ወቅቱ እኤአ 1908 ነው። በኒዮርክ ከተማ ነዋሪ የሆኑ ጥቂት ሴቶች የተሻሻለ የሥራ ሰአትና ደመወዝ እንዲኖራቸው፣ የመምረጥ መብታቸው እንዲከበር አደባባይ በመውጣት ድምጻቸውን አሰሙ። ከአንድ ዓመት በኋላም የአሜሪካን ማህበራዊ የሴቶች ብሄራዊ ቀን በማለት ማወጁን የታሪክ ድርሳን ያስረዳል። በዚህ የአመጽ እንቅስቃሴ ስሟ ጎልቶ የሚነሳው ክላራዚክትን የተባለች ሴት በየዓመቱ በዓለም ዙሪያ የሚከበረው ዓለም አቀፍ ሴቶች ቀን (ማርች 8) ዓለምአቀፋዊ ቅርጽ እንዲይዝ በማድረግ ጉልህ ሚና ተወጥታለች፡፡
በብዙ ትግል ድል ያጎናፀፉትን ማሰብና ቀኑን መዘከር ግድ ይላል። ታዲያ ትግሉን በማስቀጠል በማህበራዊ፣ በኢኮኖሚና በፖለቲካው ዘርፍ ጠንካራ የሆኑ ሴቶችን ማፍራት ሳይዘነጋ ነው። መብቶቻቸውን ለማስከበር፤ ከወንዶች ባልተናነሰ አምራች ሆነው እራሳቸውንና ቤተሰባቸውን ለማስተዳደር ብሎም በሀገር ኢኮኖሚ እድገት ውስጥ ሚና እንዳላቸው በተግባር ያሳዩ ሴቶችንም ማፍራት ተችሏል። የሥርዓተ ፆታ እኩልነት እስኪረጋገጥ ግን ትግሉ መቀጠል አለበት። የወንድ የበላይነትና ሴቷን የበታች አድርጎ ማየት ጎልቶ በሚስተዋልባቸው እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ሀገራት ደግሞ ሥራዎች ይጠበቃሉ፡፡
በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ሴቶች በማህበራዊ፣ በኢኮኖሚያዊና በፖለቲካው መስክ አበረታች የሆነ እንቅስቃሴ እያደረጉ ቢሆኑም በማህበረሰቡ የተሳሉበት ሥነልቦና ጥንካሬያቸው አጉልቶ እንዳይወጣ ተጽእኖው አድርጓል። እንዲህ በተለያየ ጫና ውስጥም ሆነው ግን ለቤተሰባቸው፣ ለአካባቢያቸውና ለአገራቸው የላቀ አበርክቶ እያደረጉ ይገኛሉ። በአርዓያነትም የሚጠቀሱ ሴቶችን ማፍራት ተችሏል፡፡
ሴቶች በተሰማሩበት ማንኛውም የሥራ ዘርፍ ውጤታማ ከመሆን ውጭ ምርጫ የላቸውም። ምንም እንኳን የወንድ በሆነ ዓለም ውስጥ ሴቶችን ወደፊት ማውጣት ቢከብድም፤ ወደፊት ለወጡት ወንዶች ግን የጀርባ አጥንት መሆናቸው ዓለም የመሰከረውና የሚታይ ሃቅ ነው። ሴቶች የማይቻል የሚመስለውን ሁሉ ችለው፤ ቀዳዳውን ጠግነው፤ የጎበጠውን አቃንተው፤ ለችግሮች ሁሉ እማ መላ ሆነው፤ ጨለማውን ገፈው ብርሃን መሆን ይችላሉ። ሴት ልጅ እናት፣ እህትና ሚስት ከመሆን ባለፈ በቤት ውስጥና በተለያዩ ማህራዊ ግንኙነቶች እንዲሁም አገራዊ በሆኑ ጉዳዮች ውስጥ ሳይቀር ትርጉም ያለው ሥራ በመሥራት አገርን መለወጥ የምትችል ተፈላጊና አስፈላጊ ናት።
