አትክልትና ፍራፍሬ በማከፋፈል የንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩት አቶ አዲስ አለማየሁ ከጅምላ አከፋፋዮች በመረከብ ለሆቴሎች፣ ለሆስፒታሎች እና ለገበያ ማዕከላት አትክልትና ፍራፍሬ ያቀርባሉ፡፡ በሥራው ከ10 ዓመታት በላይ አሳልፈዋል፡፡ በዚሁ ቆይታቸው የሚገጥማቸው ችግሮች በየጊዜው እየሰፋ መምጣቱን ነው የሚናገሩት፡፡ የንግድ ሰንሰለቱ በደላሎች የተሞላ መሆንና የተቆጣጣሪ አካል ድክመት የንግድ ሥርዓቱን የማይፈታ ሰንሰለት አድርጎታል።
አቶ አዲስ እንደሚያስረዱት፤ አትክልትና ፍራፍሬ ከአርሶ አደሩ እስከ ሸማቹ እስኪደርስ ድረስ ያለው የገበያ ሰንሰለት እጅግ የተንዛዛ ነው፡፡ የንግድ ሰንሰለቱ ከአርሶ አደር ተነስቶ የገጠርና የከተማ ደላሎችን አልፎ ጅምላ አከፋፋዮች እጅ ይደርሳል። በዚህም አይቆምም ወደ ቸርቻሪዎች ወርዶ ነው ሸማቾች ጋር የሚደርሰው፡፡ ደላሎች ምርቱን ወደ አከፋፋዮች ሲያመጡ የቫት ደረሰኝ አይቆርጡም፡፡ ጅምላ አከፋፋዮች ምርት ከሚረከቡት ደላላዎች ደረሰኝ ስለማይቀበሉ ለቸርቻሪውም አይሰ ጡም፡፡ ቸርቻሪዎች ግን ለሸማች ሲያደርሱ ደረሰኝ እንዲቆርጡ ይገደዳሉ፡፡ በዚህም ምክንያት ቸርቻሪዎች ያወጡትን ተጨማሪ ወጪ የሚያወራርዱበት ማረጋገጫ የላቸውም፡፡
አቶ አዲስ የገበያው የንግድ ሰንሰለቱ መርዘሙና ሕጋዊ ሥርዓት አለመኖሩ ለግብርና ምርቶች በየጊዜው መወደድ ዋነኛ ምክንያቶች መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡ የምርት እጥረት በሚኖርት ወቅት ደግሞ ይባስ የንግድ ሰንሰለቱ እንደሚረዝም ያስረዳሉ፡፡ እንዲሁም ቸርቻ ሪዎች ጋር ሲደርስ የሚጠየቀው ደረሰኝ ደግሞ በንግድ ሰንሰለቱ መርዘም ተጨማሪ ጫና እንደሚፈጥር ይገልጻሉ፡፡ «በንግዱ ዓለም የሚታየው አሠራር ከመንግሥት ጋር ድብብቆሽ ነው» የሚሉት አቶ አዲስ፤ የንግድ ሥርዓቱን በኃላፊነት እየተመራ በሚያሰራና ኅብረተሰቡን በሚጠቅም ሕግ እየተመራ አለመሆኑን ይናገራሉ፡፡ እንዲሁም በጊዜ መፍትሄ ካልተበጀለት የግብርና ምርቶች ውድነት በልቶ ማደርንም ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ ይሆናል ይላሉ፡፡
የገበያ ሰንሰለቱ መርዘምና የአገር ውስጥ የገበያ ሥርዓቱ ላይ የተንሰራፉ ችግሮች አገሪቱ ግብር በአግባቡ እንዳትሰበስብ፣ ነጋዴው ትርፋማ እንዳይሆን፣ ሸማቹም ምክንያታዊ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ እንዲቸገር አድርጓል፡፡ በአገር ውስጥ የገበያ ሰንሰለት ያለወጪ ትርፋማ የሚሆኑት ደላሎች ናቸው፡፡ የገበሬ ህብረት ሥራ ማህበራትም በቁጥር ከመበራከት ባለፈ እና ምርቶቹን ለማሳያ ያህል ከማቅረብ በዘለለ በገበያው ላይ የፈቱት ችግር እንደሌለ ይናገራሉ፡፡ ከነርሱም ጥሩ ምርት ለማግኘት ተጨማሪ ዋጋ ይጠይቃሉ፡፡ ከህብረት ሥራ ማህበራቶቹ ጥሩ ምርት ለማግኘት ተጨማሪ ገንዘብ ሲከፈል ደግሞ ዞሮ ዞሮ ጫናው ሸማቹ ላይ ይሆናል ሲሉ የገበያው ሰንሰለት መርዘምና ሕጋዊ ሥርዓት አለመያዝ እያስከተለ ያለውን ጫና አመልክተዋል ፡፡
