ከሀገራዊ ለውጡ ማግሥት አንስቶ በተለይም በብልፅግና ፓርቲ መሪነት እንደ ክልል የተከናወኑ መንግሥታዊና ድርጅታዊ ተግባራትን በጥልቀት በመገምገም ባንድ በኩል የክልሉን አጠቃላይ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና የሠላም ሁኔታዎች በሚገባ በመረዳት በየዘርፉ ለሚስተዋሉ ውስንነቶች አስተማማኝና ዘላቂነት ያለው መፍትሄ ማስቀመጥ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ለመተከል ዞን የሠላም እጦት ዋነኛ መንስኤዎች በሆኑ ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባት ከመፍጠር ባለፈ ችግሩን ከምንጩ ለማድረቅ የሚያስችሉ ስልቶችን በመቀየስ በአመራሩ የላቀ ቁርጠኝነት እንዲተገበሩ ማድረግ ወቅታዊ ክልላዊ ሁኔታችን ግድ እንደሚል ይታመናል።
በዚህም እምነት ላይ በመመስረትም እኛ የቤኒሻንጉል- ጉሙዝ ከፍተኛና መካከለኛ የብልፅግና ፓርቲ አመራር አባላት በፓርቲው አስተባባሪነት በተዘጋጀው የ3 ቀናት ኮንፈረንስ በወቅታዊ ክልላዊ የፖለቲካና የሠላም ሁኔታዎች ላይ የተዘጋጀውን ሠነድ መሠረት በማድረግ በስፋት እና በጥልቀት ተወያይተናል።
በዚህ ውይይታችን የተገነዘብናቸው መልካም ሥራዎችና አፈፃፀሞች መኖራቸው እንደተጠበቁ ሆኖ በአንፃሩ የላቀ ትርጉም ሰጥተን ልንረዳቸው፣ አፋጣኝ፣ አስተማማኝና ዘላቂ መፍትሄ ልንሰጣቸው፣ በተለየ የአፈፃፀም ስልት፣ በጋራ ጥረትና በተቀናጀ ርብርብ የመጨረሻ እልባት ልናበጅላቸው የሚገቡ አሳሳቢ ተግዳሮቶች እንዳሉብን በጥልቀት ተገንዝበናል።
ከዚህ አንፃር በተለይም ተፈጥሮ የለገሠችንን ዕምቅ ሃብትና ፀጋ ተጠቅመን ፣ የህዝብን ኑሮ መለወጥ ፣ ለሀገርና ለወገን የሚተርፍ ውጤት ማስመዝገብ ፣ ለላቀ ልማት የሚውል ሃብት እና ወረት ማካበት ሳንችል እስከአሁን መዝለቃችን በእጅጉ የሚያሰቆጭ ስለመሆኑ የጋራ መግባባት ፈጥረናል።
ከዚህም በተጨማሪ የአብሮነት ተምሳሌትና የብዝሃነት መገለጫ የነበረችው ክልላችን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ይህንን የመሠለው መልካም ገፅታዋ ተቀይሮ በአስከፊ የእርስ በእርስ ግጭት፣ በዜጎች ሞትና መፈናቀል፣ በሠላምና መረጋጋት ዕጦት ስትጠቀስ ማስተዋል በእጅጉ አሳዝኖናል።በንፁሃን ዜጎቻችን ላይ የደረሰው ሞትና መፈናቀል ልብ ሰባሪ መቼም እና የትም መደገም የሌለበት አሳዛኝ ድርጊት በመሆኑ መላ የክልላችንን ኗሪዎች ይቅርታ እየጠየቅን በተግባር ለመካስ መዘጋጀታችንን እናረጋግጣለን።
በሌላ በኩል በተለይም በየደረጃው የሚገኙ አንዳንድ አመራሮቻችን የፓርቲያችንን ዕሴቶችና መርሆዎች በሚገባ በመገንዘብና ከራስ ጋር በማዋሃድ በህዝብ ዘንድ እንዲሰርፁ በማድረግ በአንድ ስሜትና በህብረት የብልፅግና ጉዟችንን ለማሳካት እንዲረባረብ ከማነሳሳት ይልቅ በአደናቃፊ አስተሳሰቦች ሥር ወድቀው ብልፅግና አሃዳዊነትን የሚያቀነቅን፣ የዜጎችን እራስን በራስ የማስተዳደርና የመምራት ሕገ-መንግሥታዊ መብት የሚጋፋ አድርገው ከሚስሉ ጥቂት አደናጋሪ ኃይሎች ጋር በመሰለፍ ለግል ሥልጣናቸው እየተስገበገቡ እንደቆዩ በኮንፈረንስ መድረኩ ነጥሮ ወጥቷል።
