ከአስር ዓመት በፊት የተካሄደ የሕዝብና ቤት ቆጠራን ይዞ በ2012 ዓ.ም ነፃና ገለልተኛ ምርጫ አካሂዳለሁ ማለትና የምርጫ ክልሎችን ወስኖ ወደ ምርጫ መግባት ተገቢ አለመሆኑን ምሁራን ይናገራሉ፡፡ አንዳንዶች ደግሞ በሳይንሳዊ የሕዝብ ቁጥር ትንበያ ምርጫውን ማካሄድ እንደሚቻል ይገልጻሉ፡፡
በሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የዲፕሎማሲና ዓለምአቀፍ ግንኙነት መምህር እንዳለ ንጉሴ እንደሚናገሩት፤ ምርጫ አንድ መንግሥት ሕጋዊ ነቱን የሚያረጋግጥበት መንገድ ነው፡፡ ይሁንና አሁን ባለው ሁኔታ ነፃና ገለልተኛ ምርጫ ለማካሄድ የሕዝብና ቤት ቆጠራ አልተከናወነም፡፡ በዚህ ሁኔታ ወደምርጫ መግባት ተገቢነት የለውም፡፡
ትክክለኛው የሕዝብ ቁጥር መረጃ ሳይኖር ምርጫ ቢከናወን ለእያንዳንዱ ክልል ምን ያህል በጀት እንደሚያስፈልገው መረዳት ያዳግታል፡፡ አዲስ የተወለዱ እና በቦታው የሌለውን ለይቶ አስፈላጊ የሆኑ ነገሮች ለሕዝቡ ሳይደርሱ ይቀራሉ፡፡ ከዚህ አንጻር ታይቶ ምርጫው መከናወን እንደሌለበት ይናገራሉ፡፡
የአገር ፍላጎትን ያስቀደመ ምርጫ ማካሄድ ካስፈለገ ሕዝቡ ተረጋግቶ መቆጠርና የሚፈልገውን ማግኘት ይኖርበታል የሚሉት መምህር እንዳለ፤ የፖለቲከኞች ፍላጎት መጠበቅ ላይ መሠረት ያደረገ ሥራ ይበልጥ ችግሩን ያሰፋዋል፡፡ ለዚህም ባለፉት የሕዝብና ቤት ቆጠራዎች የሕዝብን ቁጥር በመቀነስና በመጨመር ረገድ የተፈፀሙ ችግሮች ማሳያ ናቸው፡፡ በመሆኑም ያለፈውን ሳያርሙ ወደ ሥራ መገባቱ ተገቢነት እንደሌለው ይናገራሉ፡፡
የምርጫ ክልሎችን መወሰን የሚቻለው በሕዝብ ቁጥር መረጃ እንደሆነ የሚያነሱት መምህር እንዳለ፤ ምርጫ የመረጃ ትክክለኛነትን ይጠይቃል፡፡ ለዚህም የሕዝብ ቆጠራው መልስ የሚሰጥ ሲሆን፤ ይህ በሌለበት ግን ምርጫውን ማከናወን ከፖለቲካ አንጻር ብቻ ሳይሆን ከኢኮኖሚና ፖሊሲ ዝግጅት አንጻር ከፍተኛ ችግር ይፈጥራል፡፡ በሀገር አቀፍ ደረጃ ወይም በሀገር ውስጥ በተወሰነ የአስተዳደር ክልል ስለአለው
የሕዝብ ብዛትና የሥነ ሕዝብ ባህሪያት፣ የማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ እንዲሁም ቤቶች ብዛትና ሁኔታ የሚገልፁ መረጃዎችን የመሰብሰብ፣ የማጠናቀር፣ ትክክለኛነቱንም በመገምገም የትንተና ሪፖርት ለማዘጋጀት አዳጋች ይሆናል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የትምህርት ጥናትና ምርምር መምህር ዶክተር ፈርዴሳ ጀበሳ በበኩላቸው፤ የሕዝብ ብዛት ሳይታወቅ ምርጫ ማከናወን የምርጫ ማጭበርበርን ይፈጥራል፣ ክልሎች በፖለቲካ ውክልና ማግኘት የነበረባቸውን ውክልና እንዳያገኙም የሚያደርግ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ሕዝቡ ግብር የሚገብርባት ሀገር መብቶቹንና ጥቅሞችን ለማስከበር የሚሰራ ተወካይ እንዳይኖረው ያደርጋል ይላሉ፡፡
