በየዓመቱ መስከረም 24 የሚከበረው የዓለም መምህራን ቀን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ40ኛ፣ በኢትዮጵያ ደግሞ ለ32ኛ ጊዜ በደብረብርሃን ከተማ ተከብሮ ውሏል። በዓሉን በማስመልከትም በኢትዮጵያ መምህራን ማህበር (ኢመማ) እና በደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የጋራ ትብብር መስከረም 26 እና 27/2012 ዓ.ም በወቅታዊ የሀገራችን የትምህርት ተደራሽነት፣ ተገቢነትና ጥራት ላይ ያተኮረ አገር አቀፍ ኮንፈረንስ ተካሂዷል።
በዩኒቨርሲቲው መሰብሰቢያ አዳራሽ በተካሄደው ኮንፈረንስ ላይ የትምህርት ሚኒስቴር የስራ ኃላፊዎች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዚዳንቶችና ተወካዮች፣ ምሁራን፣ ተመራማሪዎች፣ የየክልሎች የትምህርት ቢሮ ኃላፊዎች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የታደሙ ሲሆን የተለያዩ ጥናታዊ ፅሁፎች ቀርበውም ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል።
ለውይይት የቀረቡት ስራዎች አስራ አራት ሲሆኑ በርዕሰ ጉዳዮቻቸው የተለያዩ፤ አጠቃላይ ማእቀፋቸውም በአሁኑ ሰዓት አገሪቱ እየተከተለች ያለችው የትምህርት አቅጣጫ ላይ ያተኮሩ ሆኖ፤ በተለይ የትምህርት ተደራሽነት፣ ተገቢነት እና የትምህርት ጥራትን ማዕከል ያደረጉ ነበሩ።
የተመረጡትን 14 ጥናታዊ ፅሁፎች በተመለከተ ያነጋገርናቸው የኢመማ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ዮሐንስ በንቲ እንደገለፁልን ጥናት የተካሄደባቸው ርዕሰ ጉዳዮች በአጠቃላይ 54 ሲሆኑ ካለው ጊዜ አኳያ 14ቱ ተመርጠው ለውይይት የቀረቡ ናቸው። ሁሉም ጥናቶች በግብአትነት የሚወሰዱና የሚሰራባቸው ናቸው። ሁሉም የአገራችንን ትምህርት ታሪካዊ ዳራ የፈተሹ፣ ያለበትን ሁኔታ የመረመሩና የወደፊቱን አቅጣጫ ያመላከቱ ከመሆናቸው አኳያ ተፈላጊነታቸው ከፍተኛ ነው።
ጥናታዊ ፅሁፎቹ አገራችን በአሁኑ ሰዓት ያጋጠማትን የትምህርት ጥራት ችግርና በእውቀትና ክሂሎት ሙሉ የሆነ ብቁ የተማረ የሰው ሀይል የማፍራት ችግር፤ እንዲሁም ችግሩን በዘላቂነት ከመፍታት አኳያ ምን ማድረግ እንዳለባት፣ የአገራችንን የሰለጠነ የሰው ሀይል ፍላጎት፣ የመምህራንን ታሪካዊና ወቅታዊ ሁኔታ፣የወጣቶችን የትምህርት ፍላጎት፣ ተሳትፎና አቅም ከወቅቱ የገበያ ፍላጎት አንፃር የቃኙ፤ ከአገራችንም አልፈው ዓለም አቀፋዊውን የትምህርት ፍልስፍና፣ የመማር-ማስተማር ሂደትና የመምህራንን ጥራት፣ ብቃትና ደረጃ በሚገባ የፈተሹ በመሆናቸው ለትምህርትና ምርምር ተቋማት፣ ፖሊሲ አውጪዎችና ለተመራማሪዎች ያላቸው ጠቀሜታ በቀላሉ የሚታይ አለመሆኑንም ዶ/ር ዮሐንስ ተናግረዋል።