«መንግሥት በዘርፉ ላሉ ችግሮች መፍትሄ ለማምጣት ቢሰራም ለውጥ አልመጣም» የሚሉት አቶ አዲስ፤ አርሶ አደሩ የሚያመር ተውን ምርት በቀጥታ ለአከፋፋዮች እንዳያ ቀርብ ያገደው የቫት ደረሰኝ መቁረጥ አለመቻሉ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ ኅብረተሰቡ የግብርና ምርት ተጠቃሚ እንዲሆን ለማድረግ ደግሞ እሴት ያልተጨመረበት የግብርና ምርት ላይ የሚጣለው ቫት ሊነሳ እንደሚገባ ይጠቁማሉ፡፡ እሴት ባልተጨመረበት የግብርና ምርት የቫት መጨመሩ ቢቀር ገበሬው በቀጥታ ያለደላላ ጣልቃ ገብነት እና በአጭር መንገድ ምርቱን ለአከፋፋዮች ማቅረብ ይችላል የሚል እምነት አላቸው፡፡
የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የንግድ መረጃ ሥራ አመራር ዳይሬክተር ዶክተር ይበልጣል አሰፋ በአገር ውስጥ ገበያ ላይ ያለው ችግር ከአርሶ አደር እስከ ሸማቹ ጫና የሚፈጥር መሆኑን ይገልጻሉ፡፡ አርሶ አደሩ የሥራውን ዋጋ ያህል አለማግኘት፣ ነጋዴውም በተመቻቸ ሁኔታ እየሰራ አለመሆን፣ ሸማቹም ያለ በቂ አቅርቦት ከፍተኛ ዋጋ እያወጣ እንደሚገኝ ይናገራሉ፡፡
በንግድ ሰንሰለቱ እየተጠቀሙ የሚገኙት በምርቱ ላይ ምንም ዓይነት እሴት ሳይጨምሩ የሚሰሩ ደላሎች መሆናቸውን በመጥቀስ የአቶ አዲስን ሃሳብ ያጠናክራሉ፡፡ ደላሎች የንግዱን ሰንሰለት ከማረዝም በተጨማሪ የገበያውን ዋጋ በመቆጣጠር ንግዱ ጤናማ እንዳይሆን እንደሚያደርጉም ያመለክታሉ፡፡ የገበያ ትስስር ደካማ መሆኑ የንግድ ሰንሰለቱ መርዘምና ሕጋዊ አለመሆን ተጠቃሽ መሆናቸውን ያስረዳሉ፡፡ የህብረት ሥራ ማህበራት ጠንካራ እና ሁሉንም አምራች ያቀፉ አለመሆኑ ለችግሩ መፍትሄ ማምጣት አለመቻሉን ያስረዳሉ፡፡
ዶክተር ይበልጣል እንደሚናገሩት፤ የምርቶች አቅርቦትና የገበያ ትስስር የተስተ ካከለና የተረጋጋ አይደለም፡፡ የንግድ ሰንሰለቱ ሥርዓት አልባ ሆኗል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የሚመራው በገበያ መር ባለመሆኑ፣ አቅርቦትና ፍላጎትን በማመጣጠን የሚሰራው ባለመሆኑ ነው፡፡ የግብርና ምርት ንግዱን ገበያው ሳይሆን ደላሎች ስለሚቆጣጠሩት ምክንያታዊ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ እየተንሰራፋ መጥቷል፡፡ በቂ አቅርቦት አለመኖሩ ተጠቃሽ ምክንያት ነው። በሚኒስቴሩ በኩል ከንግዱ ተዋናዮች ጋር ምክክር ከማድረግ እስከ አስተዳደራዊ እርምጃዎችን እንደ መፍትሄ ቢወሰድም ችግሩ ሊቀረፍ እንዳልቻለ ይጠቅሳሉ፡፡
የአገሪቱ የነፃ ኢኮኖሚ አሠራር በአገራዊ እና ማህበረሰባዊ ኃላፊነት፣ በበቂ አቅርቦት፣ በፍትሐዊ ዋጋ እየተተገበረ አለመሆኑን ዶክተር ይበልጣል ይናገራሉ፡፡ ገበያው በአቅርቦት እና ፍላጎት መመጣጠን የሚመራ እንዲሆን ማድረግ ያስፈልጋል የሚል ሃሳብ ያቀርባሉ፡፡ መቅጣት እንዲሁም ማስጠንቀቂያ መስጠት መፍትሄ እያመጣ አለመሆኑን የሚያምኑት ዶክተር ይበልጣል፤ አቅርቦት ሲስተካከል የገበያ ሥርዓቱ ይሻሻላል ባይ ናቸው፡፡ እንዲሁም የገበያውን ሥርዓትና ዋጋ ለመቆጣጠር ዋናው ነገር ስለገበያ ሁኔታና ስለ ንግድ ያለው ግንዛቤ ማስፋፋት ያስፈልጋል፡፡ አርሶ አደሩ እና ጅምላ ነጋዴ ባለሀብቶችን በቀጥታ ማገናኘት የሚቻልበት መንገድ መፍጠርም እንደ መፍትሄ ይጠቁ ማሉ፡፡
