አብርሃም ተወልደ
ሀገራችን የግሉ ዘርፍ በኢኮኖሚ ውስጥ ጉልህ ስፍራ እንዲይዝ ትፈልጋለች። የግሉ ዘርፍ በተለይ በኢንዱስትሪው መስክ እንዲሰማራ ይፈልጋል። ሀገሪቱ ኢኮኖሚዋን ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ ለማሸጋገር በምታደርገው ጥረት የግሉ ዘርፍ ሚና ከፍተኛ መሆኑ ታምኖበታል። የግሉ ዘርፍ ከንግድና አገልግሎት ዘርፍ እየወጣ በኢንዱስትሪው ዘርፍ እንዲሰማራ ይፈልጋል። በዚህም የግሉ ዘርፍ ራሱንና ሀገሩን ይጠቅማል የሚል እምነት አለ።
ይህን ተከትሎም የሀገር ውስጥ ባለሀብቶችና ዲያስፖራዎች በሆቴልና በሌሎች የተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ተሰማርተው እየሰሩ ናቸው። እነዚህ ባለሀብቶች ለዜጎች የሥራ እድል በመፍጠር፣ የውጭ ምንዛሪ በማስገኘት፣ የእውቀትና ቴክኖሎጂ ሽግግር መሳሪያ በመሆን ላይ ይገኛሉ። በውጭ ምንዛሪ ከውጭ የሚመጡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በማምረት የሀገሪቱን የኢንቨስትመንት አቅጣጫ ተከትለው እየሰሩም ናቸው።
ችግሩ ባለሀብቶቹ በኢንዱስትሪው መስክ በስፋ ት አለመሰማራታቸው ላይ ነው። የእነሱ ትኩረት አሁንም በንግድ ላይ ነው። በህንጻ ግንብቶ ማከራየት ላይ ተጠምደዋል። ሀገርን የሚያለማው ይህ ሳይሆን በኢንዱስትሪ ዘርፍ መሰማራት ነው።
ከባለሀብቶቹ መካከል አንዳንዶቹ ሀብታቸውን በአግባቡ በመጠቀም በሀገሪቱ የተለያዩ ኢንዱስትሪዎችን በመገንባት እንደ ዘይት ፣ፓስታና መኮሮኒ ያሉትን ምርቶች እያመረቱ ይገኛሉ። እነዚህ ባለሀብቶች ከምንም ተነስተው በታታሪነት እና በትጋታቸው ጥሪት እና ሀብት አካብተዋል።
በአገር ውስጥ ያገኙትን ሀብት አገር ላይ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ሥራዎች ላይ የሚያውሉ የአገርና የህዝብ ባለውለታዎች ናቸው። ይህንን ጸጋ የሰጠችኝ አገሬ ናት እኔም ለአገሬ ይህንን አደርጋለው የሚሉ ጀግኖች ናቸው።
ከዚህ በተጻራሪው ደግሞ አንዳንድ ባለሀብቶች በሀገር ውስጥ ካፈሩት ሀብት እየቀነሱ ወደ ውጭ ሀገሮች ያሸሻሉ። በአገር ቤት ሰርቶ ንብረት አፍርቶ በልጽገው ሲያበቁ የአገርን ሀብት በውጭ ምንዛሪ በመቀየር እያሸሹ ናቸው። የሚያሸሹት ደግሞ ልክ እንደ ኢትዮጵያ በድህነት ወደማይዳክሩ ኢንቨስትመንቱ በጣም አስፈላጊ ወደ አልሆነባቸው ሀገሮች በመሄድ ነው።
