የአልኮል ማስታወቂያዎች በምን መልክ መቅረብ አለባቸው? ለሚለው ጉዳይ ትኩረት እንዳልተሰጠ ይነገራል፡፡ የተቆጣጣሪው አካል ለዘብተኛ አቋምና ተከታትሎ ዕርምጃ አለመውሰድም ማህበረሰቡ ላይ በአልኮል መጠጥ ማስታወቂያዎች ምክንያት የሚደርሰው ጉዳት አሳሳቢ እንዳደረገው ባለሙያዎች ይገልጻሉ።
ወይዘሮ ፍቅርተ ማሞ በንፋስ ስልክ ላፎቶ ክፍለ ከተማ በሰዲል ለኢትዮጵያ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የምክር አገልግሎት ባለሙያ ናቸው። በመገናኛ ብዙሃን የሚተላለፉ የአልኮል መጠጥ ማስታወቂያዎች አግባብነት በተመለከተ አቀራረቡ የሚያሳስባቸው ጉዳይ መሆኑን በአፅንኦት ይገልጻሉ። ዛሬ ላይ በተለያዩ መገናኛ ብዙሃን የሚቀርቡ የአልኮል መጠጥ ማስታወቂያዎች እጅግ በማጋነንና ማራኪ በማድረግ የሚቀርቡ በመሆናቸው ህብረተሰቡ የሚያስከትለውን ጉዳት ዘንግቶ ተጠቃሚ እንዲሆን እያበረታቱ መሆኑን ይናገራሉ። ከዚሁ ጋር ተያይዞ የአልኮል መጠጥ ማስታወቂያዎቹ በየጊዜው በሚያቀርቡት አጓጊ ሽልማት የተጠቃሚውን ቁጥር ከፍ እንዳደረገው ብዙ ማሳያዎችን በመጥቀስ ያስረዳሉ።
የአልኮል መጠጥ ማስታወቂያዎች ከማህበረሰቡ ታሪክና ባህል ጋር ተዋህደው የሚነገሩ በመሆናቸው ህብረተሰቡ በቀላሉ በማስታወቂያዎቹ ተማርኮ ወደ አልኮል መጠጥ ይሳባል። ይባስ ብሎ ሕፃናትና ታዳጊዎች በማስታወቂያዎቹ በመማረክ ከማስታወቂያዎቹ ጋር የሚቀርቡ ዜማዎችን ሲያዜሙ መስማት የተለመደ መሆኑን ያስረዳሉ። የማስታወቂያዎች አቀራረብ ልጓም ካልተበጀለት ትውልዱ ላይ ሊፈጥር የሚችለው አሉታዊ ተፅዕኖ ከፍተኛ መሆኑን እንደ ማሳያ ያነሳሉ። የማስታወቂያ ሥራዎች ከአስተዋዋቂው ስነምግባርና የምናስተዋውቃቸው ምርቶች ለሀገር ከሚሰጡት ጥቅም አኳያ መታየት አለባቸው የሚለውን ሃሳብ ልናጤነው ይገባል የሚል እምነት አላቸው።
ወይዘሮ ትዝታ ዳዲ ደግሞ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ጤና ፅሕፈት ቤት ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ቁጥጥር ባለሙያ ናቸው። ወይዘሮ ትዝታ የአልኮል መጠጦች ህብረተሰቡ ላይ የሚያደርሱት የጤና ችግሮች ከፍተኛ መሆኑን ይገልጻሉ፡፡ ከሚያስከትሉት የጤና ችግሮች መካከል የልብ በሽታ፣ የደም ግፊት፣ የኩላሊት ማጣራት ተግባር ማስተጓጎል፣ የአዕምሮ ጤና ችግር ዋንኞቹ ሲሆኑ በተለይ በሰውነታችን ጤናማነት ላይ ጉልህ ሚና ያለው ጉበት አልኮል ዋንኛ ጠንቁ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ ሌላኛው በቅርቡ ይፋ የሆነው የጥናት ግኝት እንደሚያስረዳው አልኮል መጠጣት ካንሰርን የሚያስከትሉ ሴሎችን ዕድገት ያፋጥናል። የስኳር በሽታን እንደሚያስከትልም ያብራራሉ።