በተለይም በሕዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት የክልሉ ሕዝብ ውክልናው ወንበሮች እንዲያንስ የሚያደርግና በፖለቲካ ሥርዓቱ ላይ ጫና እንደሚፈጥር ይገልጻሉ፡፡ በአንድ አካባቢ የሚኖሩ ነዋሪዎች ወይንም አንድ ብሔር በሕዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤትም ሆነ በፌዴሬሽን ምክር ቤት ለፖለቲካ ውክልና እንዳያገኝ ማድረግ እንደሆነም ያስረዳሉ፡፡ የሕዝብ ቁጥርን መረጃ ሳይዙ ወደ ምርጫ መግባት የፖለቲካ ሥርዓቱን ያዛባል ሲሉ ይሞግታሉ፡፡
የደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ መምህር አቶ ሀሳቡ ተስፋ በሁለቱ ምሁራን ሀሳብ አይስማሙም፡፡ የሕዝብ ቆጠራው ሳይካሄድ ምርጫን ማከናወን የሚቻልበት ሳይንሳዊ የሕዝብ ቁጥር ግመታ ወይም ትንበያ መኖሩን ይናገራሉ፡፡ እንደእርሳቸው ማብራሪያ፤ በሕገመንግሥቱ ሕዝብ ሳይቆጠር ምርጫ መካሄድ የለበትም የሚል ነገር የለም፡፡
ሁለቱም ሕገመንግሥታዊ ድንጋጌዎች በመሆናቸው አንዱ ከአንዱ መነጣጠል የለበትም የሚለው ሕጋዊ መሠረት የለውም፡፡ ምክንያቱም የሕዝብ ቆጠራው ሳይካሄድ ለሁለት ጊዜያት በሳይንሳዊ ግመታ ምርጫ ተካሂዷል፡፡ አሁንም ቢሆን ያንን መሠረት አድርጎ ምርጫውን ማከናወን ችግር አይፈጥርም ባይ ናቸው፡፡
የሕዝብ ቁጥርን በትክክል ማወቅ ለወንበር ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ የአገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ ለማስተካከል ጭምር ያገለግላል የሚሉት መምህር ሀሳቡ፤ መንግሥት ይህንን ሲያደርግ አይጠቅምም ከማለት አኳያ ሳይሆን ከአገር ደህንነት አንጻር ቅድሚያ ሊያገኝ የሚገባው የትኛው እንደሆነ በማመኑ ነው፡፡ ስለሆነም የሕዝብ ቆጠራው ባይካሄድም ምርጫው መካሄዱ ቢያንስ ሁለተኛ ሕግ እንዳይጣስ ያደርጋል፡፡
መምህር እንዳለና ዶክተር ፈርዴሳ እንደሚሉት፤ ለወደፊቱ የሚያስፈልግን ገቢና ወጪ የሚተነብይ የንዋይ እቅድ ለማውጣትና በጀት ለመመደብ፣ ለክልሎች ለማከፋፈልም የሕዝብ ቁጥር ወሳኝ ነው፡፡
ይሁንና መሬት ላይ ያለውን ትክክለኛ የሕዝብ ቁጥር መረጃ ሳይገኝ ወደ ምርጫ መግባት ከሕዝብ ምጣኔና ስርጭት ጋር ያልተጣጣመ በጀት ለመበጀት ይዳርጋልና መፍትሄው ሕዝብ ቆጠራው ሳይካሄድ ምርጫውን አለማካሄድ ነው ይላሉ፡፡