ኢትዮጵያ የሌሎች ሀገሮች ባለሀብቶች ኢንቨስት እንዲያደርጉ ጥሪ እያቀረበች እያለ የተገኘውን ሀብት ይዞ በሌላ ሀገር ለመስራት ማሰብ ጤነኛነት አይደለም። በጣም አንግት የሚያሳደፋ ተግባር ነው፤እነዚህ ግለሰቦች ሀብት ያገኙት እንዲሁም ንብረቱን ያካበቱት በኢንቨስትመንቱ ምክንያት ከቀረጥ ነጻ በተፈቀደላቸው እድል እና በተፈጠሩላቸው ምቹ ሁኔታዎች መሆኑ ሊዘነጋ አይገባም።
ሀገራችን ውስጥ በተቋራጭነት የተሰማሩ የቻይና ኩባንያ ሰራተኞች አሉ የተባለው ትዝ ይለኛል። ኢት ዮጵያውን ሙስና ላይ መጠመዳቸውን አይተው ሙሰ ኞቹ ሌላ ሀገር አላቸው ወይ አሉ ይባላል። በአንዳንድ ባለሀብቶችና የንግዱ ማህበረሰብ ዘንድ የሚታየው ነገር በእርግጥም ይህን ያስጠቅሳል።
እነዚህ ባለሀብቶች ሀብታቸውን እንደ ፈለጉ ሊያደርጉ ይችላሉ። ኃላፊነት የሚሰማው ባለሀብት ግን ይህን አያደርግም። አምርተው ሀገርና ህዝብ መጥቀም ሲገባቸው ኢንቨስትመንቱን ሊያሰፋፉበት የሚችሉትን ሀብት ማሸሽ አልነበረባቸውም።
እነዚህ ባለሀብቶች ወይም ባለጸጋዎች ልጆቻቸውን በውጭ ሀገር ያስተምራሉ፤ልጆቹ በነጻ አይደለም የሚማሩት ከሀገር ቤት በሚገኝ ሀብት ነው። በሀገር ውስጥ ሊታከሙት የሚችሉትን በሽታ ውጭ ሀገር ሄደው ነው የሚታከሙት። ከእነዚህም አለፍ ብለው መኖሪያ ቤት የሚገዙና የሚሰሩ እንዲሁም ድርጅት የሚከፍቱ የሚገነቡም አሉ።
ውጭ ሀገር ነጋ ጠባ ይመላለሳሉ። ይህን የሚያደርጉት ደግሞ በሀገር ውስጥ ላለው ሥራቸው የሚሆን ጥሬ እቃ ፍለጋ አይደለም፤ታመው ሊሆን ወይም በዚያ ሌላ የንግድ ሥራ ወይም ኢንቨስትመንት ኖሯቸው ሊሆን ይችላል።
ጁንታው በፈጠራቸው ኢንቨስትመንቶች ሰበብ በዱባይ በሪል ስቴት ልማት ውስጥ የተሰማሩ እንዳሉ አንዳንድ መረጃዎች ይጠቁማሉ። እነሱ አይኖራቸውም አይባልም። ከሀገሪቱ በተለያየ ዘዴ የዘረፉት ሀብት ሌላ ብዙ የሚያሰራም ነው። የእነሱ ነገር የለየለት ነው።
ሌሎች ሀገሪቱ በኢንቨስትመንትም ይሁን በንግዱ ዘርፍ በፈጠረችላቸው ምቹ ሁኔታ ተጠቅመው ከብረው ይህን ሀብት እዚሁ አገር ቤት ሊሰሩበት ሲገባ በባእድ ሀገር ለተለያዩ አላማዎች ማዋላቸው በእኔ እምነት ትክክል አይደለም። በውጭ ሀገር ሌላ ኢንቨስትመንት ቢያካሂዱበት እንኳ እኔ ሰዓቱ ነው ብዬ አላምንም።
በርካታ ኢትዮጵያውያን በውጭ ሀገሮች ካፈሩት ሀብት የተወሰነውን ለቤተሰባቸው፣ለወዳጅ ለዘመዳቸው እየላኩ ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን እየፈቱ ናቸው። ከዚህም አልፈው በሀገሪቱ የተለያዩ የኢንቨስትመንት ሥራዎች በመሰማራት ለዜጎች የሥራ እድል እየፈጠሩ ይገኛሉ።