የሴቶች ተፈላጊና አስፈላጊነት የሰው ዘርን በመተካት ትውልድን የማስቀጠል ብቻ አይደለም። ከመውለድና ከማሳደግ ጸጋቸው ባለፈ አበርክቷቸው የትየለሌ ነው። በተፈጥሮ ከተሰጣቸውና ልዩ ከሚያደርጋቸው ተፈጥሯዊ ባህሪ በተጨማሪ ሴቶች ዕድሉ ከተሰጣቸው በየትኛውም መስክ ቀዳሚና ልዩ መሆን የሚችሉ ብርቱዎችና አገርን በበጎ የሚያስጠሩ ናቸው። ከቀደሙት ቀደምቶች ብንነሳ ሉሲ (ድንቅነሽ) ኢትዮጵያ የሰው ዘር መገኛ ለመሆኗ ማረጋገጫ ምሳሌ በመሆን ለአገር ኩራት የሆነችው ሉሲ (ድንቅነሽ) ሴት ናት።
ሉሲ (ድንቅነሽን) በቀዳሚነት አነሳን እንጂ በቀደመው ዘመንም ይሁን አሁን ባለንበት ዘመን ተዓምር የሠሩ፣ እየሠሩ ያሉና መሥራት የሚችሉ እልፍ አዕላፍ እንስቶች አሉ። በፖለቲካው፣ በኢኮኖሚውና በማህበራዊ እንቅስቃሴያቸው አንቱ የተባሉ ለቁጥር የበዙ ኢትዮጵያዊ እንስቶች አሉ። በአስራ አምስተኛው ክፍለ ዘመን በአፄ ዘርዐያቆብ ዘመን ሴቶች ከማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አበርክቷቸው በተጨማሪ በፖለቲካው ዘርፍ ከፍተኛ ተሳትፎ ነበራችው። ንጉሱ ዘጠኝ ሴቶችን በከፍተኛ የመንግሥታቸው አመራር ውስጥ ሾመው እንደነበርም ታሪክ ይነግረናል። በአፄ ልብነድንግል የንግሥና ዘመንም ንግሥት እሌኒ የንጉሡ አማካሪ ነበረች። የአክሱም ሥልጣኔ ንግሥት የሰለሞናዊ ስርዎ መንግሥት አስጀማሪ ንግሥተ ሳባንም ማንሳት እንችላለን። በዘመነ መሳፍንት ወቅትም እንዲሁ ጉልህ ተሳትፎ የነበራቸው በርካታ ሴቶች ስለመኖራቸው ታሪክ ያስረዳል።
ዘመነ መሳፍንት ሲነሳ ለዛሬ ነጻነት የበቃንበት የዓድዋ ድል ደምቆ መታየቱ የግድ ነው። ከኢትዮጵያ አልፎ ለአፍሪካውያን ኩራት የሆነውና ደማቅ አሻራ ያኖረው የዓድዋ ድል ሲነሳ ደግሞ እቴጌ ጣይቱ ብጡል ከፊታችን ድቅን ማለታቸው አይቀሬ ነው። ጀግናዋ ሴት ጠንካራና ብልኋ መሪ ጣይቱ ብጡል በእቴጌነት ዘመናቸው የነበራቸው የፖለቲካ እና የአመራር ተሳትፎ ከፍተኛ ነበር። ብዙዎች እንደሚስማሙት እቴጌ ጣይቱ የጦር መሪ፣ የጦርነት ዘዴ ቀያሽ፤ የአዲስ አበባ ከተማ እንድትመሰረት ሐሳብ አመንጭ፤ ብልህ እና ጥበበኛ ሴትም ነበሩ።