ከመተከል ዞን የሠላም እጦት ጋር በተያያዘ ችግሩን ለመፍታት የሚደረገውን ጥረት ከማደናቀፍ ባለፈ ዋነኛ ተባባሪ፣ አባባሽና አቀጣጣይ መሆናቸው፣ ከሌሎች የውስጥ ፅንፈኛ ኃይሎች እና የውጪ ተላላኪዎች አፍራሽ እንቅስቃሴዎች ጋር ተዳምሮ በሚፈለገው ፍጥነት፣ በሚቻለው ልክ እና መጠን ውጤት እንዳይመዘገብ እንዳደረገ በሚገባ ተገንዝበናል።
ስለሆነም የተጀመረውን ውስጣችንን በሚገባ የመፈተሽና የማጥራት ሥራ የበለጠ አጠናክረን ማስቀጠል እንዳለብን ከመግባባት ላይ ደርሰናል። በእነዚህ አበይት ግንዛቤዎች ላይ በመመስረትም የሚከተለውን ባለ 9 ነጥብ የአቋም መግለጫ አውጥተናል።
1ኛ. በክልላችን አጠቃላይ እና በተለይ ደግሞ በመተከል ዞን የተጀመረውን የህግ የበላይነትን የማረጋገጥ ሥራ ይበልጥ አጠናክሮ በማስቀጠል ማንም ይሁን ማን ወንጀል ፈፃሚዎችንና ተባባሪዎቻቸውን በሕግ ተጠያቂ ለማድረግ አስፈላጊውን መስዋዕትነት ሁሉ እንከፍላለን፡፤
ከዚሁ ጎን ለጎን መንደራቸውን ትተው ወደ አጎራባች አካባቢዎች እና ወደ ጫካ የተሰደዱ ወገኖቻችንን ወደ ቀድሞ የመኖሪያ ቀያቸው ለመመለስ፣ በዘላቂነት ለማቋቋምና በመካከላቸው የተፈጠረውን ቅሬታ በእርቅ በማሻገር የአካባቢውን ሠላም ወደነበረበት ለመመለስ ከመቼውም ጊዜ በላይ በላቀ ቁርጠኝነትና የህዝብ ወገንተኝነት ስሜት እንሠራለን።
2ኛ.በአንድ በኩል ውስጣችንን በሚገባ በመፈተሽ እና በማጥራት፣ በሌላ በኩል ደግሞ የፓርቲያችንን እሴቶችና መርሆዎች በሚገባ በመገንዘብና ከራሳችን ጋር በማዋሃድ ተግባሮቻችን ሁሉ በሠፊ የህዝብ የባለቤትነት ተሳትፎ እንዲተገበሩ እና ለብልፅግና ጉዟችን ስኬት ተደማሪ አቅም እንዲሆኑ ለማስቻል ከመቼውም ጊዜ በላይ የላቀ ርብርብ እናደርጋለን።
3ኛ.ሕብረ-ብሔራዊነታችን የውበታችን መገለጫ እና የጥንካሬያችን ምንጭ እንጂ የልዩነታችንና የመለያያችን ምክንያት አለመሆኑን በጥልቀት በመገንዘብ ከዚህ በተቃራኒ የሚራመዱ የፅንፈኝነትና የዋልታረገጥነት አስተሳሰቦችን በመታገል ለዜጎች እኩልነትና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት አበክረን እንሠራለን።
4ኛ. በየደረጃው በሚገኙ አመራሮቻችን ዘንድ የሚስተዋሉ የጎሰኝነትና ከባቢያዊነት አመለካከቶች፣ ተልዕኮን በሙሉ እምነት ተቀብሎ ያለመተግባር ዝንፈቶች፣ የራስን ያልተገባ ድሎትና ምቾት ለህዝብ ጥቅም ሲባል አሳልፎ ያለመስጠት ስንፈቶች እና ሥልጣንን ያለ አግባብ ለመቆጣጠር የሚደረጉ ጥረቶች አምርረን በማውገዝና በመታገል ቁርጠኛ ተተኪዎችን ለማፍራት በአንድ ስሜት እንተጋለን።
