ቅድመ – ታሪክ
ለእሱ ቄራና አካባቢው ተወልዶ ያደገበት ብቻ አይደለም። እንጀራውን የበላበት፣ ህይወቱን ያቀናበትና ያሻውን ሁሉ የፈጸምበት ስፍራ ነው። ልጅነቱ በመከራ የተፈተነ በመሆኑ ተመችቶት አላደገም። ወላጆቹ ችግረኞች ነበሩ። እንደ እኩዮቹ ትምህርቱን የጀመረው ገና በጠዋቱ ቢሆንም ከአራተኛ ክፍል መሻገር አልቻለም። ለዚህም ምክንያቱ ቤተሰቦቹ እሱን ለማስተማር እጃቸው ማጠሩ ነበር።
ቢኒያም ከዚህ በኋላ ህይወቱን ለመምራት ያገኘውን ሁሉ መስራት ግድ አለው።ሆዱን ችሎ ቤተሰቦቹን ለማገዝ የመጀመሪያ ምርጫው በቄራ በረት ለከብቶች እረኝነት መቀጠር ሆነ። በቄራ የከብቶች ማደሪያ በአነስተኛ የቀን ክፍያ ገንዘብ ማግኘት ሲጀምር ለፍላጎቱ መሆን አላቃተውም።
ቄራ የአቅምን ሰርተው የሚያገኙበት ስፍራ መሆኑ እንደቢኒያም ላሉ የሰፈር ልጆች በእጅጉ የሚጠቅም ነው። ስፍራውን ለከብቶች ማደሪያ ከሚያደርጉ ተመላላሽ የከብት ነጋዴዎች በየዕለቱ የሚገኘው ጥቅም ላወቁበት ቁምነገር ሰርቶላቸዋል። በርካቶች ገቢውን ከራሳቸው አልፈው ለቤተሰቦቻቸው ያውሉታል። አንዳንዶች ደግሞ ለዕለት ፍላጎት፣ ለመጠጥና ጫት ያደርጉታል።
ጠበኛው ወጣት
ቢኒያም በቄራ የከብቶች እረኛ መሆን ከጀመረ ወዲህ ለኪሱ የሚሆን ገንዘብ አላጣም። ከስራ መልስ ጎራ በሚልባቸው መጠጥ ቤቶች ጨዋታ ሲጀምር ግን ከብዙዎች አይስማማም። እንደውም አንዳንዴ ከስድብ አልፎ ለድብድብ ሁሉ ይጋበዛል። ከዚህ ባስ ባለ ጊዜም ለክስና ለእስር ይዳረጋል።
የቢኒያምን የተለመደ ባህርይ የሚያውቁ በርካቶች ቀረብ ብለው ሊመክሩት ሞክረዋል። አንዳንዶቹም ይህ ክፉ ልማዱ አንድ ቀን ከችግር ሊጥለው እንደሚችል እያዋዙ ነግረውታል። ቢኒያም ለጊዜው ምክራቸውን የሰማ ይመስላል። ለጥቂት ቀናት ከራሱ ታርቆም ሰላማዊ ለመሆን ይሞከራል። ከቀናት በኋላ ግን የነበረው ማንነት ያገረሽበትና ለጠብና ድብድብ ሲጋበዝ ይስተዋላል።
አንድ ቀን ቢኒያም መሀመድ ከተባለ ሰው ጋር ጠብ ገጠመ። እንደዋዛ የተነሳው ጭቅጭቅ ለድብድብ ሲበቃ ያስተዋሉ ገላጋዮች ከመሀል ገብተው ጠቡን ለማብረድ ሞከሩ። በሁለቱ መሀል የሆነው አለመግባባት ለጊዜው ጋብ ያለ መሰለ። ገላጋዮቹ ተዘናግተው በጨዋታ ውስጥ እንዳሉ ግን ድንገት ቢኒያም ጠቡን ጭሮ ነገሩን ቆሰቆሰው።