የፖለቲካ ተሳትፏቸውን እንደማሳያ ብንጠቅስ፣ ኢትዮጵያን በኃይል በቅኝ ለመግዛት የመጣው ወራሪው ፋሽስት ጣሊያን በውጫሌ አንቀጽ 17 የውል ስምምነት ላይ ኢትዮጵያን ከጨዋታ ውጭ ሊያደርጋት የነበረውን ሴራውን በማክሸፍ ሚና የነበራቸው እቴጌ ጣይቱ ውሉ ሊያስከትል የሚችለውን አገራዊ ጉዳት ቀድሞ በመረዳት ንጉሠ ነገሥቱ አፄ ምኒልክ ውሉን ቀደው በጣልያን ላይ ጦርነት እንዲታወጅ ጠንካራ አቋም የወሰዱ ብርቱና ኩሩ ሴት መሆናቸውን ታሪክ ያስታውሳቸዋል። በዓድዋው ጦርነት በተዋጊነት እንዲሁም በጦርነቱ የተጎዱትን ወታደሮች በማከምና በማበረታታት በአጠቃላይ በኢትዮጵያ የአርበኝነት ታሪክ ውስጥ ያለተነገረላቸው ብዙ ሴቶች መኖራቸውን ታሪክ ያስታውሳል።
ከቀደምቶቹ መለስ ስንል ታዲያ ዛሬም በጦር ሜዳው መስክ ዳር ድንበራቸውን ለማስከበር የሚዋደቁ ጀግኒቶችን ቤት ይቁጠራቸው። ከጦር ሜዳው ባሻገርም ኢትዮጵያ ስሟ በዓለም መድረክ ከፍ ብሎ እንዲጠራ የሚተጉ ሴት አትሌቶቻችን እልፍ ናቸው። ‹‹ወላድ በድባብ ትሂድ›› እንዲሉ ከለምለሟ ምድር ኦሮሚያ፣ ከሰሜኑ የአገሪቷ አካባቢ እንዲሁም ከደቡብ የሚተካኩቱ የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ በዓለም አደባባይ ደግመው ደጋግመው ከፍ አድርገዋል።
በማህበራዊ ዘርፉም እንዲሁ በአበርክቷቸው ነጥረው የወጡ በርካታ ሴቶች አሉን። ከእነዚህም መካከል ወላጅ አልባ ለሆኑ ህጻናት እናትም አባትም ሆነው የብዙ ህጻናትን ዕድል ፈንታ መስመር የቀየሱ ወይዘሮ አበበች ጎበናን ማንሳት የግድ ነው። ‹‹ስም ከመቃብር በላይ ይውላል›› እንዲሉ አበበች ጎበና ሁሌም ሲወሱ የሚኖሩ የደጋግ ልቦች ተምሳሌት ናቸው። እንደ አበበች ጎበና ሁሉ ታዲያ ስማቸውን ጠርተን የማንዘልቃቸው አንድ ሺ አንድ ሴቶቻችን እናት፣ ሚስትና እህት ሆነው አገራቸውን በተለያየ ዘርፍ እያገለገሉ ይገኛሉ።
በኢኮኖሚው ዘርፍ ቢባልም ጉልት ቸርችረው ቤታቸውን ሞልተው፤ ከኑሮ ጋር ታግለው ትውልድ ከሚያፈሩ እናቶች ጀምሮ እስከ ላይኛው ወጪ ገቢ ንግድ ድረስ የሚሳተፉ ሴቶች በአገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ ጉልህ ድርሻ በመወጣት ላይ ናቸው። በፖለቲካው ዘርፍም እንዲሁ በተለያዩ የሥልጣን እርከን ላይ ሆነው አገራቸውን በታማኝነት ያገለገሉ፣ እያገለገሉ ያሉና ዕድሉ ቢሰጣቸው ደግሞ የበለጠ የሚሰሩ እልፍ እንስቶች በኢትዮጵያ ምድር አሉ። እነዚህን ብርቱና ትጉ ሴቶችን ይዘን ኢትዮጵያን ወደ ብልጽግና እናሻግር በማለት አበቃሁ ሰላም!
ፍሬሕይወት አወቀ
አዲስ ዘመን የካቲት 29 ቀን 2015 ዓ.ም