በኢትዮጵያ የሚገኙ ክልሎች ‹‹ልዩ›› በሚል ስያሜ የፖሊስ ኃይል ማደራጀት የተጀመረው በሚሊኒየሙ መግቢያ በሶማሌ ክልል ከኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጪ ግንባር (ኦብነግ) ጋር ከነበረው የሽምቅ ውጊያ ጋር በተያያዘ መሆኑን የታሪክ ድርሳናት ይጠቁማሉ። ባለፉት አመታትም ፉክክር በሚመስል መልኩ ክልሎች ልዩ ኃይል እንደ መደበኛ ሠራዊት ሲያሰለጥኑ እና ሲያስታጥቁ ከርመዋል።
ይህ የኃይል አደረጃጀትም ሁለት ዓይነት አስተያየትን ሲያስተናግድ ቆይቷል። አንደኛው ‹‹ክልሎች የራሳቸውን ልዩ ኃይል አደራጅተውና አስታጥቀው ማሰማራታቸው ለአገር ደኅንነት አደጋ ነው፤ የእነዚህ ኃይሎች አደረጃጀትም ሕጋዊ መሠረት የሌለው ነው›› የሚል ነው። ሌላኛው ደግሞ የልዩ ኃይል ፖሊሶችን ጥቅም ከግምት በማስገባት የአንድን ክልል ሕዝብ ደኅንነት ለማስጠበቅ ከፖሊስ ባሻገር ይህ ሠራዊት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሊያበርክት እንደሚችል የሚሞግት ነው።
ከልዩ ኃይል አመሠራረት ጋር አብሮ ከሚነሱት ጉዳዮች መካከል አንዱ ሕጋዊ መሠረቱ ነው። የኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 52 የክልሎች ስልጣንና ተግባር ይደነግጋል። የሕገ-መንግሥቱ አንቀጽ 52/2/ሰ ክልሎች የክልላቸውን የፖሊስ ኃይል ያደራጃሉ፣ ይመራሉ፣ የክልሉን ሰላምና ጸጥታ ያስጠብቃሉ ይላል። ይሁን እንጂ ይህን የሕገ-መንግሥቱ አንቀጽ አንዳንዶች በፈለጉት መልኩ ይተረጉሙታል።
ይሁንና ክልሎች ሰላምና ጸጥታ የሚያስከብሩት መደበኛ ፖሊስን ተጠቅመው እንጂ ከመደበኛ ፖሊሱ በተጨማሪ ሌላ የልዩ ኃይል ፖሊስ እንዲያደራጁና እንዲያሰማሩ ፈቃድን አይሰጥም። ምንም እንኳን ከትጥቅ አያያዝና አደረጃጀት ጋር የተያያዘ ግልጽ ፖሊሲን ባያስመለክትም፣ ከተልዕኮ አንፃር የፖሊስ ሰራዊቱ መያዝ የሚገባው ትጥቅና አደረጃጀት ከአገር መከላከያ ሰራዊትም በላቀ መልኩ መሆን አለበት እንደማይል ለመረዳት የሕገ መንግሥት ወይንም የሕግ ተንታኝ መሆን አይጠይቅም።
ይሁንና ቀደም ሲል አገር ይመራ የነበረው መንግሥት ይህን የሕግ አንቀፅ ለትርጉም እንዲጋለጥና ከፍ ሲልም በርካቶች ሲገልፁት እንደሚሰማው ‹‹ለራሱ እንዲመቸው›› ክፍት አድርጎት አንደ መጽሐፍ ቅዱስ አትንኩብኝ ብሎ በመቆየቱ ክልሎችም በራሳቸው መንገድ ሲረዱት፣ ከሕግ አውድ ውጪም ሲተረጉሙት ቆይተዋል።
ይህ ተከትሎም ልዩ ኃይሎች የተቋቋሙበት ሕጋዊ መሠረት፣ ተጠያቂነታቸው፣ በሙያ ቀኖናቸው ፖሊስ ወይንስ ተዋጊ መሆን አለመሆናቸው፣ የልዩ ኃይሎችን ዕዝ ሰንሰለት፣ ብዛት፣ መሣሪያ ዓይነት፣ በሕግ የተደነገገ ሚና እንዲሁም ከፌዴራል ፖሊስም ሆነ ከመከላከያ ሰራዊት ጋር ስለሚኖራቸው የሥራ ግንኙነት ግልፅ ባለመሆኑ አጠቃላይ አደረጃጀቱ በየጊዜው የበርካቶች ትችት ተለይቶት አያውቅም።