ትክክለኛ የሕዝብን ቁጥር ማወቅ የሕዝብና የመሠረተ ልማት ስርጭትን ለማስተካከል፣ ለአዲስ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች፣ እቅድ ለማውጣት፣ የሥራ አጡን ቁጥር በትክክል ለማወቅ ያግዛል፡፡ ይሁንና አዲስ የሚመረጥ ፓርቲ ይህንን ባልያዘበት ሁኔታ አገር ሊመራ አይችልም፡፡ ስለዚህ ቅድሚያ ለሕዝብ ቆጠራው መሰጠት እንዳለበት ይናገራሉ፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ550 ወንበር አንድ መቶ ሺ ሕዝብን በመወከል የየውክልና ፖለቲካ ሥርዓቱ ይካሄዳል፡፡ የፌዴሬሽን ምክር ቤትም
የሀገሪቱን ብሔር ብሔረሰቦች እና በአንድ ሚሊዮን ዜጎች አንድ ተወካይ በመወከል ሥራውን ይከውናል፡፡ ይህ ደግሞ የተሳሳተ ወይንም የተዛባ የሕዝብ መረጃን ከያዘ ብዙ ችግሮችን መፍጠሩ አይቀርምና አሠራሮች ከወዲሁ ታርመው ቅድሚያ ለሕዝብ ቆጠራው መሰጠት እንዳለበትም ያሳስባሉ፡፡
መምህር ሀሳቡ በበኩላቸው፤ መፍትሄው ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ቁጭ ብለው መወሰን ሲችሉ የሚመጣ ነው ይላሉ፡፡ በተለይም ሕግን በሕግ እንጂ በስምምነት ብቻ ማድረግ ለማንም እንደማይበጅ ያነሳሉ፡፡ ቆጠራው ሲራዘም ሕግ ተጠሷል፡፡ አሁንም ምርጫውን ለማራዘምና ለማድረግም ሕግ እንዳይጣስ ሕግን መሠረት አድርጎ መተግበር ሰፊ አማራጭ ይሰጣልም ባይ ናቸው፡፡ ሕገ መንግሥቱን ማሻሻል ካስፈለግም ቁጭ ብሎ በመምከር ለአገር እንዲበጅ አድርጎ መስራት መፍትሄን ያመጣልም ብለዋል፡፡
አሁን አገሪቱ ባለችበት ሁኔታ ሕግ ማሻሻል ቅቡልነቱን አጠያያቂ ያደርገዋል፡፡ እዚህ ላይ ትኩረት ሰጥቶ መወያየትና ለምርጫው መከናወን ይመች ዘንድ እንዲሁም ውክልና እንዳይነፈግ ሳይንሳዊ የሕዝብ ቁጥር ትንበያን ወይም ግመታ መጠቀም ሁነኛ መፍትሄ መሆኑን አንስተዋል፡፡
በሕገ መንግሥቱ አንቀፅ 103(5) መሠረት የምርጫ ቦርድ የምርጫ ክልሎችን የሚወስነው ከሕዝብና ቤት ቆጠራ ኮሚሽን በሚያገኘው መረጃ መሠረት ነው፡፡ ምርጫ በየአምስት ዓመቱ፣ ሕዝብና ቤት ቆጠራን ደግሞ በየአስር ዓመቱ ሊካሄዱ እንደሚገባ በግልፅ አስቀምጧል፡፡ ይሁንና 3ኛው ሕዝብና ቤት ቆጠራ ከሦስት ዓመት በፊት በ2009 ዓ.ም መካሄድ ቢኖርበትም አልተካሄደም፡፡
በ2012 ዓ.ም እንደሚካሄድ የሚጠበቀው ምርጫ የሕዝብ ቁጥር ትክክለኛ መረጃ ሳይኖር ከተከናወነ በሕዝብና መንግሥት መካከል መተማመን አይኖርም፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች አሸናፊነትም ዴሞክራሲያዊ ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡ ሕዝቦች ትክክለኛ ወካያቸውን እንዳያገኙ ያደርጋል፡፡ በዚህም በአገሪቱ ላይ ሰላምና መረጋጋትን ለመፍጠር አስቸጋሪ ይሆናል፡፡
አዲስ ዘመን ነሃሴ 26/2011
ጽጌረዳ ጫንያለው