የማህበሩ የውጪና ያገር ውስጥ ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጫንያለው ታፈሰወርቅን ስለጥናታዊ ፅሁፎቹ፣ ስለተወያዮቹ ተሳትፎና ስለተገኘው ግብአት ጠይቀናቸው ጥናቶቹ ከመጀመሪያው ጀምሮ እስከ መጨረሻው ድረስ ተገቢውን የጥናትና ምርምር ሂደት አልፈው እዚህ የደረሱ መሆናቸውን፤ የታዳሚ ምሁራንም ተሳትፎም በጣም አስደሳች፣ አገርና ህዝብን ማዕከል ያደረገና ተገቢውን ግብአት ያስገኘ መሆኑን ተናግረዋል።
የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ጊዜያዊ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ደረጀ አንዳርጌ ኮንፈረንሱንና የጥናትና ምርምር ስራዎቹን አስመልክተው የተናገሩ ሲሆን ስራዎቹ የተካሄዱት ውይይቶችና የተሰጡት የመፍትሄ ሃሳቦች ከፍተኛ ግብአት በመሆን በትምህርቱ ዘርፍ የተደቀኑብንን ዘርፈ ብዙ ተግዳሮቶች ለመቅረፍ በአገር አቀፍ ደረጃ እየተደረገ ያለውን ጥረት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያግዙና ዘላቂ መፍትሄ እንደሚያስገኙ፤ የትምህርት ጥራትን ከማስጠበቅ፣ ተደራሽነትን ከማስፋት፣ ፍትሀዊነት ከማሰፈን፣ አገራችን የሚያስፈልጓትን ብቁ የሰው ሀይል ከማፍራት፣ የወጣቱን ስነምግባር ከማነፅ፣ ወዘተ አኳያም ድርሻቸው የጎላ እንደሚሆን ገልጸዋል።
ይህን አይነቱን አገር አቀፍ ኮንፈረንስም ሆነ ሌሎች በትምህርት ላይ የሚደረጉ ተመሳሳይ ተግባራት የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ፣ ምሁራኑና የዩኒቨርሲቲው ማናጅመንት ምን ጊዜም እንደሚደግፉና እንደሚተባበሩ የገለፁት ዶ/ር ደረጀ ሌሎች ተቋማትም ተመሳሳይ አቋም እንዲኖራቸው አሳስበዋል።
በዚህ “Teaching, Learning, and Community Services for National Development” በሚል አጠቃላይ ስያሜ በተጠራው አገር አቀፍ ኮንፈረንስ ላይ ከቀረቡት ጥናታዊ ፅሁፎች፣ ከተደረጉት ውይይቶችና ከተሰጡት አስተያየቶች በየደረጃው በሚገኙ የትምህርት ተቋማት በቀላሉ የማይታይ፣ ፈጣንና ዘላቂ መፍትሄን የሚሻ የትምህርት ጥራት ችግር መኖሩን፤ በመምህራን ልማት፣ ጥራት፣ ብቃትና የሙያ ፍላጎት/ፍቅር እንዲሁም ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ ዙሪያ በርካታ ችግሮች መኖራቸው ታይቷል። ትውልድና አገር አደጋ ላይ ከመውደቃቸው በፊት በፈጠነ መልኩ ብዙ ስራዎች መሰራት እንዳለባቸው፤ እንዲሁም ከስነ-ምግባር ጀምሮ እስከ ተነሳሽነትና ፍላጎት አለመኖር፤ አቋራጭ መንገድን መሻት፤ ትምህርት ለመከታተል እንኳን ፍላጎት ያለመኖር እና የመሳሰሉ ውስብስብ ችግሮች በተማሪዎች በኩል እንደሚስተዋል፤ እነዚህን ችግሮች ከመፍታት አኳያ ብዙ እንዳልተሰራና ሊሰሩ የሚገቡ ጉዳዮች በርካታ መሆናቸውን ለመረዳት ተችሏል።
ከቀረቡት ጥናታዊ ፅሁፎች በጎላ መልኩ ተሳታፊዎችን ሲያነጋግር የነበረው ሌላው ጉዳይ በመማር-ማስተማሩም ሆነ ባጠቃላይ ትምህርቱ ዘርፍ የሚታዩ ችግሮች ምንጮቻቸው በርካታ መሆናቸው እየታወቀ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት የሚጠበቅባቸውን ተግባርና ሀላፊነት ሲወጡ አለመታየታቸው ነው።
