
‹‹ቅዳሜን ከሰዓት›› የተሰኘው የኢ ቢ ኤስ ቴሌቪዥን ፕሮግራም ላይ ቅርብ ጊዜ የተጀመረ (እኔ እንዳየሁት) አንድ አዝናኝ ፕሮግራም አለ:: ይሄውም ፈቃደኛ የሆኑ መንገድ ላይ የተገኙ ሰዎችን የግል ሕይወታቸውን የተመለከቱ የተለያዩ ጥያቄዎችን መጠየቅ ነው:: ከስቱዲዮ ያሉ ተወዳዳሪዎች የተጠያቂዎችን አካላዊ ሁኔታ በማየት ምን እንደሚሉ መገመት ነው::
መንገድ ላይ የተቀረጸውን ምስል እና ከንግግራቸው ቀንጨብ አድርገው ስቱዲዮ ለሚወዳደሩት ያሰሟቸዋል:: አንዲት ተጠያቂ መንገደኛ የመንግሥት ሰራተኛ መሆኗን ተናገረች:: ከስቱዲዮ ያሉት ተጠያቂዎች የመንግሥት ሠራተኛዋ ለመጨረሻ ጊዜ የሞላችው የሞባይል ካርድ ባለ ስንት እንደሚሆን ገምቱ ተባሉ:: ‹‹ባለ 10 ብር›› አሉ:: ለምን ሲባሉ የመንግሥት ሰራተኛ ስለሆነች የሚል ነበር ግምታቸው:: መልሱ ሲታይ ግን የመንግሥት ሰራተኛዋ የሞላችው ባለ 50 ብር ነበር::
ባለፈው ቅዳሜ የሰማኋት ይቺን አንዲት ነጠላ ማሳያ ያመጣሁት ነገሩን ስላስታወሰችኝና ፈገግ ስላሰኘችኝ እንጂ የሦስት ሰዎችን ግምት እንደ መደምደሚያ ወስጄ አይደለም:: ቢሆንም ግን በዚያ ፕሮግራም የሦስት ሰዎች ግምት ይሁን እንጂ የመንግሥት ሰራተኛን እንደ የድሃ ድሃ ማየት አሁን አሁን የብዙ ሰዎች እምነት እየሆነ ነው::
ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የመንግሥት ሠራተኛ ድሮ ይሰጠው የነበረውን ክብደት አይደለም የሚሰጠው:: እንዲያውም መቀለጃ እና የኑሮ አስከፊነትን መግለጫ ሆኗል:: ገበሬዎች ሲቀላለዱ ‹‹ምነው እንደ መንግሥት ሠራተኛ ጃምቦ ትጠጣለህ!›› እየተባባሉ ይፎጋገራሉ ይባላል:: ጃምቦ የድሃ ሆኖ ማለት ነው፤ እነርሱ ወደ ወይን እና ውስኪ አድገው ማለት ነው:: በአገራችን ፊልሞችና የቀልድ ቪዲዮዎችም የምናያቸው የመንግሥት ሠራተኛን ድህነት የሚያሳዩ ናቸው::
የመንግሥት ሠራተኛ ለምን የድሮ ክብሩንና ክብደቱን አጣ ? የመንግሥት ሠራተኛ የድሮ ክብሩን እና ክብደቱን ያጣው ከየትኛውም ማህበረሰብ የከፋ ድህነት አጋጥሞት አይደለም:: የአመለካከት ለውጥ ስለመጣ ነው:: የተማረ ኃይል ስለበዛ እና በግል ንግድ በሚተዳደረውና በመንግሥት ሠራተኛው መካከል ያለው የትምህርት ደረጃ ያን ያህል የጎላ ልዩነት የሌለው መሆኑ ነው::
ቀደም ሲል በነበሩት ዘመናት የመንግሥት ሠራተኝነት ከልክ በላይ ይከበር የነበረው በትምህርት ደረጃው ነበር:: የተማረ እና የሰለጠነ ነው ተብሎ ስለሚታመን ነበር:: ከሌላው የህብረተሰብ ክፍል የተለየ የአለባበስና አመጋገብ ሥርዓት ስለነበረው ነው::
እንዲያውም እስከ ቅርብ ጊዜያት ድረስ የገጠሩ ማህበረሰብ ልጁን የሚያስተምር አፈርና ጭቃ እንዳይነካው፣ ዝናብም ሆነ ፀሐይ እንዳይመታው፣ ሱፍና ከራቫት አድርጎ ቢሮ ውስጥ ቁጭ እንዲል ነበር:: ክብርና ሞገስ የሚመስለው እሱ ነው:: ይህ ልማድ ሆኖ ነበር:: ቀደም ባለው ዘመናት የተማረ የሰው ኃይል በቁጥር ትንሽ ስለነበር ከፍተኛ ኃላፊነት ላይ ይደርሳሉ:: አሁን ግን ዘመኑም አስተዳደራዊ ሥርዓቱም ተቀይሯል:: የባህል አብዮት ተፈጥሯል:: በአንድ ነጋዴ እና በአንድ የመንግሥት የሥራ ኃላፊ መካከል ያለው የትምህርት ደረጃ ጠባብ ነው፤ ምናልባትም ነጋዴው የሚበልጥበት ዕድልም ሊኖር ይችላል::