እንደ ወይዘሮ ትዝታ ማብራሪያ አልኮል መጠጥ ማስታወቂያዎች በመገናኛ ብዙሃን የሚቀርቡበት መንገድ የሚያስከትሉትን ጉዳት የዘነጋና ይበልጥ የከፋ ጉዳት ሊያስከትል በሚችል መልኩ ነው። ለዚህም የማስታወቂያ ህጎችን መተግበርና ማህበራዊ ኃላፊነት በተላበሰ መልኩ መሠራት እንዳለባቸው ያሳስባሉ።
የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ ዶክተር አሚር አማን በትዊተር ገጻቸው የስፖርትና መዝናኛ ፕሮግራሞች ላይ የአልኮል ይዘታቸው ከ10 በመቶ በላይ የሆኑ የአልኮል መጠጦች ማስተዋወቅ ክልክል መሆኑና የአልኮል ይዘታቸው ከ10 በመቶ በታች የሆኑትም የአልኮል መጠጦች የማስታወቂያ የሰዓት ገደብ እንደተቀመጠ መናገራቸው ይታወሳል፡፡ ይህን ተከትሎም ባለፈው ማክስኞ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በመገናኛ በዙሃን የሚታየውን የአልኮል መጠጥ ማስታውቂያ አግባብነት ላይ መክሯል።
በኢትዮጵያ የምግብ መድሀኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን ቀርቦ በምክር ቤቱ አባላት ውይይት የተደረገበት የአልኮል መጠጥ ማስታውቂያዎች መመሪያ ረቂቅ አዋጅ በሙሉ ድምፅ ለሴቶች ወጣቶችና ሕፃናት ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ተመርቷል።
ረቂቅ አዋጁ የአልኮል መጠጥ ማስታወቂያዎች ከምሽቱ ሦስት ሰዓት እስከ ንጋት አስራ ሁለት ሰዓት ብቻ እንዲተዋወቁ የሚፈቅድ ሲሆን፤ የማስታወቂያዎቹ ይዘት ላይ እቅባዎችና ሌሎች ዝርዝር ጉዳዮችን አካቷል። የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴርም በአልኮል መጠጥ ላይ የሚሠሩት ማስታወቂያዎች ባህልን፣ማንነትንና ታሪክን በሚያዛባ መልኩ እንዳይቀርቡ ለማድርግ የሚያስችል ጥናት በማድረግ ላይ መሆኑን አሳውቋል።
የኢትዮጵያ የምግብ መድሃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን በታኅሣሥ ወር 2008 የአልኮል መጠጥ ማስታወቂያን ስርዓት ለማስያዝ የሚያስችል መመሪያ ማውጣቱ ይታወሳል። በመመሪያ ቁጥር 33/2008 የአልኮል ይዘት ያላቸው መጠጦች የማስታወቂያ አግባብነት በተመለከተ በሚከተለው መልኩ አስቀምጦ እንዲተገበር ወስኖ ነበር፡፡ «ማንኛውም የአልኮል መጠጥ ማስታወቂያ መጠጡን መጠቀም ለጤና ተስማሚ እንደሆነ፣ ግላዊና ማህበራዊ ስኬትን እንደሚያስገኝ፣ ለተሻለ ሥነ ልቦናዊ ወይም አካላዊ ብቃት እንደሚጠቅም፣ የፈዋሽነት ባህሪ እንዳለው፣ ለግብረ ስጋ ግንኙነት የተለየ ጥቅም እንዳለው፣ የንጥረ ነገሮቹን በጎነት፣ ከመጠን በላይ መወሰድን የሚገፋፋ ወይም መሰል የተጋነነ መልዕክት የሚያስተላልፍ መሆን የለበትም» ይላል።