የሐሮማያ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ መምህር አቶ ፍሬዘር ጥላሁን ሸማቹ በግብርና ምርት አማራጭም የንግድ ፍትህም አጥቷል ይላሉ፡፡ ይሄ ደግሞ የግብይት ሥርዓቱን የመቆጣጠሪያ መንገድ ድክመት ያስከተለው መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ ባህላዊ የንግድ ሥርዓቱ ላይ ደላላዎች ሲጨመሩበት ደግሞ የንግድ ሰንሰለቱ እንዲረዝምና ጤናማ እንዳይሆን እንደሚያደርግም ይገልፃሉ፡፡
የምግብ ግብዓቶች ምርት ወጪ ሲጨምር ምርቱ ላይም ጭማሪ ይኖራል፡፡ ነገር ግን አሁን ያለው ሁኔታ ለምሳሌ የፍራፍሬ ዋጋ ሳይጨምር የጭማቂ ዋጋ መጨመር ሁኔታ በመኖሩ ጤናማ አለመሆኑን ያሳያል፡፡ የአገር ውስጥ የግብርና ምርቶች ከምርት ሂደት ጀምሮ ምን ዓይነት ወጪ እንደሚያወጡ ከመመዝገብ አንስቶ ምርቱ ሸማች ጋር እስኪደርስ ያለውን መንገድ ሕጋዊና ግልጽ ማድረግ ያስፈልጋል የሚል አቋም አላቸው፡፡
አቶ ፍሬዘር እንደሚናገሩት፤ አቅርቦት ባልጨመረበት ሁኔታ የሸማቾች ፍላጎት እየጨመረ መምጣቱ ምንም ያህል ዋጋ ቢጨምር ሸማች መግዛቱ አይቀርም በሚል እሳቤ ሕዝቡ እየተጎዳ ነው፡፡ የግብይት ሰንሰለቱ ግልጽና ትክክለኛ አለመሆኑ ሸማቹ እንዲበደል ያደርጋል፡፡ ለምን አለአግባብ ዋጋ ይጨምራል አልገዛም የማለት አቅም ሊኖረው ይገባል፡፡ የገበያው ተቆጣጣሪ እንዲሆን ደግሞ አማራጭ ያስፈልጋል፡፡ በአንድ ዓይነት የንግድ ሰንሰለት እየተሰራጩ ያሉት የግብርና ምርቶች ተጨማሪ አማራጭ ሊኖር ይገባል፡፡ ነጋዴውም የሚያተርፈው የሕዝቡን አቅም ባላማከለ መልኩ ዋጋ በመስቀል ሳይሆን ኃላፊነት በተሞላ በትና ጤናማ በሆነ መንገድ እንዲሆን በጋራ ሊሰራ ይገባል፡፡ እያንዳንዱን የገበያ ሁኔታ መንግሥት መቆጣጠር ስለማይችል የገበያ ዋጋ ዋና ተቆጣጣሪ መሆን ያለበት ሸማቹ ነው፡፡
የፕላንና ልማት ኮሚሽን የ2010 የማክሮ ኢኮኖሚ አፈጻጸም ሪፖርት እንደሚ ያመለ ክተው የ2010 ዓ.ም አገር አቀፍ የዋጋ ንረት ሁኔታ ምግብና ምግብ ነክ የሆኑ ሸቀጦች በ16 ነጥብ አምስት በመቶ ጨምሯል፡፡ ከ2006 ዓ.ም ጀምሮ የዋጋ ንረቱን ለመቆጣ ጠርና ለመቀነስ ከታቀደው አንጻር ከፍተኛ መሆኑን ሲያመለክት፤ በ2010 ዓ.ም የምግ ብና ምግብ ነክ ሸቀጦች ዋጋ ንረት 20 ነጥብ 9 በመቶ የደረሰበትም ጊዜ እንደነበር ያሳያል፡፡ በተለይ ከውጭ ምንዛሪ ተመን ለውጥ እና እጥረትን እንደ ሽፋን በመጠቀም ከጉዳዩ ጋር ተያያዥነት የሌላቸውን የግብርና ምርቶች በማከማቸት፣ እጥረት በመፍጠር፣ በምግብ ሸቀጦች የዋጋ ንረት እንዲያጋጥም ምክንያት መሆኑን አመልክቷል፡፡
ሰላማዊት ንጉሴ