በዘመን ሂደት ቴክኖሎጂ መስፋፋቱ፣ አስተዳደራዊ ሥርዓት መቀየሩ እና ትምህርት መስፋፋቱ የባህልና ልማድ አብዮት ፈጠረ:: ይህ የባህል አብዮት ደግሞ የአመለካከት ለውጥ አመጣ:: ዛሬ ላይ ባለው አመለካከት አንድ በዲግሪ የተመረቀ ሰው የመንግሥት ሠራተኛ ሆኖ ከመቀጠር ይልቅ ነጋዴ መሆንን ይመርጣል:: እንደ ድሮው ‹‹ሸቀጣም!›› ይሉኛል የሚል ፍርሃት የለም:: ‹‹ሸቀጣም!›› ብሎ የሚሳደብ ቢኖር የሚሳቅበት ተሰዳቢው ሳይሆን ተሳዳቢው ነው፤ ምክንያቱም የኋላቀር አመለካከት ተሸካሚ ነው:: ዛሬ ላይ አንድ የመንግሥት ሠራተኛ አደገ የሚባለው ከመንግሥት ሥራ ወጥቶ የግሉ ሥራ ሲጀምር ነው::
የመንግሥት ሠራተኝነትን እንደ ብቸኛ የኩራትና የትልቅነት መገለጫ የማድረግ አስተሳሰብ መቀየሩ መሰልጠን ነው፤ የአስተሳሰብ ማደግ ልንለው እንችላለን:: ዳሩ ግን በተቃራኒው ደግሞ በዚህ ዘመን ‹‹ኋላቀር›› ሊባል የሚችል የተዛባ አመለካከትም አለ:: ይሄውም የመንግሥት ሠራተኝነትን የችግርና የመጨረሻ አማራጭ አድርጎ ማየት ነው:: የድሃ ልጆች ብቻ አማራጭ ሲያጡ የሚገቡበት ተደርጎ ነው የሚታይ:: ከአንድ የአመለካከት አብዮት ወደ ሌላ የአመለካከት አብዮት ስንሄድ በፍፁም ሽምጠጣና ጽንፍ መሆን የለበትም::
የመንግሥት ሠራተኝነት ማለት የሕዝብና አገር አገልጋይነት ማለት ነው:: በመንግሥት ሠራተኛ ላይ የሚያሾፈውና የሚቀልደው ሁሉ አገልግሎት ለማግኘት የመንግሥት ሠራተኛው ጋ ነው ደፋ ቀና ሲል የሚውል:: የመንግሥት ተቋማት አገልግሎት የሚሰጡት ለሕዝብ ነው:: አንድ የመንግሥት ሆስፒታል ውስጥ ለመታከም የሚሄድ ሰው ሐኪሞችን እንደ ፈጣሪ ነው የሚያያቸው:: የወንጀል ድርጊት የተፈጸመበት አንድ ትልቅ ነጋዴ ወደ ፖሊስ ነው የሚሄደው:: ‹‹የመንግሥት ያለህ!›› ብሎ ነው የሚጮህ:: እነዚህ እንዲደርሱለት ወይም እንዲያድኑት የሚሄድባቸው ተቋማት ሁሉ በመንግሥት መዋቅር ሥር ያሉ ናቸው::
ማንኛውም ግለሰብ(ሀብታምም ይሁን ድሃ) የቀበሌ አገልግሎቶች ያስፈልጉታል:: እነዚህ የቀበሌ አገልግሎቶች የሚሰጡት በመንግሥት ሠራተኛ ነው:: መንግሥት እነዚያን አገልግሎቶች ለመሥጠት የግድ በዘርፉ የሰለጠኑ ሠራተኞች ያስፈልጉታል:: በአጠቃላይ ሕዝቡ በሙሉ ሀብታም ቢሆን እንኳን ለአንዲት አገር ሕዝብ መንግሥትና የመንግሥት ሠራተኛ የግድ ነው::
ሌላው መጠቀስ ያለበት ነገር ደግሞ የራሱ የመንግሥት ሠራተኛው ስንፍና እና አላዋቂነት ነው:: ለመኖር ብቻ የሚሰራ የመንግሥት ሠራተኛ አለ፤ ከወታደርና ፖሊስ በስተቀር በአገር ፍቅር ስሜት የሚሰራው በጣት የሚቆጠር ቢሆን ነው:: እንዲያው ማን ይሙት አንድ የመንግሥት ሠራተኛ የ20 ሚሊዮን ብር ሎተሪ ቢወጣለት ሥራውን አይለቅም? እኔ ለአገሬና ሕዝቤ በሰለጠንኩበት ሙያ ማገልገል አለብኝ፣ በእኔ ቦታ የሚፈጠረው ክፍተት ሕዝብ ይበድላል ብሎ የሚቀመጥ ይኖራል? አይመስለኝም!
