ምሽቱ በቅዝቃዜ ታጅቦ የሚወርደው ዶፍ ዝናብ ከሚሰማው ነጎድጓድ ጋር የምፅዓት ቀን የቀረበ አስመስሎታል። ከአንገትዋ ቀና ብላ ከተንቀሳቃሽ ስልኳ ላይ ሰዓት ተመለከተች። ከለሊቱ 7 ሰዓት 34 ደቂቃ ይላል። እንቅልፍ የነሳት ቅዝቃዜው አልያም ደግሞ የሰማዩ ነጎድጓድ ድምፅ አይደልም። ይልቁንም በውስጥዋ የተፈጠረው እልህ፣ ቁጭትና ንዴት ስለ ዝናቡ ትኩረት እንዳትሰጥ አድርጓታል።
መተኛት እጅጉን ፈልጋለች፤ ነገር ግን አይንዋ ሊከደን አዕምሮዋ ሊያርፍ ፈፅሞ አልቻለም። በእርግጥ አልጋ ስትቀይር ቶሎ ተላምዳ ወዲያው ወደ እንቅልፍ የመሄዱ ልምድ የላትም። የዛሬው እንቅልፍ ማጣት ግን ከቀየረችው አልጋ ጋር የሚያያዝ አይደለም። ባመነችው መከዳትዋ በወደደችው መገፋትዋ አንገብግቧታል። ለዓመታት ተንከባክባ ያቆየቸው ፍቅሯ እንደ ጉም መምነኑ አንጀትዋን አቁስሎታል።
“ወይኔ ሳምሪ!” እያለች የተኛችበትን ፍራሽ በንዴት ስትደልቅ ነው ያመሸቸው። ‹‹ለምን ግን እንዲህ አደረገኝ? እኔ ለሱ በታመንኩ። ያለሱ ሰው ቀና ብዬ ማየት የማልችል የፍቅሩ እስረኛ አድርጎኝ እሱ እንዴት እኔ ላይ እንዲህ አይነት ክህደት ይፈፅማል? ለዚያውም ከገዛ ጋደኛዬ ጋር! ይባስ ብሎ እኔው አልጋ ላይ። ወይኔ ሳምሪ!›› ትላለች የቁጭት ስሜት እረፍት እየነሳት።
ሳታውቀው የሀሳብ ፈረስ ወደፍቅር ጅማሮዋ ያስጉዛት ጀመር። ገና የሁለተኛ ዓመት የኮሌጅ ተማሪ ሆና ነበር ሳምሶንን የተዋወቀችው። ሳምሶን እጅግ በጣም ተግባቢና ጎበዝ ተማሪ ነበር። ከእርስዋ ጋር ያስተዋወቃት ጉብዝናው ነው። በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሳለች ብዙም ትኩረት የማትሰጠው ትምህርት ኮሌጅ ስትገባ ፈታኝ ሲሆንባት ወሎና አዳርዋ ቤተ መፅሀፍ ሆነ።
ቤተ መፅሀፍ ማዘውተርዋ ደግሞ ከሳምሶን አስተዋወቃት። በተደጋጋሚ የምትቀመጥበት ወንበር ፊት ለፊት ተቀምጦ ሙሉ ትኩረቱን መፅሀፍትና ፅሁፎች ላይ ያደርግ የነበረው ሳምሶን ሳታወራው በዓይን እጅጉን ተላመደችው። ስንት ሰዓት አንብቦ ምን ያህል ዕረፍት እንደሚያደርግ፤ አዘውትሮ ያነበው የነበረው ምን ዓይነት መፅሀፎች እንደነበሩ ሁሉ በደንብ ለይታ ታውቅ ነበር።
አብረው ፊት ለፊት ተቀምጠው ብዙ ሰዓት ከማሳለፋቸው ቀስ በቀስ አቀራረባቸው። ሰላምታ ጀመሩ። ግንኙነታቸው ጠንክሮ አንብበው ሲደክማቸው ለእረፍት ከቤተ መፅሀፍ ወጥተው ንፋስ እየተቀበሉ ማውራትና ይበልጥ መቀራረባቸውን ማጠንከር ጀመሩ። ቀስ በቀስ አብሮ ማንበብና መረዳዳት ገፍቶም ወዳጅነትና ውሎ አድሮ ግንኙነታቸውን ወደ ፍቅር አሳደጉት።