ተሳታፊዎች እንደሚሉት አገር ያለ ትምህርትና የተማረ የሰው ሀይል የሚታሰብ ጉዳይ አይደለም፤ እድገትና ብልፅግናም እንደዛው። በትምህርትና መልካም ስነምግባር የታነፀ፣ እራሱንና ማንነቱን በውል የተገነዘበ፣ ብዝሀነትን የተረዳ፤ አገሩን፣ ወገኑንና ባህሉን ጠንቅቆ የሚያውቅ . . . ትውልድ ካልተገነባ ወደፊት እንዲኖረን የምንፈልገው አገር ሊኖረን አይችልም። በመሆኑም ትውልድና አገር የመገንባት፣ ባህልንና ማንነትን/ኢትዮጵያዊነትን የማስረፅ ተግባር የአንድ ወገን የቤት ስራ አለመሆኑ እየታወቀ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ሃላፊነታቸውን ከመወጣት ወደ ኋላ ማለት አይገባቸውምና ሁሉም ሃላፊነቱን በአግባቡ ሊወጣ ይገባዋል። ለዚህ ደግሞ ጊዜው አሁን ነው። በተለይ በመምህራን ልማትና በተማሪዎች በኩል የሚታዩ ችግሮችን መፍታት ላይ ሳይዋልና ሳይታደር መፍትሄ ማፈላለጉ ላይ ሊሰራ ይገባል። ይህ ካልተደረገ ተተኪ ትውልድ ማፍራት አይቻልም።
ከኢመማ ከተገኘው መረጃ መረዳት እንደተቻለው የዘንድሮው የዓለም መምህራን ቀን አከባበር “Young Teachers: The Future of The Profession” በሚል መሪ ቃል ታጅቦ የተከበረ ሲሆን ይህም “ትምህርት ዓለም አቀፍ” (Education International /EI/) እና ሌሎች ማለትም ዓለም አቀፍ የሰራተኞች ድርጅት (ILO)፣ ዩኒሴፍ፣ እና የተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም (UNDP) በጋራ ሆነው ያዘጋጁትና ያፀደቁት፣ የወቅቱን የዓለማችንን ሁኔታና ወጣቱ ያለበትን አጠቃላይ ይዞታ ያገናዘበ መሪ ቃል ነው። የመሪ ቃሉ መልእክትና ፍሬ ሀሳብም የወጣቱን ተተኪነት፤ ወጣት መምህራን ወደ ሙያው እንዲመጡና ሙያው እንዲቀጥል ማድረግን ታሳቢ ያደረገ መርህ ነው።
የማህበሩ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ዮሐንስ በንቲ እንደሚናገሩት ወጣቱን የሙያው ፍቅር እንዲኖረውና ወደ መምህርነት እንዲመጣ ለማድረግ መንግስታት በቂና ተመጣጣኝ የክፍያ ስርአትን ተግባራዊ ሊያደርጉ ይገባል። መንግስታት ወጣቱ መምህርነትን ቀዳሚ የሙያ ምርጫው ሊያደርግና ወደ ሙያው በመምጣት በጡረታ የሚሰናበቱትን አንጋፋ መምህርን በመተካት ዘርፉን ማስቀጠል እንዲችል ሁኔታዎችን ከወዲሁ ማስተካከልና ማመቻቸት ይጠበቅባቸዋል። ይህ ካልተደረገ በትምህርት ጥራትም ሆነ የተማሪዎች ጥራት ያለው ትምህርት የማግኘት መብታቸው ላይ ተፅእኖ ይፈጥራል።
ከላይ እንደተመለከተነው በትምህርቱ ዘርፍ በርካታ ችግሮች አሉ። በመሆኑም መፍትሄ ሊፈለግላቸው ግድ ነው። ይህ እውን የማይሆን ከሆነ ግን በየትምህርት ተቋማቱ “በ20… በአፍሪካ የመሪነት ሚናን መጫወት”፣ “በ2025 ከዓለም የልህቀት ማእከል . . . በመሆን” የሚሉትን ዓላማ፣ ራዕይና መሰል ጉዳዮች ማሳካት ስላቅ ይመስላልና አስቸኳይ መፍትሄ ሊፈለግላቸው ይገባል።
አዲስ ዘመን ጥቅምት 10/2012
ግርማ መንግሥቴ