በእርግጥ አገርን ማገልገል ማለት የግድ በመንግሥት ሠራተኝነት ብቻ አይደለም:: የግል ሥራ ቢጀምር ለሌሎች ዜጎችም የሥራ ዕድል ይፈጥራል:: በግል ሥራ መሰማራት ራስን ብቻ ሳይሆን አገርን ማገልገል መሆኑ ማንንም አያከራክርም፤ ዳሩ ግን የመንግሥት ሠራተኛ መሆንን እንደ ሥቃይ ወይም እንደ አማራጭ መፈለጊያ ማድረግ ስንፍና ብቻ ሳይሆን የአገርና ሕዝብን ክብር መቀነስ ነው:: የመንግሥት ሠራተኛነቱን አማራጭ መፈለጊያ አድርጎ የሚሰራ ዜጋ መሳለቂያ ቢሆን አይገርምም፤ ምክንያቱም የሚሰጠው አገልግሎትም ለተገልጋዮች ምቾት የማይሰጥ ነው የሚሆን:: ሥራውም አሰልቺ ይሆንበታል:: የሥራ ቀናት የሚዘጉበትን ‹‹ካላንደር›› ነው የሚቆጥር::
የመንግሥት ሠራተኛን መቀለጃ ካደረጉት ነገሮች አንዱ ደግሞ ራሱ መንግሥት ነው:: የኑሮው ጉዳይ ከአገሪቱ የኢኮኖሚ አቅም ጋር የሚሄድ ነው ብለን እንለፈው:: ዳሩ ግን ተገቢውን ሰው በተገቢው ቦታ የማስቀመጥ ችግር አለ:: ይህ ባለመሆኑ ነው አገሪቱም ማደግ ያልቻለችውና ለኑሮ ውድነት የተዳረግነው:: በትክክል ለአገር ፍቅር ብለው የሚሰሩ ሰዎች በበላይ አመራር ምናልባትም እንደ ጅል ይታዩ ይሆናል እንጂ የተለየ ማበረታቻ ሲሰጣቸው እምብዛም አይታይም:: በእርግጥ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሽልማትና ማበረታቻዎች ተጀምረዋል::
መንግሥት ሙስናን በከፍተኛ ሁኔታ መቆጣጠር ባለመቻሉና ኃላፊነታቸውን በማይወጡ ሠራተኞች ላይ ተገቢውን ቅጣት ባለመስጠቱ ነው ከድህነት መውጣት ያልቻልነው:: ሙስና ሲባል የግድ የገንዘብ ብቻ አይደለም፤ የጊዜ ብክነትና የሰው ኃይልን በአግባቡ አለመጠቀም ሙስና ነው:: ተገልጋይ የሚያጉላሉ ሠራተኞች ላይ ቁጥጥር አለማድረግ ራሱ መንግሥትን ማሰደብ ነው::
በአጠቃላይ፤ የመንግሥት ሠራተኛ ድሮ ከልክ ያለፈ ክብርና ክብደት ይሰጠው የነበረው ከዘመኑ አንፃር በነበረ አመለካከት ነው:: ዘንድሮ መቀለጃ የሆነው ደግሞ በመንግሥስትና በሠራተኛው ከልብ አለመሥራት እና በግል ዘርፍ ውስጥ ባሉት ሰዎች የተዛባ አመለካከት ነው:: በነገራችን ላይ በግል ዘርፍ ውስጥ ላሉት ይህን ዕድል የፈጠረላቸው መንግሥት ነው::
ስለዚህ ዘመኑን የዋጀ የአስተሳሰብ አብዮት ስናመጣ ‹‹ኋላቀር›› የሆነ የተዛባ አመለካከትንም እናስወግድ!
ዋለልኝ አየለ
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 11/2015