በተጨማሪም «በማንኛውም የአልኮል መጠጥ ማስታወቂያ የአልኮል መጠጡ በኃላፊነት መጠጣት እንዳለበትና ለአካለ መጠን ላልደረሰ ልጅ የማይሸጥ ወይም የተከለከለ እንደሆነ መግለጽ አለበት። የአልኮል መጠኑ ከ 10 በመቶ በላይ የሆነ ማንኛውም መጠጥን የሚመለከት ማስታወቂያ ከውጭ ከሚለጠፍ ማስታወቂያ እና እለታዊና ሳምንታዊ ካልሆነ ጋዜጣ እና መጽሔት በስተቀር በሌሎች የማስታወቂያ ማሰራጫ ወይም ማስተላለፊያ መንገዶች አማካኝነት ማሰራጨት የተከለከለ ነው» በማለት በዝርዝር ያስቀምጣል።
«ለአካለ መጠን ያልደረሰ ልጅ ላይ ትኩረት የሚያደርግ ወይም አካለ መጠን ያልደረሰ ልጅን የማስታወቂያው ተዋናይ አድርጎ የሚጠቀም ወይም ሌላ መሰል መልዕክት የሚያስተላልፍ መሆን የለበትም። የመጠጥ ማስታወቂያ በመገናኛ ብዙሃን ላይ በሚሰራጭ የልጆች ፕሮግራም ላይ ማስተዋወቅ የተከለከለ ነው። ማንኛውም የአልኮል መጠጥ ማስታወቂያ የልጆች ፕሮግራም ከመጀመሩ ሠላሳ ደቂቃ በፊት እና ካለቀ በሠላሳ ደቂቃ ጊዜ ውስጥ መተላለፍ የለበትም» ይላል። ይሁን እንጅ ይህ መመሪያ ከወጣ ሁለት ዓመታትን ቢያስቀቆጥርም በአተገባበሩ ላይ ችግር ይስተዋላል።
የማስታወቂያ ስርዓት አዋጅን በተመለከተ አዋጅ ቁጥር 759/2004 ነሐሴ 21 ቀን 2004 ዓ.ም በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ሥራ ላይ ውሏል፡፡ ይህ አዋጅ ሦስት ዋና ዋና ዓላማዎች አሉት፡፡ የመጀመርያው ዓላማ ገበያ መር የሆነው የኢኮኖሚ ስርዓት ጤናማ በሆነ ውድድር እንዲመራ ለማድረግ ሲሆን፤ ሌላኛው ደግሞ ማስታወቂያ በህግ ስርዓት ባለመመራቱ ምክንያት በህብረተሰቡ ላይ ሊደርስ የሚችለውን የመብትና የጥቅም ጉዳት ለመከላከል፤ እንዲሁም የሀገርን ገጽታ ሊያበላሹ የሚችሉ አደገኛ ማስታወቂያዎችን ለመከላከል ታሳቢ ያደረገ ነው፡፡
ሌላኛው ነጥብ የማስታወቂያ ማስተላለፍ ሥራ የሚያስከትለውን በጎ ያልሆነ ተጽዕኖ ለመከላከል ሲባል በማስታወቂያ ወኪልነት፤ አስነጋሪነት እና አሰራጭነት የሚሳተፉ ሰዎችን መብትና ግዴታ ግልጽ በሆነ አግባብ በመደንገግ ህግና ስርዓትን የማስከበር ሂደቱን ውጤታማ ለማድረግ ነው፡፡ አሁንም በህዝብ ተወካዮች ምክርቤት ፀድቆ ተግባራዊ ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው መመሪያም የአፈፃፀም ችግር እንዳያጋጥመው ከወዲሁ ሊታሰብበት እንደሚገባ አስተያየት ሰጭዎቹ አፅንኦት ሰጥተውበታል።
አዲስ ዘመን ታህሳስ 7/2011
ተገኝ ብሩ