድ ወረዳ ሰባት ጤና ጣቢያ የሚገኝ ሲሆን፤ የአገልግሎቱ ሙሉ ዝግጁነት ካለ ችግርን ከመፍታት አኳያ የማይተካ ሚና አለው፡፡ ማቆያው ደግሞ የእናቶች ሞትን በመቀነስ ረገድ ብቻ ሳይሆን ጤናማ እናቶች እንዲኖሩ በማድረጉ ዙሪያ የማይተካ ሚናን እየተጫወተ ይገኛል። በሌላ በኩልም ጤና ጣቢያው በስሩ የሚገኙ ጤና ኬላዎችን የጊዜ ሰሌዳ በማውጣት ባለሙያና ግብአቶችን በማሟላት እንደሚደግፍና ከጤና ጣቢያ አቅም በላይ የሆኑ አንዳንድ ህክምናዎችን ወደ ሆስፒታል ሪፈር እንደሚያደርግ ተናግረው ይህም ጠንካራ የክትትል ድጋፍ ስርዓት እንደተዘረጋ አድርጓል ብለዋል፡፡
ሌላው በጉዳዩ ዙሪያ ያነሱት ‹‹አምቡላንስ በማይገባባቸው ቦታዎች የሚገኙ ነፍሰ ጡር እናቶች ቀድመው በመምጣት የአግልግሎቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን ሲሆን፤ ልዩ ድጋፍ እና ክትትል ለሚያስፈልጋቸው እናቶች ደግሞ ክትትል ማድረግ ተችሏል፡፡ ምክንያቱም አንዲት ነፍሰጡር እናት በማቆያ ለረጅም ቀናት መቆየት የምትችልበት እድል ተሰጥቷታል፡፡ ለዚህ ደግሞ በቀበሌያችን የሴቶች ልማት ቡድን አደረጃጀት አለ። እንደአደረጃጀቱ የእናቶችን ጤና አገልግሎት ለመስራት ኮማንድ ፖስት ብቻ ሳይሆን የልማት ቡድኖቹም እንዲያግዙ ተደርጎ መሰራት ተጀምሯል፡፡ በዚህም መተጋገዝ ለእናቶች ጤና በተግባር እንዲታይ ሆኗል፡፡
የልማት ቡድኖቹ በስራቸው ካለው ህብረተሰብ መካከል ማን ነፍሰ ጡር እንደሆነ ማን ጤና ጣቢያ ሄዶ እንደወለደ ያሳውቃል። በስሩ ላሉ ሴቶች የበለጠ ኃላፊነት ስላለበትም ከእርግዝና፣ ወሊድ እና ድህረ ወሊድ ድረስ ያለውን ሁኔታ ይመዘግባልም፡፡ ከዚያ ለሚመለከተው ክፍልም ሪፖርት ያደርጋል። ይህ ደግሞ ከጤና ተቋም ውጪ እንዳወልድ ያግዛል፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ ፕሮጀክቱ ለህብረተሰቡ በተለያዩ መድረኮች ያስተምራል፡፡ በሬዲዮ ጭምር ትምህርት የሚሰጥበት ሁኔታም ተመቻችቷል፡፡ ምናልባት እንኳን አንዲት እናት የምትኖርበት ቦታ እሩቅ ቢሆን በጤና ጣቢያ የእናቶች ማቆያ ቤት ስለተዘጋጀ አስቀድማ ከዚያ በማረፍ መውለድ ትችላለችና ይህ በትብብሩ እየተሰራ መሆኑንም ነግረውናል፡፡
ህብረተሰቡ በማቆያው ስፍራ የሚደረገውን ዝግጅት እንዳይጨናነቅ ለማድረግም በሦስት እዮሹ ሥራ ይሰራል፡፡ መንግስት የበለጠ ትኩረት ሰጥቶ የእናቶችን ሞት ለመቀነስ እናቶች በየቤታቸው መውለድ የለባቸውም፣ የሰለጠነ የሰው ኃይልና በጤና ተቋም መውለድ አለባቸው የሚል አቋም በሀገር ደረጃ በመያዙ አሁን በተቻለ መጠን ይህንኑ ተግባራዊ ለማድረግ በተደራጀ መልኩ ስለምንንቀሳቀስ ቁጥራቸው ከፍ ያለ ሆኗል። ከአጋር አካላት ጋር መስራት መቻሉ ደግሞ ይበልጥ ነገሩን ከፍ አድርጎታልም ብለዋል፡፡ ምክንያቱም ማረፊያ ቤታቸውን በጥራት ሰርቶ ለገንፎ እና ለተለያዩ ወጪዎች ሸፍኖ ምቾት ተሰምቷቸው እንዲታረሱ እየተደረገም መሆኑን አውግተውናል፡፡ እኛም ይህ ሥራችሁ ዛሬም፣ ነገም ለእናቶች ሀሳብም ሂሳብም መቀነሻ ይሁን በማለት አበቃን፡፡ ሰላም!
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 10/2013