አፍሪካን ልክ እንደ ቅርጫ ስጋ በመበጣጠስና በመቆራረጥ በሚመቻቸው መጠን ማሳነስና ባሪያ አድርጎ ማስቀጠል የአውሮፓውያኑ የወቅቱ ህልም ነበር ። የወቅቱ ሀሳብ አመንጪ ፖርቹጋል ብትሆንም አውሮፓውያን በሁሉም አጋጣሚ አፍሪካን ለመበዝበዝ ተዘጋጅተው ነበር ።
በአውሮፓውያን የቅርጫው ድርድር (ክፍፍል) ሲወጣ እድለ ቢሷ ጣሊያን ከወደ ምስራቅ አፍሪካ የሆነችውን በተፈጥሮ ሀብት የበለፀገችው “ኢትዮጵያ” የምትባል አገር ደረሳት። አንዳንድ እጣ አነሳስ ወደ መቃብር ሊያመራ እንደሚችል አላወቀችምና ጣሊያን የደረሳትን ድርሻ በፈገግታ ነበር የተቀበለችው።
ያልተነካ የተፈጥሮ ሀብትን ነፋሻማ አየሯን የለመለመች ምድርን ለመቀራመት ባሰበችበት ሰዓትም ልቧ በደስታ ዘለለች፤ ወደ ማዕበል እሳት እየተጓዘች ስለመሆኑ ግን ምንም አልጠረጠረችም።
ታዲያ ትልቅ ምኞት ደስታና ሀብት ሰንቃ አይኗን በጨው ታጥባ ጉዞዋን ወደ ኢትዮጵያ ያደረገችው ጣሊያን በኃይልና በማደናገር ብርቅየዋን አገር ለመቆጣጠር እቅድ ነድፋ ተንቀሳቀሰች፤ በወቅቱም ከእቅዶች መካከል የማደናገሪያ ወይም የማምታቻ “ውል” ማዘጋጀት አንዱ ነበር።
የውጫሌ ውል በሚያዝያ 1881 ዓ.ም በአሁኑ አምባሰል ወረዳ ውጫሌ በምትባል ቦታ በዳግማዊ አፄ ምኒልክና በጣሊያኑ ንጉስ አምቤርቶ መካከል ተፈረመ። የውጫሌ ውል 20 አንቀጾች ያሉት ሲሆን አንቀጽ 17 ላይ የሰፈረው ፅሁፍ በኢትዮጵያ በኩል ተቀባይነት በማጣቱ ለጦርነቱ መቀስቀስ ምክንያት መሆኑን ደግሞ የተለያዩ የታሪክ ድርሳናት ያወሳሉ።
በዚህም የአንቀፁ የጣሊያንኛ ትርጉም የኢትዮጵያ መንግስት ከውጭ አገር መንግስታት ጋር የሚያደርገውን ግንኙነት በኢጣሊያ መንግስት አማካኝነት ማድረግ ይገባል የሚል ሲሆን ነገሩ ግን የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት በቀጥታ በጣሊያን በኩል እንዲከናወን የሚያስገድድ ነበር።
በአንቀጽ 17 አማካኝነት ጣሊያን የውሉን ሀሳብ በጣሊያንኛ በመቀየር የኢትዮጵያን ሉአላዊነት በማጥፋት የጣሊያን ሞግዚት እንድትሆን ቀዳዳ ያበጀ ነው ብለው ነገስታቱ እና መኳንቱ ስለተገነዘቡ የውጫሌ ውልን እንደማይቀበሉት አሳወቁ።
እትጌዋም “እኔ ሴት ነኝ፣ ጦርነት አልወድም ግን እንዲህ መሳዩን ውል ከምቀበል ጦርነት እመርጣለሁ” ብለው ቆርጠው ተነሱ። ከዚህም በኋላ ንጉሰ ነገስት ዳግማዊ አፄ ሚኒሊክ ለመላው ኢትዮጵያውያን ጥሪ አቀረቡ፤ ከአራቱም አቅጣጫ የተመመው የኢትዮጵያ ስራዊት ወረኢሉ ከትሞ እንዲጠብቅ ከንጉሱ በኩል ትዕዛዝ ተላለፈ።
የአገራቸውን መሪ ጥሪ በደስታ የተቀበሉት የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች ያላቸውን ነገር ሁሉ ጥለው እምቢ ለአገሬ ብለው ንጉሱን ተከትለው ጦር አንግበው ግስጋሴያቸውን ወደ ዓድዋ ተራሮች አደረጉ።
የካቲት 23 ቀን 1888 ዓ.ም ንጋት ላይ አገሬን ነፃነቴን ክብሬን አላስነካም በሚል ወገን በአንድ በኩል፣ በሌላ በኩል ደግሞ በእብሪት ከተወጠረ ዘመናዊ የጦር መሳሪያ ከታጠቀ ከተቀናጀ ሰራዊት ጋር የዓድዋ ጦርነት ተደረገ።
በጦርነቱ ውጤት ጣሊያን በዓድዋ ላይ ተሽመድምዳ መውደቋ መሸነፏ በመላው አውሮፓ ሲሰማ የዜና ምንጮችም ቀዳሚ ዘገባቸው ሲያደርጉት ትልቅ አግራሞት ቢፈጥርም በተቃራኒው ደግሞ ለመላው አፍሪካውያን የመነቃቂያ በዓለም ላይ አዲስ ክስተት የማያ ጊዜ ሆነ ። ጥቁሮች በጦር ሜዳ ተሰልፈው በራሳቸው ወግና ባህል ወኔና ጀግንነት ነጮችን ማሸነፍ እንደሚችሉም የብስራት ደውል ተደወለ።