ሁለቱ ሰዎች በድጋሚ ተያያዙ። አስቀድሞ ጉዳዩን ያሰበበት ቢኒያም መሀመድን ለማጥቃት አልተቸገረም። ያለውን ሀይል አሳባስቦ ተጋጣሚውን ለመጣል ታገለ። ጉዳዩ ድንገቴ የሆነበት መሀመድ በቢኒያም ጉልበት ተሰብሮ ለመውደቅ አፍታ አልቆየም። እጅ ሰጠ። በድብድቡ ክፉኛ ተጎድቶም አካሉ በደም ተለወሰ።
ዳግመኛ ለግልግል ከመሀል የገቡ ቢኒያምን ገስጸው ተጎጂውን ለህክምና አደረሱ። ውሎ አድሮ ቢኒያም በመሀመድ ክስ ቀርቦበት ጣቢያ ቀረበ። ፖሊስ ጉዳዩን ከስር መርምሮ ጥፋተኛውን ለየና መሀመድን ፍርድ ቤት አቀረበው። ፍርድ ቤቱ የተበዳይን ቃል አዳምጦና እውነታውን በምስክሮች አረጋግጦ ለቢኒያም ድርጊት የሚገባውን የሶስት ወራት አስራት ፈረደበት።
ቢኒያም ለእስር ቅጣቱ ወደቂሊኒጦ ማረሚያ ቤት ወረደ። ከጥቂት ቀናት በኋላ ግን ቅጣቱ ወደገንዘብ ዋስትና ተቀይሮለት ከእስር ተለቀቀ። ከማረሚያ ቤት ከወጣ በኋላም የከብት እረኝነት ስራውን ጀመረ። እንጀራ የሆነውን የቄራ ከብቶችን የመጠበቅ ስራ መቼውንም መተው አይፈልግምና ቢኒያም ከሌሎች ጋር ሰላም ሆኖ ለመቀጠል ሞከረ።
አንዳንዴ መለስ ብሎ የትናንቱን ያስታውሳል። ያለፈበትን መንገድ፣ ያሳለፈውን ችግርና ውጣ ውረዱ ሁሉ ትውስ ይለዋል። የተጣላቸውን ሰዎች ድርጊት ደግሞ በተለየ እያሰበ በሀሳብ ይቃኘዋል። ከጠብ በኋላ ያለውን ጥላቻም በቀላሉ አይተወውም። ቂም ቋጣሪ ልቡ ሁሌም ቢሆን ጥላቻን ይይዛል። ባላንጦቹን ባያቸው ጊዜም ጠብ ናፋቂ ማንነቱ ይፈትነዋል።
ቢኒያም ከመሀመድ በተጋጨ ጊዜ አሸናፊነቱ የእሱ እንደነበር ያውቃል። በዚሁ ሰበብ ተከሶ ማረሚያ መውረዱንና በገንዘብ ዋስ መለቀቁን ሲያስበው ግን ጥላቻው በእጥፍ ይጨምራል። ይህ ጥላቻ የሚሽርለት ዳግም አግኝቶ የልቡን ሲያደርስ እንደሆነም ለራሱ ሲነግረው ቆይቷል። ይህን ደግሞ መሀመድን ባየውና ባገኘው ቁጥር ባመቸው ምልክት ሁሉ ሲገልጽለት ቆይቷል።
ዳግመኛ እስር
ቢኒያም እንደቀድሞው ሁሉ ህይወቱን ቀጥሏል። አሁንም በእረኝነት ከተቀጠረበት የቄራ ከብቶች ማደሪያ የሚያገኘው ደመወዝና ጥቅም አልቀረበትም። ከሴት ጓደኛ ጋር መታየቱን ያስተዋሉ አንዳንዶች ደግሞ በትዳር ቢሰበሰብ ሲሉ ተመኝተዋል። በርካቶችም የራሱን ህይወት ቢጀምር ክፉ ልማዱን ሊተው እንደሚችል ገምተዋል። ቢኒያም ግን አሁንም አብሮት የኖረው ሀይለኝነት እየተከተለው ነው።
ከዕለታት በአንዱ ቀን ቢኒያም ዳግመኛ ከአንድ ሰው ጋር ተጣለ። ጠቡ የከፋ ግጭት አስከትሎም ጠበኛውን በድብደባ ጎድቶ ለክስ ተዳረገ። በተደጋጋሚ ክሱን ያስተናገደው ፖሊስ ጣቢያ ጉዳዩን በእርቅ መፈጸም ሳያሻው ተከሳሹን ወደ ፍርድ ቤት ላከ። ፍርድ ቤቱም የተፈጸመውን የድብደባ ወንጀል ከግምት አስገብቶ በቢኒያም ላይ አስራትን በየነ ።