አደረጃጀቱ የሚራመድበትም ሆነ የሚገራበት የሕግ እና ፖሊሲ መንገድ ባለመኖሩም ክልሎች በተለያዩ ጊዜያት በሚያካሂዷቸው ወታደራዊ ትዕይንቶች ላይ የልዩ ኃይል አባላቱ መካከለኛ እና ከባድ የነፍስ ወከፍና የቡድን የጦር መሣሪያዎችን ታጥቀው ታይተዋል።
የኃይል አደረጃጀቱ ብሔር ተኮር በመሆኑም አንደኛው ክልል ለሌላኛው አንደኛው ብሔር ለሌላኛው የሚቆም አልነበረም። ይህም አገር አቀፍ የሆነውን አብሮነት፤ የሕዝቦችን አንድነት በእጅጉ ሲሸረሽረው ታይቷል። በየክልሉ ያለው ልዩ ኃይል በስልጠና አወሳሰዱ፣ በትጥቁ፣ በሚወስዳቸው እርምጃዎችና በሚሰማራባቸው ተልዕኮዎች የወታደራዊ ኃይል ባህሪ ያለውና የዜጎችና ሰላምን ደህንነት ከማስጠበቅና ማስከበር ይልቅ ወደ ድንበር ጠባቂነቱ ሲያመዝንም ታዝበናል። አልፎ አልፎም ከፌዴራሉ መንግሥት የፀጥታ አካላት ጋር የጥይት እሩምታ እስከመለዋወጥ ከፍ ሲል ጦርነት እስገመግጠም መተላለፉ የቅርብ ጊዜ ትውስታችን ነው።
ገና ከጅምሩም ሆነ ከቅርብ አመታት ወዲህ የሚሆነው የሚያሰጋቸው በርካቶች የፌዴራሉ መንግሥት በየክልሉ ያሉትን የተደራጀና የታጠቀን ልዩ ኃይል በአግባቡ ማደራጀት እንዳለበት ሲሞግቱ፣ አደረጃጀቱ ተለውጦ ወደ መደበኛ ፖሊስ ወደ መከላከያ ሠራዊት ወይም ደግሞ ወደ ፌዴራል ፖሊስ ውስጥ እንዲጠቃለልና በዚያ ዕዝ ስር እንዲተዳደር በተደጋጋሚ ሲጠይቁ ቆይዋል።
ላለፉት አመታት ሰሚ ጆሮ የተነፈገው ይህ ጥያቄ በመጨረሻም በለውጡ መንግሥት ምላሽ ተሰጥቶታል። የአገሪቷን የግዛት አንድነት፤ የአገሪቷን ሉዓላዊነት፣ የአገሪቷን የሕዝቦች ደህንነት መነሻ በማድረግ መከላከያን ጨምሮ የተለያዩ የጸጥታ ኃይሎች ሪፎርም የመስራት ተግባር ቅድሚያ የተሰጠው ሲሆን ባለፉት ሦስትና አራት ዓመታትም ይህ ተግባር በከፍተኛ ትኩረት ሲከናወን ቆይቷል። በአንድ በኩል ውስጥ ላይ የተቃጣውን ጥቃት የመመከት በሌላ በኩል ደግሞ ይሄንን ሪፎርም የመስራት ሥራ ተሠርቷል።
ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጀኔራል አበባው ታደሰ ከሰሞኑ ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) ጋር በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ባደረጉት ቆይታ እንደገለፁትም፣ ሪፎርሙ የሚያጠነጥነው በኢትዮጵያዊነት የተገነባ ለሁሉም ሕዝብ እኩል የሆነ እና በቂ ችሎታ ያለው ዘመናዊ የጸጥታ ግብረ ኃይል እና መዋቅር መገንባት ነው። ይህ ኃይል ምንድን ነው የሚዘምነው? ለምንድን ነው ይህ ኃይል ሪፎርም እየተደረገ ያለው ? ለሚለው ግን አገሪቷ ሁለት ስጋቶች ስላሉባት ነው።