አይቻልምን ወደ ይቻላል የቀየሩ ለዓለም አዲስ ክስተትን ያስተዋወቁ ነፍሳቸውን የገበሩ አጥንታቸውን የከሰከሱ አባቶቻችን እና እናቶቻችን ውለታቸው ምን ይሆን ብድራቸውስ እንዴት ይከፈል ይሆን። ይህ ደግሞ የእኛ የአሁኖቹ ትውልዶች የምንጠይቀው ጥያቄ ነው።
የዓድዋ ድል የአፍሪካ ጦር የአውሮፓውያንን ጦር የደመሰሰበት ብቻ ሳይሆን የጥቁር ኃይሎች ከነጭ አውሮፓውያን ኃይሎች ጋር በመፋለም ታሪካዊ የበላይነትን ያስመዘገቡበት አንፀባራቂ፣ አስደናቂ አስደማሚ ብሎም ለኋላው ታሪክ ለፊተኛው ደግሞ ትልቅ ትምህርት ቤት የሆነ ድል ነው።
ዓድዋ ለሰለጠነችው ጣሊያን ታላቅ ውርደትና ሞት፣ ለነጭ አውሮፓውያን በሙሉ ደግሞ ሃፍረትና ስብራት ሲሆን ለኢትዮጵያን እና ለመላው ጥቁር ህዝቦች ደግሞ ደማቅ የድል ድል ሆኖ ዛሬም ድረስ ቀጥሏል።
የኢትዮጵያ የዓድዋ ድል ዓለምን የታሪክ አካሄድ የለወጠ ነጮች በጥቁሮች ላይ የነበራቸውን የበላይነት ያፈረሰ ለነጭ ገዢዎች መራር የማይዋጥ ሽንፈት የሆነበት ለጥቁር ህዝቦች ግን ታላቅ ትንሳኤና የማንነት ትግል የተረጋገጠበት ነበር።
ዓድዋ የማይሰረዝ የማይጠፋ የማይቀየር እስከ ዘለዓለም ሲዘከር የሚኖር አልፋና ኦሜጋ ድላችን ነው። ዓድዋ የአካልና የመንፈስ ጥንካሬ የፅናት ተምሳሌት ነው። ይህ ጽናትና አልበገር ባይነት ደግሞ በእኛዎቹ በዛሬዎቹ ትውልድ ይደገም ዘንድ በየዓመቱ የኋሊት እየተጓዝን እንዘክረዋለን።ነገር ግን ከመዘከር ባለፈ ዓድዋን ሆነን ለመገኘት ምን ያህል ጽናት አለን?
አባቶቻችን በደምና አጥንታቸው ጠብቀው ያቆዩትን ምድር እኛ በአስተሳሰባችን ካጠበብነው የቱ ጋር ነው የእነሱ ልጅነታችን ? አንድ ለመሆን የተዋደቁ እናትና አባቶቻችን አጥንትና ደማቸው አደራ ይሁነን። ለአገሩ ክብር ሲል ደረቱን ለባሩድ የሰጠው ወገኔ መንፈሱ አይውቀሰን ያንን ጊዜ እናስታውስና ለአንዲት ኢትዮጵያ ዘብ እንቁምላት።
እኛ የማን ልጆች እንደሆንን እናሰላስል የአባቶቻችንን የሞራል ልዕልና በእኛም ላይ ይታይ ። ራሳችንን እናክብር አገራችንንም በተግባር እንጥቀም። ዛሬም የዓድዋን ድል መሰል የጀግንነት ስራ ከሁላችንም ይጠበቃል።
ከጥበት ወጥተን ለአገራችን ልንሰራባቸው የሚገቡ በርካታ የቤት ስራዎች ያሉን ህዝቦች ነን። አገራችን እንደ ዓድዋው ዘመን በቀጥታ ቅኝ ሊገዟት ባይመጡም በእጅ አዙር ሊያንበረክኳት የእነሱ ተላላኪ የሆነ መንግስት ሾመው እንደፈለጉ ሊፈልጧት ሊቆርጧት የሚቋምጡ በርካታ የዓለም አገራት መኖራቸው የአደባባይ ሚስጥር ነው።
ይህንን የእጅ አዙር ቅኝ ግዛት ስናከሽፈው ቆይተናል አሁንም እያከሸፍነው ነው። ይህንን ለማስቀጠልም ወደፊትም ብዙ ይጠበቅብናል። ለዚህ ደግሞ ትልቁ ኃይላችን የኋላውን ታሪካችንን ስንቅ አድርገን ለዛሬው ማንነታችን በአንድነት ቆመን መስራት ስንችል ብቻ ነው።
በመሆኑም እንደ ዓድዋው ጊዜ ልዩነቶቻችንን ወደጎን በማድረግና በዓለም ላይ ያለን ኢትዮጵያውያን በሙሉ በአንድ አፍ ተናጋሪ በአንድ ልብ መካሪ ሆነን በመቆም ችግሮቻችን ላይ በመዝመት ዓድዋን መድገም ይጠበቅብናል።
አስቸጋሪ ነገሮችን አሸንፈን ከችግሮቻችን በላይ ሆነን በመገኘት የአባት የእናቶቻችንን አደራ የምናስቀጥል ትውልዶች ልንሆን ይገባል። ከዓድዋ ጀምሮ የኢትዮጵያን እድገት የማይመኙ ይልቁንም በተፈጥሮ ሃብቷና በልጆቿ በመነገድ መበልጸግ የሚፈልጉ ኃይሎች ዛሬም ድረስ አሉና የኋላውን ታሪካችንን እየነገርን ዛሬም የአባቶቻችን ልጆች መሆናችንን ደግሞ በስራዎቻችን ልናስመሰክር ይገባል። አበቃሁ!
በእምነት
አዲስ ዘመን መጋቢት 3 ቀን 2015 ዓ.ም