አገራዊ ለውጡን ተከትሎ በኢትዮጵያ ከ113 በላይ ግጭቶች ስለመከሰታቸው በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐብይ አህመድ መግለጻቸው ይታወሳል። በእያንዳንዱ ግጭት ጀርባም የሰው ሕይወት ጠፍቷል፤ አካል ጎድሏል፤ ንብረት ወድሟል፤ በርካቶችም ከመኖሪያ አካባቢያቸው ተፈናቅለዋል።
እነዚህ ግጭቶች በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የተከሰቱ ይሁኑ እንጂ፤ ከእያንዳንዱ ግጭት ጋር የህወሓት ጁንታ ስም ተደጋግሞ ተነስቷል። ይሄም ኋላ ላይ አፍጥጦ የወጣ እውነት ሆኖ ተገኝቷል።
የህወሓት ጁንታው ያፈጠጠ የአጥፊነት ብቻ ሳይሆን የአገር አፍራሽነት ተግባር ገሃድ ከወጣበት ከጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም ምሽት ጀምሮ ግን እነዚህ ግጭቶች እምብዛም አልታዩም።
ይህ ደግሞ የጁንታው መዳከም ብሎም መደምሰስ በየአካባቢዎቹ ዜጎች ሰላማዊ አየር እንዲተነፍሱ ያስቻላቸው መሆኑን የሚያስረዳ ሲሆን፤ የጁንታው መዳከም በየአካባቢው ያሉ የእጅ አዙር ሁከት ፈጣሪ ተቀጣሪዎችም አቅም እየደከመና እየተመናመኑ መምጣታቸውን የሚያሳይ ነው።
ይሁን እንጂ ቀደም ሲልም ሆነ አሁንም ድረስ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን ውስጥ ባለው ችግር የሕዝብ እንባ አባሽ አጥቶ፤ የሚፈስሰውም ደም ፍትህ ናፍቆ፤ ችግሩም ዘላቂ መፍትሄና ሃይ ባይ አጥቶ እንዳለ ቀጥሏል። ዓመታትን በተሻገረው በዚህ ችግር በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ተፈናቅለው በጊዜያዊ መጠለያ ጣቢያ ውስጥ ይገኛሉ፤ በርካታ ቤቶች ተቃጥለዋል፤ ንብረት ወድሟል፤ ተዘርፏል፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎችም ክቡር ሕይወታቸውን አጥተዋል፤ አካላቸውም ጎድሏል።
ሰዎች በአሰቃቂ ሁኔታ በቀስት ተገድለዋል፤ ነፍሰ ጡር እናቶች ሆዳቸው በስለት እየተቀደደ ጽንሳቸው እንዲወጣ ተደርጓል።
ይህ ሁሉ ግፍና መከራ መገለጫዋ እየሆነ የመጣችው መተከል ዞን ነዋሪዎቿ ዓመታትን የስቃይ እንባ እያነቡ፣ በሰቀቀን የሚኖሩባት፤ ሲብስም የሚሰደዱባትና ሀብት ንብረታቸውን የዘራፊና የእሳት ሲሳይ የሚያደርጉባት ሆናለች። ዋናው ጉዳይ ግን ይህ ሁሉ የሚሆንባት መተከል ዞንም ሆነች እንደ አጠቃላይ ክልሉ ለምን የአካባቢውን ሰላም ማስከበር፤ የሕዝቡንም ደህንነት ማስጠበቅ አቃታቸው? በዞኑ ስር የሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎች ከሦስት ጊዜ ላላነሰ በኮማንድ ፖስት እንዲተዳደሩ ሲደረግ ለምን ዘላቂ መፍትሄ አልመጣም? የሚለው ነው።
ቀደም ሲል ሲገለጽ እንደነበረው በተለያዩ አካባቢዎች ያሉ ግጭቶች የህወሓት ጁንታ ሁለንተናዊ ድጋፍና ተሳትፎ ያለባቸው ናቸው። በእርግጥም ያ መሆኑ ገሃድ ወጥቷል። ነገር ግን ከጁንታው መወገድ በኋላ በሌሎች አካባቢዎች የሚስተዋሉ የሰላም መደፍረሶች ወደ መክሰም ሲሄዱ፤ በመተከል ያለው ችግር ለምን እልባት አላገኘም የሚለው ጉዳይ ብዙዎችን ግራ ያጋባም፣ ያስገረመም ጉዳይ ሆኗል።
እርግጥ ነው፣ በዚህ አካባቢ ያለው ችግር እልባት ያለማግኘቱ ገፍቶ ዛሬም ዜጎች እያነቡና ክቡር ሕይወታቸውን፣ አካልና ንብረታቸውን እያጡ በሰቀቀን የሚኖሩ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ፤ ከትናንት በስቲያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ወደ አካባቢው አቅንተው ከአካባቢው የአመራር አካላትና ኅብረተሰብ ጋር መወያየታቸው ይታወሳል። ይህ ደግሞ በአካባቢው ዘላቂ ሰላም እንዲመጣ የሚያግዝ ትልቅ እርምጃ መሆኑ እሙን ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትሩም በሥፍራው ሄደው ከሕዝቡ ጋር ተወያይተው ያለውን እውነት ከተረዱ በኋላ፤«ጠላቶች ኢትዮጵያን በብሔርና በሃይማኖት ለመከፋፈል ያላቸው ፍላጎት ዛሬም አልጠፋም። በጽናትና በአንድነት ስንታገለው ግን ይህ ፍላጎት መና ሆኖ ይቀራል። በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ከመተከል ነዋሪዎች ጋር ባደረግሁት ውይይት ያየሁት ሕዝባችን ለአንድነት፣ ለሰላም፣ ለልማትና ለብልጽግና ያለው ፍላጎት ከማንኛውም ከፋፋይ አጀንዳ ይበልጣል። ይሄንን ጽኑና አስተዋይ ሕዝብ ይዘን ችግሮች እንዳይደገሙ አድርገን እንፈታቸዋለን፤» የሚል ሀሳብ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው አስፍረዋል።
ሀሳቡ ተገቢ ብቻ ሳይሆን የሕዝቡን ትክክለኛ ስሜት የያዘም ነው። ምክንያቱም እርሳቸው እንዳሰፈሩት ሕዝቡ ለአንድነት፣ ለሰላም፣ ለልማትና ለብልጽግና ያለው ፍላጎት ከማንኛውም ከፋፋይ አጀንዳ ይበልጣል። ነገር ግን አንድ መሪ ብቻውን ይሄን እውነት ተረድቶ ችግሮችን ሁሉ ሊፈታ አይችልም።
እናም ሕዝቡ ይሄን ስሜት ተረድቶ ከጎኑ የሚቆም፤ ሰላምና ደህንነቱን የሚያስጠብቅ፤ የሚፈስስ እንባውን የሚያብስ፤ ለፈሰሰ ደሙም ፍትህ የሚሰጥ፤ ችግሩንም በዘላቂነት ሊፈታለት የሚችል አመራር በየደረጃው ይፈልጋል። በመሆኑም በአካባቢው ሕግ በማስከበር፣ ወንጀለኞችን አደብ በማስያዝ እና በየደረጃው ያለ አመራርንም በሥራው ልክ ፈትሾ የማስተካከያ እርምት በማድረግ የዜጎች የሰቆቃ ሕይወት መቋጫ እንዲያገኝ የሚያስችል ሥራ ማከናወን ግድ እና ለነገ የማይባል ተግባር ሊሆን ይገባል።
አዲስ ዘመን ታህሳስ 15/2013