በፍቅር አብረው መሆናቸው ደግሞ ለሳምራዊት የተሻለ ዕድል ፈጠረላትና ይበልጥ ቀርቦ በትምህርቷ ይረዳት ጀመር። ያም እንደ ሳምሶን የተሻለችና ውጤቷ ተማሪ አደረጋት። የሳምሶን ጨዋታ አዋቂነትና በቀላሉ ከሰዎች ጋር የመላመድ ባህሪው ደግሞ ሳምራዊት እጅጉን እንድትወደው አደረጋት። ሳትሰስት አፈቀረቸው። እሱም የምሩን ወደዳት።
ከሱ ጋር በነበራት ግንኙነት ደስተኛ ሆነች። ተመርቀው ወጥተው አንድ ዓመት አንኳን ሳይሞላቸው ከቤተሰብ ተለይተው አብረው ተጠቃለሉ። ለሁለት ዓመታት ያህል የረባ ጠብ እንኳን ሳይገጥማቸው በፍቅር ቆዩ። አንድ መስሪያ ቤት ተቀጥረው መስራታቸው ደግሞ ፍቅራቸው እንዲጠነክር አብሮነታቸው እንዲበረክት ምክንያት ሆነ።
ከመጀመሪያ የፍቅር ግንኙነታቸው ጀምሮ የነበራቸውን ተናፋቂ ጊዜያት አንድ ባንድ እያስታወሰች “ታዲያ ለምን? ለምን? ሳምሶን ለምን?!” እያለች ተንሰቅስቃ አለቀሰች። የፀባቸው መነሻ የሆነችው የራስዋ ጓደኛ ገነት ናት። ከገነት ከአንድ ዓመት በፊት ትሰራበት የነበረው መስሪያ ቤት ውስጥ የተዋወቃቻት ጓደኛዋ ናት። ሳምራዊት መስሪያ ቤትዋን ብትቀይርም ከገነት ጋር እጅግ በጣም ከመግባባታቸው የተነሳ ከስራ ሰዓት ውጪ እየተገናኙ የሚያሳልፉት ከስዋ ጋር ሆነ።
ሳምራዊት የቀድሞ መስሪያ ቤትዋ ውስጥ እያለች ከባልዋ በተጨማሪ ከገነት ጋር በመሆን የምሳ ሰዓታቸውን አብረው በማሳለፋቸው ይበልጥ ወዳጅነታቸው ጠነከረ። ይባስ ብሎ አንዳንድ ሚስጥሮች ከባልዋ እየደበቀች ለገነት የምትነግርበት አጋጣሚ ብዙ ነበር። ሳምራዊት ከገነት ጋር ጥሩ ወዳጅነት መስርታ ባልዋንም አደራ ሰጥታ ወደ ሌላ መስሪያ ቤት ከተዛወረች በኋላ የገነትና የሳምሶን አብሮ መሆን አልተቋረጠም።
ሳምራዊት ወደ ሌላ መስሪያ ቤት መዛወር የገነትና የሳምሶን ጓደኝነት አጠነከረው። በሻይና ምሳ ሰዓታቸውን አብረው ማሳለፍ አዘወተሩ። ሳምራዊት ደጋግማ ባልዋ ጋር ስትደውል ገነት አብራው እንዳለች ደጋግሞ መናገሩ መጀመሪያ ላይ ደስ ትሰኝበት የነበረችው ሳምራዊት እያደር ውስጥዋ ቅሬታ ይፈጥርባት ጀመር። የሳምራዊት እያደር ጥርጣሬ ውስጥ መግባት ደግሞ ጉዳዩ ይበልጥ ውስብስብ አደረገው።
ሳምራዊት ጓደኛዋን ገነትን በባልዋ መጠራጠርዋ ሲብስ የጥርጣሬዋ እውነትነት ማረጋገጫ እራስዋ ገነት ለማድረግ ወሰነች። መጀመሪያ ገነትን እንደ ቅርብ ጓደኛ አየቻት። ባልዋን ከሌላ ሰው እንደምትጠረጥረውና ያንን ጥርጣሬዋን ማረጋገጥ እንደምትፈልግ ለዚህ ደግሞ ገነት ሳምሶንን የወደደችው መስላ ከበፊቱ በላይ እንድትቀርበው፣ አብራው ብዙ ጊዜ እንድታሳልፍና መውደድዋን እንድትገልፅለት ጠየቀቻት።