አንደኛው ስጋት ከባቢያችን ነው። «ሆርን አፍሪካ» የምንለው ስጋት ነው። ሁለተኛው በየጊዜው እየተቀያየረ የመጣው የዓለም ሁኔታ አገራችን ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ ነው። እነኝህን ሊመክት የሚችል የጸጥታ መዋቅር ለመገንባት ነው። ሕዝብ በሰላም ወጥቶ በሰላም የሚገባባት፣ ልማት ያለምንም የጸጥታ እንቅፋት የሚሳለጥባት አገርን መፍጠር ነው።
በእርግጥ አገር ችግር ውስጥ ባለችበት ጊዜ ልዩ ኃይሎች የክልላቸውን ፀጥታ ይጠብቁ ነበር፤ ከመከላከያ ጋር ሆነው አብረው ሞተዋል። ቆስለዋል፤ ደምተዋል። ይሁንና የልዩ ኃይሉን ጥንካሬ መስዋዕትነትና ልፋት እንዳለ ሁሉ በሌላ በኩል እጥረቶችም አሉ። እጥረቶችን የሚገልፁ ማሳያዎች ምንድን ናቸው? ካልን ሕገ-መንግሥት ነው፤ ከሕገመንግሥት አንፃር ስናይ እነዚህ ኃይሎች ሕጋዊ አይደሉም። ሕገመንግሥቱ እውቅና አይሰጣቸውም።
የኢትዮጵያ ሕዝብ ማወቅ ያለበት በአገሪቷ የፀጥታ ኃይል እንዲገነባ የሚፈቅደው ሕግ መንግሥት መከላከያና ፌዴራል ፖሊስን ነው። ከመከላከያ ውጪ የታጠቀ ኃይል ኢትዮጵያ ውስጥ መኖር የለበትም። የታጠቀ ኃይል ሕግ የሚፈቅደው መከላከያ እና የብሔራዊ ደህንነቱ ነው። ከዚህ ውጪ ሕገመንግሥቱ ላይ መብት የተሰጠው የለም። በሌላ አነጋገር ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ እንዳሉት፣ በኢትዮጵያ ውስጥ 14 ሬንጀር መመስረት አይቻልም።
አሁን ላይም የኢትዮጵያን የግዛት አንድነት ለማስጠበቅ እና አንድነቱ የተጠናቀረ እንዲሆን በሚል መልሶ ኃይሉን የማደራጀት ሥራ በየክልሉ ተጀምሯል። በፕሮግራሙ መሠረትም በሕገ መንግሥቱ የፀጥታ ኃይል፤ መከላከያ፤ ፌዴራል ፖሊስ ይኖራል። በክልሎች መደበኛ ፖሊስ ይኖራል። ሲደመር ሦስት ሬንጀር ይኖራል።
እንደሚታወቀው ገደብ የሌለው ነፃነት ጥፋት ያመጣል። በጎበዝ አለቃ የሚመራ አገር ግድግዳው እንደዘመመ፣ ጣራው እንደተቀደደ፣ ማገሩ እንደላላ ደሳሳ ጎጆ ነው። የጊዜ ጉዳይ እንጂ ጎጆው መፍረሱ አይቀርም። ይህ እንደመሆኑ የመንግሥት ውሳኔ ፋይዳው ዘርፈ ብዙ ነው።
ከሁሉ በላይ ብሔርን የማያይ፤ ዘርን የማይመርጥ ኢትዮጵያዊ የሆነ የፀጥታ መዋቅር ይገነባል። በዚህ መልክ የተዋቀረ ኃይል መኖሩም ከማንም በላይ የአገር ሉአላዊነትና ደህንነት እንዲሁም የሕዝቡን የሰላም ዋስትና ያረጋግጣል። መከላከያውም በየመንደሩ በየክልሉ ከሚደራጀው ኃይል ጋር ፖለቲከኛው ባመፀ ቁጥር ከመጋጨት እረፍት ያገኛል።
ይህን ውሳኔ አብዛኞቹ ክልሎችና የፀጥታ አካላት ተቀብለው ለውጤታማ ትግበራው ተባባሪ መሆናቸውን ከቃል ባለፈ በተግባር እያረጋገጡ ናቸው። በአንዳንድ አካባቢዎችም ከተግባቦት ውስንነትና ከኮሚኒኬሽን ችግር አንፃር በተዛባ መልኩ የመረዳት አዝማሚያ ታይቷል።