ቢኒያም የእስራት ፍርዱን ተቀብሎ ማረሚያ ቤት ወረደ። ለሁለት ወራት ያህል ከቆየ በኋላም ዳግመኛ በገንዘብ ዋስ ከእስር ተለቆ ወጣ። ተመልሶ ወደ እረኝነት ስራው ከገባ በኋላ የተለመደ ህይወቱን መምራት ያዘ። አብሮት የኖረው ቂመኝነትና ውስጡ የመሸገው ክፉ ጥላቻም ጠብ ከገጠማቸው ጋር ሁሉ የጎሪጥ እያተያየ ጥርሰ ያናክሰው ያዘ።
አሁን ቢኒያም የሚጣላቸው ሰዎች በርክተዋል። ትዕግስት አልባነቱን የተረዱ ብዙዎችም ከእሱ መራቅ ጀምረዋል። በየቀኑ ከኪሱ የማይለየው ስል ቢላዋ አሁን የቅርብ አጋሩ ያህል እንደሆነ እየተሰማው ነው። በወጣ በገባ ቁጥር ከጎኑ እንደሻጠ ይዞት ይጓዛል። በአጋጣሚ የተጣላቸውን ጠበኞቹን ባየ ጊዜም ቢላዋውን እየነካካ እነሱ ላይ ያፈጣል።
ጥር 12 ቀን 2010 ዓም
የጥምቀት በዓል በድምቀት ተከብሮ አልፏል። አሁንም ግን በቄራና አካባቢው ያለው የበዓል ድባብ አልቀዘቀዘም። በዓሉ የአደባባይ እንደመሆኑ በርካቶች በሀገር ባህል ልብስ ተውበው ስፍራውን እንዳደመቁት ይታያሉ። ቢኒያም ከስራ መልስ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ ኳስ ለማየት ወደ አንድ ሬስቱራንት ዘለቀ። ጨዋታውን ጥቂት ተመልክቶም ወደ ጎፋ ማዞሪያ ለመሄድ ተነሳ።
ጎፋ የሄደበት ምክንያት የሴት ጓደኛውን ለማግኘት ነበርና በቀጠራት ቦታ አግኝቶ አብሯት ሲጨዋወት ቆየ። ከጓደኛው ጋር አሳልፎ ወደ ቄራ ሲመለስም ምሽት ሁለት ሰዓት ሆኖ ነበር። ቢኒያም ተመልሶ ወደሬስቶራንቱ የሄደው ለብቻው ሆኖ ለመዝናናት ነበርና ወንበር ስቦ ከአንድ ጥግ ተቀመጠ። የሚፈልገውን አዞም ዓይኖቹን ከመግቢያው በር ላይ ተከለ።
የሬስቶራንቱ ፈዛዛ መብራት በድምቀት የፈገገ ባይሆንም ወጪና ገቢውን ለመለየት የሚያዳግት አይደለም። የቢኒያም ዓይኖች ፈዛዛውን ብርሀን አሸንፈው አካባቢውን ሲላመዱ ግራና ቀኝ ማስተዋል ያዙ። አሁን በቤቱ የተቀመጡ እንግዶችን በቀላሉ መለየት ይቻላል። የሚበሉትንና የሚጠጡትን ጭምር ለይቶ ለማውቅ አዳጋች አይደለም።