ለዚያ ደግሞ እስዋ ብቻቸው የሚሆኑበት ጊዜ ማመቻቸት እንደምትችልና ባልዋ ሳምሶንን ችላ በማለት ለገነት ይበልጥ እንዲቀርብ ማድረግን እንደ ሌላ ዘዴ ለመጠቀም ወሰነች። ያንንም አደረገችው። ይህ ደግሞ ገነትና ሳምሶን ብቻቸው እንዲሆኑና ብዙ ጊዜያቸውን አብረው ማሳለፍ አስቻላቸው። የሳምራዊት ፀባይ መቀያየር ሳምሶን ግራ አጋባው በአንፃሩ ደግሞ የገነት እሱን በጣም መቅረብና ከሚስቱ ሳምራዊት የተሻለች ሆና መገኘት አስገረመው።
ገነት እያንዳንዱ እንቅስቃሴያቸውን ለሳምራዊት ሪፖርት ማድረግዋን ቀጠለች። ውሎ ሲያድር የገነትና ሳምሶን ግንኙነታቸው እየጠነከረ የሳምሶንና የሳምራዊት ፍቅር እየተቀዛቀ ሄደ። ነገር ግን ሳምራዊት ይበልጥ የመፈተኛ ዘዴዎች ማመቻቸትዋን ቀጠለቸው። ገነት ለሳምሶን የአብረን እንደር ጥያቄ እንድታቀርብለት መወትወትዋን ቀጠለች። ገነት ይህን ማድረግ ቢከብዳትም ከጓደኛዋ የቀረበላት የእርጅኝ ባሌን ልለየው የሚለው ጥያቄዋ መግፋት ከበዳትና ያንንም አደረገችው።
ሳምሶን ግን በቀላሉ እጅ የማይሰጥ መሆኑን ገነት ለሳምራዊት ስትነግራት “አውቆ የማስመሰል ስራ እየሰራ ነው በጥያቄሽ በርቺ” በማለት ገፋፋቻት። ገነት የፍሬዘር ታማኝ መሆን ሲገርማት የሳምራዊት አጉል ጥርጣሬ ያስገርማት ጀመር። ውሎ ሲያድር ጉዳዩ ውስበስብ እየሆነ ሄደ። ገነት ሳታውቀው እጅግ በጣም የቀረበችውን ሳምሶንን ወደደችው። በታማኝነቱ ምክንያት አፈቀረችው።
ለሳምራዊት ትነግራት የነበረው የአብሮ መዋላቸው እና የሆኑትን ሁሉ መንገር መደበቅ ጀመረች። ይሄኔ ሳምራዊት ገነትን በጥርጣሬ ለማየት አበቃት። ይህም ጥርጣሬዋ ከፍ ብሎ የእውነት ተጣላቻት። ይሄኔ ነው ሁሉ ነገር ገሀድ የወጣው።
ገነት ለሳምሶን ሚስቱ ስታሰልለው እንደነበረና ስለሱ ሳምራዊት እየደወለች እንድታደርግ የምትነግራትን ቀድማ ቀርፃ ያስቀመጠችው የስልክ ድምፅ አሰማቸው። በዚህ ደግሞ ሳምሶን እጅግ ተበሳጨ። በሚስቱ ድርጊት በጣም አፈረ። ስለጉዳዩ ሊያወራት ሲሞክር መካድዋ ደግሞ ይበልጥ በጣም አበሸቀው። ቀስ በቀስ ለሳምራዊ ያለው ፍቅር መንጠፍ ጀመረ። ከገነት ጋር ደግሞ በተቃራኒው በጣም ተላመዱ። ቀስ በቀስም የፍቅር የድብቅ የፍቅር ግንኙነት ጀመሩ።
ይህ ሁሉ ከተኛችበት አልጋ ፊት ለፊት እንደ ተሰቀለ ቴሌቪዥን የሆነ ታሪክ እንደሚያሳያት ሁሉ አንድ ባንድ ታወሳት። ትላንት የባልዋና የገነት ግንኙነት እውነት መሆኑ በዓይኗ በብረቱ አየች።
አዲስ ዘመን ሐምሌ 26/2012
ተገኝ ብሩ