በተለይ በብሔር ፖለቲካ ልቦናቸው የተሰወረ፣ የአጥንት ፖለቲካን የሚወረውሩና ሕዝብን በማደናበር በማሳመፅ ፍላጎታቸውን ለማሳካት የሚታትሩ ተፈልፍለዋል። እጅጉን በሚያስተዛዝብ መልኩ አንዳንድ ግለሰቦችና የፖለቲካ ፓርቲ አባላት ትናንት በይፋ የልዩ ኃይል አደረጃጀት ተፈትሾ ማስተካከያ ይደረግ ሲሉ ከርመው አሁን እሺ ሲባሉ የእናቴ መቀነት አደናቀፈኝ እንዳለው ሲሆኑ እያስተዋልን ነው።
በአንዳንድ ማህበራዊ ሚዲያዎች፤ በአንዳንድ የፖለቲካና ወታደራዊ አመራሮች ላይ የሚነሱ አሉባልታዎች ወይም ደግሞ ስም የማጥፋት ዘመቻዎች እያስተዋልን እንገኛለን። እነዚህ የነገድ ፖለቲካ አራማጅ በመንደርተኛ አስተሳሰባቸው የሕዝብን ስሜት ለመቀስቀስ የሚጠቀሙበት ስልትም ተለዋዋጭ ነው። አንደኛው ‹‹ትጥቅህን አስፈትተው ሊበትኑህ ነው›› የሚል ነው።
ይሁንና ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ እንዳረጋገጡት እየተባለ ያለው ይህ አይደለም። ይልቁንስ ይህ ትልቅ ኃይል የኢትዮጵያ ኃይል ነው። እንጠቀምበት። ወደ ትክክለኛ ቦታውና ልኬታው እናምጣው ነው። እንበትነው አልተባለም፤ ትጥቁን እናስፈታው አልተባለም። የተባለው ሁሉንም እንደፍላጎቱ በአዲስ አደረጃጀት እናዋቅረው ነው። ውሳኔው ወደ መከላከያ ማስገባት፤ ወደ ፌዴራል መንግሥት ማስገባት፤ ወደ መደበኛ ፖሊስ ማስገባት ነው። በማን? በራሱ ምርጫ፤ በምን? ክብሩን በማይነካ፤ በምን? ሞራሉን በማይነካ፤ በምን? ጥቅሙን በማይነካ መልኩ።
ልዩ ኃይል ትጥቅ ሊፈታ ነው የሚለው ሀሰት ነው። እንዲያውም ሌላ መሣሪያ እንሰጠዋለን። የተባለው ሌላ ብረት እንሰጥሃለን እንጂ ትጥቅ ፍታ አይደለም። ያለም የለም። ከእኛ ጋራ ነው የሞትከው ወደ ሕጋዊ መስመር እናስገባው እንጂ እንበትነው አላልንም።
ሌላኛው የውዥንብር አጀንዳ ደግሞ ማን ፈትቶ ማን ሊቀር ዓይነት ነው። እንደ እኔ እምነትም የአገር የማዕዘን ድንጋዩ ሁሉም ዜጋ የሚኮራበትና የሚንከባከበው እንጂ አንዱን አስኮርፎ ሌላውን የሚያስደስት አይሆንም። መርጦ የመስማት ትልቅ በሽታ የሌለበት ካልሆነ ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ እንዳሉት፣ አንደኛው ክልል ኃይል እንዲኖረው ሌላው ክልል ግን ኃይል እንዳይኖረው አይደረግም።
ይሄ ኢትየጵያ ውስጥ አይታሰብም። ከልሎች ሊይዙት የሚችሉት ኃይል አንድ ነው፤ ይሄም መደበኛ ፖሊስ ነው። ከዚህ ውጪ አይዙም። መደበኛ ፖሊስ አድማ በታኝ ይኖራል ከዚህ ውጪ አይፈቀድም። ሕጉም አይፈቅድም።
አፈፃፀሙም እኩል የሚከወን ነው። አንደኛውን አሳብጦ አንደኛውን ማርገብ አይደለም። የታጠቁ ኃይሎች ትጥቅ ይፈታሉ። የትግራይ ክልል እንደማንኛውም ክልል የሚኖረው መደበኛ ፖሊስ ብቻ ነው። የታጠቀ ልዩ ኃይል የሚባል በፍፁም አይኖረውም።