ቢኒያም ያዘዘውን መጠጥ አንዴ እንደተጎነጨ ዓይኖቹን ከወዲያ ወዲህ ላካቸው። ከእሱ በተቃራኒው ጥግ ከተቀመጡት መሀል አንደኛውን ሰው ሲመለከት ግን ውሰጡ በንዴት ጋየ። ሰውዬው መሀመድ ነው። ከዚህ ቀድሞ ከእሱ ጋር ተደባድቦ ለእስር መዳረጉንና በገንዘብ ዋስ መፈታቱን የሚረሳው አልሆነም። ይህን እያሰበ ዓይኖቹን ዳግመኛ ላካቸው። ልክ እንደሱ ሁሉ መሀመድም በንዴት ጥርሱን ነክሶ እያስተዋለው ነው። ቢኒያም ማንነቱን ባረጋገጠ ጊዜ ተቁነጠነጠ። ከዚህ ቀድሞ በነበራቸው ጠብ ፍርድ ቤት አቁሞ ለእስርና ለገንዘብ መቀጮ እንደዳረገው አስታውሰ። ይህን ደጋግሞ ሲያስታውሰ የኖረ ቂሙ አገርሽቶም ውስጡ በትኩሳት ጋየ።
መሀመድ በበኩሉ ከጊዚያት በፊት በቢኒያም የሆነበትን ሁሉ አስታወሰ። በወቅቱ በፈጸመበት በደል ለክስ አቅርቦ አስፈርዶበታል። ወዲያው ግን በገንዘብ ዋስ መለቀቁን ሰምቶ ሲበሳጭ ቆይቷል። ዛሬ ደግሞ ይህ ባላንጣው ከፊት ለፊቱ ሆኖ እየገላመጠው ነው። ሁኔታውን ሲያስተውል ይባስ ንዴቱ ጨመረ።
ጥቂት ቆይቶ ቢኒያም ወንበሩን ቀየረ። መሀመድ ወዳለበት ተጠግቶም በነገር ይጎሽመው ያዘ። መሀመድ ድርጊቱን መታገስ አልሆነለትም። እንደበፊቱ ተዘናግቶ መረታት ቢከብደው ጠጋ ብሎ ስድብ ጀመረ። በጸያፍ ቃላት እየደጋገመም እናቱን ይሰድብና እሱን ያወርድ ጀመር። ቢኒያም ከመሀመድ አንደበት የሚወጣውን ቃል በሰማ ጊዜ ከተቀመጠበት ተነሳ።
መሀመድ የቢኒያምን መነሳት እንዳየ ሳይቀደም ሊቀድመው አሰበ። ሳያስበው ቀርቦም አንገቱን አንቆ ሊጥለው ተጠጋ። ቢኒያም መሀመድ በንዴት ተውጦ የሚናገረውን በዝምታ እያዳመጠ ቀረበው። ብሽቀቱ በፊቱ ላይ በግልጽ ይታያል። ከጎኑ የሻጠውን ባለጥቁር እጀታ ቢላዋ በቀኝ እጁ ዳሰሰው። ባስቀመጠበት እንዳለ ነው።
ድንገት አንገት ለአንገት ሲያያዙ የሆቴሉ ድባብ ተረበሸ። ሁኔታቸውን ያዩ አንዳንዶች መሀል ገብተው ለመገላገል ሞከሩ። አልቻሉም። ቢኒያም የመሀመድን አቅም አስተውሎ ከጎኑ ያለውን ጥቁር ቢላዋ አወጣ። ይህን ያየው መሀመድ ይበልጥ ብስጭት ገባው። ያለውን ሀይል ተጠቅሞም ስለቱን ወደባላንጣው መልሶ ሊወጋው ታገለ። አልቻለም። የቢኒያም ሀይል ከእሱ ልቆ በረታ። የቢላዋውን አቅጣጫ መልሶም መሀመድ ደረት ላይ ደጋግሞ አሳረፈው።
ቢኒያም የመሀመድን ተጎድቶ መውደቅ ባየ ጊዜ ስለቱን ከደረቱ ነቅሎ ከሆቴሉ ሮጦ ወጣ። በሆቴሉ ያሉ ሰዎች እሱን ከመያዝ ይልቅ በወደቀው መሀመድ ላይ ማተኮራቸው ለማምለጥ አገዘው። ቆም ብሎ ሳያስብ እግሩ ወደመራው አቅጣጫ አሳብሮ ሮጠ። ጨለማውን አቋርጦ ከአንድ ሰዋራ ቦታ ሲደርስም የቆመበት ስፍራ አርባ ሁለት ቀበሌ ስለመሆኑ አወቀ። ትንሽ ሲረጋጋ በእጁ ላይ ደም የነካው ቢላዋ ስለመያዙ አስተዋለ፤ጊዜ አላጠፋም። ቢላዋውን ወንዝ ውስጥ ጨምሮ ወደፊት ገሰገሰ።