5ኛ. ተፈጥሮ የለገሠችንን ዕምቅ ሃብትና ፀጋ ተጠቅመን ፣ የህዝባችንን ኑሮ ትርጉም ባለው ልክና መጠን ከመለወጥ ባለፈ ለሀገርና ለወገን የሚተርፍ ውጤት ለማስመዝገብ፣ ለላቀ ልማት የሚውል ሃብት ለማፍራት እና ወረት ለማካበት ፣ በድምሩም ድህነትንና ኋላቀርነትን ታሪክ ለማድረግ ከመቼውም ጊዜ በላይ በላቀ ቁርጠኝነት እንረባረባለን።
6ኛ. በክልላችን አስተማማኝ እና ዘላቂ ሠላም ለማስፈን ፣ በየደረጃው የሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታትና ለህዝባችን ያልተመለሱ የኢኮኖሚና የማኅበራዊ ልማት ጥያቄዎች አጥጋቢ ምላሽ ለማስገኘት የተለየ ትኩረት ሰጥተን እንሠራለን።
7ኛ. የሴቶችንና የወጣቶችን ሁለንተናዊ ብቃት በማሳደግ በክልሉ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ልማት እንቅስቃሴዎች ውስጥ በተደራጀ አኳኋን የጀመሩትን ተሳትፎ ይበልጥ በማጠናከርና በማጎልበት ባንድ በኩል የለውጥ ጠል ኃይሎች በሚያራምዱት የተሳሳተ ትርክትና ቅስቀሳ እንዳይጠለፉ ለመታደግ ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ባበረከቱት አስተዋጽኦ ልክ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለማስቻል የበኩላችንን የኃላፊነት ሚና በላቀ ቁርጠኝነት እንወጣለን።
8ኛ. እንደ ክልልም ሆነ እንደ ሀገር አብሮ የሚያኖረንና የሚያዛልቀን ስህተቶቻችንን ለማረምና ለማስተካከል፣ ፍፁም ዴሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ ለመወያየትና ለመማማር ፣ በይቅርታና በፍቅር ለመሻገር ፣ የህግ የበላይነትን በጋራ ጥረትና ትግል ለማስከበር ስንችል እንጅ የለየላቸው የጎጥና የጎሳ አጀንዳዎችን እየለቀምን፣ የተለየ ቀለም እየቀባንና ህዝብ ውስጥ እያሠራጨን እርስ በእርስ በመጋጨት ሊሆን እንደማይችል በሚገባ እንገነዘባለን።
ሰለሆነም ሠላማችንን ለማደፍረስ፣ ልማታችንን ለማስተጓጎልና አብሮነታችንን በመገዳደር ወደ ግጭት እንድናመራ የሚደረጉ ማናቸውንም ዓይነት ሙከራዎች አምርረን ከማውገዝ ባሻገር በመካከላችን ጠንካራ የአመለካከትና የተግባር አንድነት ፈጥረን በፅናት ልንታገላቸው ቃል እንገባለን።
9ኛ. የክልላችን ጂኦ-ፖለቲካዊ ሁኔታ ለበርካታ የውጪ ኃይሎች እና የውስጥ ጉዳይ አስፈፃሚዎች የግጭትና የብጥብጥ አጀንዳ ማራመጃነት የተጋለጠ መሆኑ ይታወቃል።
ስለሆነም ይህንን ተጋላጭነታችንን ከግንዛቤ ውስጥ በማስገባት ሊከሰቱ የሚችሉ የግጭት አደጋዎችን አስቀድሞ ለመከላከልና ችግሩ ዳግም እንዳይከሰት ከተጎራባች ክልሎች እና ከፌዴራል መንግሥት ጋር በቅርበት ተባብሮ ለመስራት ያለንን ቁርጠኝነት እናረጋግጣለን።
እውነተኛ ሕብረ-ብሔራዊ ፌዴራላዊ ሥርዓትን በማፅናት የክልላችን ህዝቦች የጋራ ልማትና ደህንነት ይረጋገጣል።
የቤኒሻንጉል-ጉሙዝ የብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች
የካቲት 3 ቀን 2013 ዓ.ም
አሶሳ
አዲስ ዘመን የካቲተር 04/2013