አገርን ወደኋላ የሚጎትት የማይጠቅም አስተሳሰብ በአዲስና በተሻለ አስተሳሰብ መለወጥ ከዜጎች የሚጠበቅ ተግባር ነው። ያረጀውን ማደስ፣ የሌለውን ጥበብ መፍጠር፣ ያልነበረውን መልካም ተሞክሮ መቅሰም ከተማረ ትውልድ የሚጠበቅ ልዩ ተግባር ነው። በዘመን ሂደት፣ በትውልድ ቅብብል የማይጠቅምን ፖለቲካ ማራመድ ለፖለቲከኛውም፣ ለሕዝቡም ለአገሪቷም የሚያመጣው በጎ ነገር የለውም።
በመሆኑም ለአንድ መከላከያ እውን መሆን ካለው ሁለንተናዊ ትርፍ አንፃር ሕዝቡ ከመንግሥት ጎን ሊሆን ይገባል። ቆም ብሎ በማሰብ አላስፈላጊ የሆነውን መንገድ ከመከተል ሊቆጠብም ይገባል። የGestalt Psychology አስተምሮ ‹‹The whole is greater than the sum of each parts ›› እንደሚለው የአንድን ነገር ገጽታ የምንገነዘበው በጥቅል ውቅሩ እንጂ በነጠላ ይዘቱ አይደለምና ነጠላ አተያይና ፍርድን ማስወገድና ከመፍረድ በፊት ሙሉ ምስልን መመልከት መልመድ ይገባል።
መንግሥትም እያንዳንዱን ውሳኔና አፈፃፀሙን በየጊዜው ለሕዝብ ማሳወቅ መፈተሽን ሊዘነጋው አይገባም። የደህንነት ስጋት ባለባቸው አካባቢዎችና ክልሎችም መንግሥት አስተማማኝ የመከላከያ ሰራዊቱን በአግባቡ ማስፈር ግድ ይለዋል። ምክንያቱ ደግሞ በአንዳንድ አካባቢዎች ውሳኔን ለመቀበል ዳተኝነት የሚታየው ከደህንነት ስጋት ነውና።
የክልሎች የጸጥታ ኃይልም ለውሳኔው ውጤታማ ተግባራት ከመንግሥትና ከመከላከያ ጎን መቆም ይኖርበታል። ፖለቲከኞችም ሆነ አክቲቪስቶችም በውሸት ትርክት የራሳቸውን ድብቅ አላማ ለማሳካት ከመትጋት ይልቅ አላማውን በቀና መልኩ ለመረዳት መሞከርና አማራጭ ማድረግ ይኖርባቸዋል። ከዚህ ባለፈ ካለ በቂ እውቀትና በአግባቡ ካለመረዳት በመከላከያው ሥራ እየገቡ ውዥንብር በመፍጠር በጉልበትና በአመፅ ከቀውስ ለማትረፍ ከመትጋት ሊቆጠቡ ይገባል።
መታወቅ ያለበት አብይ ጉዳይ ቢኖር ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ እንዳሉት፣ ዘርን መነሻ አድርጎ በጉልበት ስልጣን እይዛለሁ፤ መንገድ በመዝጋት ስልጣን እይዛለሁ፤ ሕዝብን በማሳመፅ ስልጣን እይዛለሁ፤ አሁን ላይ አይሰራም። በፍፁምም አይፈቀድም። ስልጣን ለመያዝ የሚፈቀደውም አንድና አንድ መንገድ ብቻ ነው፤ ይኸውም የኢትዮጵያ ውስጥ ይመራኛል ያለውን 11 ሰዓት ተሰልፎ እንደመረጠ ጊዜው ሲደርስ 11 ሰዓት ድረስ ተሰልፎ ማውረድ ብቻ ነው። አንድን መንግሥት ማውጣትም ማውረድም የሚቻለው ሕዝብ ብቻ ነው። ከዚህ ውጪ ስልጣን በጉልበት አይገኝም።
ታምራት ተስፋዬ
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 6 ቀን 2015 ዓ.ም