በእውቀትና ቴክኖሎጂ ሽግግርም ሀገራቸውን እየጠቀሙ ናቸው። የውጭ ምንዛሪ ይዘው የመጡ በመሆናቸውም ሀገሪቱን በውጭ ምንዛሪ ግኝት እየረዱ ናቸው ማለት ይቻላል።
እነዚህ ዲያስፖራ ኢትዮጵያውያን ይህን ሲያደርጉ በሀገር ቤት ካሉት ኢትዮጵያውያን ባለሀብቶች አንዳንዶች በሀገር ቤት ካፈሩት ሀብት እየቀነሱ ወደ ውጭ መላካቸው በእጅጉ ያሳስባል። እነዚህ ባለሀብቶች በሀገር ቤት ያፈሩትን ጥሪት ያጎረሳቸውን እጅ በመንከስ ሌሎች አገራት ላይ ወስደው ሲጠቀሙበት (ሲበትኑት) ይታያል።
ባለሀብቶቹ ገንዘቡን ወደ ውጭ ለመላካቸው የተለያዩ ምክንያቶች ሊጠቅሱ ይችላሉ። ቤተሰባቸውን ይበልጥ በተደላደለ ቦታ ላይ ለማኖር ፈልገው ሊሆን ይችላል። የሀገሪቱ የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ስርአት ላይ ጥርጣሬ አላቸው ብሎ መውሰድም ይቻላል። አለበለዚያም ያገኙት ሀብት ጤነኛ ስላልሆነ ማሸሽን ዋና መንገድ አድርገውት ሊሆን ይችላል።
በዚህ አይነቱ ጉዳይ ላይ የሀገሪቱ ኢንቨስትመንት ፖሊሲ ምን እንደሚል ባላውቅም፣በሀገር ድጎማና ድጋፍ ከተገኘ ሀብት ላይ በውጭ ምንዛሪ እየመነዘሩ ወደ ውጭ መላክ እኔ ጠነኛ አሰራር ነው ብዬ አላምንም። መላክ ካለበትም ምን ያህሉ መላክ አለበት የሚለው ላይ አንድ ነገር መደረግ አለበት።
የሚመለከተው አካልም የትኛውም ባለሀብት በአገር ውስጥ ያፈራውን ንብረትም ሆነ ገንዘብ ከአገር ውጭ እንዳይወጣ እና እዚሁ አገር ውስጥ ኢንቨስት እንዲያደርግ በህግ ሊያግደው ይገባል። ባለሀብቱም ቢሆን ማን እንደአገር የሚባለውን ቢሂል እና ምክር ገንዘቡ አድርጎ በታሪክም በህዝብም የሚታወስ ሥራ መስራት ይኖርበታል።
ህዝብ እና አገር አምኖ ትንሽ ስለሰራህ ይህንን ብንጨምርለት የበለጠ የሥራ ዕድል ይፈጥራል ብሎ ወስኖ እና ፈቅዶ የሰጠውን ዕድል ባልተጋባ መንገድ በመጠቀም የአገርን ፀጋ ይዞ ወደሌላ አገር መውጣት ተገቢ እንዳልሆነ በግልጽ ሊነገረው በህግም ሊጠየቅ የሚችልበት ሁኔታም ሊመቻች ይገባል።
የአገርን ጸጋ ይዞ አገርን ሳይጠቅሙ ሌሎችን አገራትን ለማበልጸግ የሚደረግ ጉዞ አስፈላጊ ስላለመሆኑ አይደለም ባለሀብት አባይ ወንዛችን እንኳን ልብ ገዝቷል። ሀብት በማሸሽ ላይ የምትገኙ አንዳንድ ባለሀብቶች እባካችሁን መንግሥት በፈጠረው ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በሀገር ቤት ያፈራችሁትን ሀብት በሀገር ቤት ለኢንቨስትመንት ማስፋፊያ ማዋል እንጂ ማሸሽ ላይ አታተኩሩ!!
አዲስ ዘመን የካቲት 16/2013