ቢኒያም መንገዱን በሩጫ እያሳበረ መካኒሳ አካባቢ ደረሰ። ከነበረበት መራቁን ሲያውቅም ጥቂት ራሱን አረጋግቶ ቆም ብሎ አሰበ። አልጋ ይዞ መተኛት አላስፈለገውም። በመንገዱ እየተዘዋወረ እስኪነጋጋ ቆየ። ታክሲ ይዞ መናኸሪያ ሲደርሰ ወደጅማ የሚሄድ አውቶቡስ ተመለከተ። አላንገራገረም። ትኬት ቆርጦ ወንበር ያዘና ጉዞውን ጀመረ። አውቶቡሱ መንገድ እንደቀጠለ ቢኒያም ምሽት ላይ የፈጸመውን ድርጊት እያሰበ ተጨነቀ። አተኩሮ ያየውን ሁሉ እየጠረጠረም በመሳቀቅ ተጓዘ።
ጥቂት ቆይቶ ከአንድ የቅርብ ጓደኛው ዘንድ ስልክ ሊደውል ሞባይሉን አነሳ። እንደሰበው ግን ፈጥኖ ቁጥሮቹን አልነካም። እየተሳቀቀ መደወሉን ተወና ዳግመኛ በሀሳብ ሰመጠ። ውስጡ እየፈራና እየተጨነቀም በትካዜ ቆዘመ። ጥቂት ቆይቶ ራሱን አበረታታ። የሞባይሉን ቁጥር ወደጓደኛው እየመታ ከወዲያኛው ጫፍ የስልኩን መነሳት ጠበቀ። ጓደኛው ሰላምታ ሳያስቀድም የመሀመድን መሞት ፈጥኖ አረዳው።
ቢኒያም ጅማ ደርሶ ከአውቶቡሱ እንደወረደ የሚያደርገው ጠፋው። እግሮቹን እየጎተተ ከማረፊያው ሲደርሰም በከፋ ድንጋጤ ውስጥ ሆነ። ቀጣዩ ቀናት በእጅጉ የተጨነቀበት፣ የፈራበትና ያያቸውን ሁሉ የሚጠራጠርበት ጊዚያት ሆነው አለፉ።
የፖሊስ ምርመራ
ፖሊስ በዕለቱ በሬስቶራንቱ ስለተፈጸመው ወንጀል ጥቆማ እንደደረሰው ጉዳዩን ለማጣራት በስፍራው ደረሰ። በሟች አስከሬን ላይ ተገቢውን የቴክኒክ ምርመራ አካሂዶ ወደ ሆስፒታል ከላከ በኋላም አስፈላጊ የሚባሉ መረጃዎችን አጣራ። ከዓይን እማኞች የተገኘው ምስክርነት በሙሉ ወደ ቢኒያም የሚያመለክት ሆኖ አገኘው። በምክትል ሳጂን አዲስ መቻል የሚመራው ቡድን በየቀኑ የሚያገኘውን መረጃ በመዝገብ ቁጥር 8331/10 ላይ እያሰፈረ ጥልቅ ምርመራውን ጀመረ።
ወንጀሉ በተፈጸመ ማግስት የተገኘው ጥቆማ ተጠርጣሪው ከከተማ ርቆ መውጣቱን የሚያመለክት ነበር። ፖሊስ ከጅማ ፖሊስ ጋር ባደረገው የቅንጅት ስራ ቢኒያም በጅማ ከተማ ከሚገኝ አንድ ሆቴል መደበቁን የሚጠቁም ሆነ። ከሶስት ቀናት በኋላ በተቀናጀ የፖሊስ ሀይል በህግ ቁጥጥር ሰር ሲውልም የፈጸመውን ወንጀል አንዳችም ሳይክድ በሰጠው የዕምነት ቃል ፈርሞ አረጋገጠ።
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 10/2012
መልካምስራ አፈወርቅ