“ የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና፤”
36ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች መደበኛ ጉባዔ “የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ትግበራን ማፋጠን” በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሄደ ሲሆን 42ኛው የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ስብሰባ ባለፈው እሮብና ሀሙስ በሕብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ ተካሂዷል። ምክር ቤቱ ለሁለት ቀናት ባደረገው ስብሰባ የሕብረቱ አባል ሀገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮችና ተወካዮች ተሳትፈዋል። ከዋናው ጉባኤ ጎን ለጎን ከተለያዩ ሀገራት መሪዎች ጋር ጠቃሚ ዲፕሎማሲያዊ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑን የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል። በአንድ በኩል ወዳጅንና አጋርን የማብዛት ፤ በተለያየ ምክንያት የተያዘን ብዥታ የማጥራት ስራ እየተሰራ መሆኑ ተመልክቷል። ስለ ታላቁ የሕዳሴ ግድብና በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል ስለነበረው ጦርነትና የሰላም ሒደት ገለጻና ማብራሪያ ከሚሰጥባቸው ርዕሰ ጉዳዮች ውስጥ ይገኙበታል።
ከ 1 ነጥብ 4 ቢሊዮን በላይ ሕዝብ ላላት አህጉር ነጻ የንግድ ቀጣና እስትንፋሷ ነው ። አብዛኛው ወጣት ለሆነው ዜጋዋ የስራ ዕድል ይፈጥራል። ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ይበረታታል፤ በሀገራቱ መካከል የእርስ በርስ ንግድን ያሳልጣል። ሰፊ ገበያና የገበያ ትስስር ይጎለብታል። ለአፍሪካዊ ሸማች ጥራት ያለው ምርትና አገልግሎት በተመጣጣኝ ዋጋ ይቀርባል። ሸማቹ በጥራትና በዋጋ አወዳድሮ የመግዛት እድል ይኖረዋል። ሀገራቱም ሆነ አህጉሯ ፈጣንና ተከታታይነት ያለው ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ለማስመዝገብና ርቆ የተሰቀለውን ብልጽግና ለማቅረብ ነፃ የንግድ ቀጣና ትስስሩ የማይተካ ሚና አለው።
በርካታ ሀገራት ላለፉት 17 ዓመታት ሲታሸና ሲጎሸ ባጅቶ ካለፉት ሶስት ዓመታት ወዲህ ደግሞ ወደ ሙከራ ትግበራ ገብቷል። ነጻ የንግድ ቀጣና ስምምነቱን ከማጽደቅ አልፈው በነጻ የንግድ ቀጣናው የሚካተቱ ምርቶችንና አገልግሎቶችን ለይተው አቅርበዋል። ሀገራችንም ለኢትዮጵያና ለቀጣናው የገቢና ወጪ ንግድ መቀልጠፍ ትልቅ ሚና ያለውን በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነውን የድሬዳዋ ነፃ የንግድ ቀጠና ባለፈው ዓመት በይፋ ስራ ማስጀመሯ ይታወሳል። በነጻ የንግድ ቀጣናው የሚካተቱ ምርቶችንና አገልግሎቶችን መለየቷ እየተነገረ ቢሆንም እንደሌሎች ሀገራት የሸማቹን ጥቅም ከግንዛቤ ያስገባ ይሁን አይሁን ወደፊት የምናየው ይሆናል።
የሆነው ሆኖ ነጻ የንግድ ቀጣናው ስትራቴጂካል ግብ በመጀመሪያ ኢኮኖሚያዊ እድገትና አንድነት በማስከተል ደግሞ ፖለቲካዊ አንድነት በማምጣት የፓን አፍሪካኒዝምን ህልም እውን ማድረግ ነውና ይበል የሚያሰኝ ነው። ሆኖም ከዚያ በፊት ግጭትን ከአህጉሪቱ ለማስወገድ የሚደረገው ጥረት ይበልጥ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል የሚሉ ወገኖች አሉ ። ከ3 ነጥብ 4 ትሪሊዮን ዶላር በላይ የሚገመት ጥቅል አህጉር ውስጥ ምርት /GDP/ እና ከኤርትራ በስተቀር 55 ሀገራትን በነጻ የንግድ ቀጣናዊ ትስስር የማካተት ነገር አልጋ በአልጋ እንደማይሆን ቢታመንም ጉዞው መጀመሩ በራሱ በልክ እውቅና ሊቸረው ይገባል።
ዛሬ ቻይና በመቶ ሚሊየኖች የሚቆጠሩ ዜጎቿን ከድህነት አረንቋ ማውጣት እና በዓለማችን ሁለተኛውን ግዙፍ ኢኮኖሚ መገንባት የቻለችው በሯን ለንግድ በመክፈቷ ነውና አፍሪካም የዘገየ ቢሆንም ይህን ዳና ለመከተል መወሰኗ ይበል የሚያሰኝ ነው።በጸረ ቅኝ ግዛት ትግልና በፓን አፍሪካኒዝም መካከል ሲመናተል የኖረውን አህጉራዊ ተቋም ታሪካዊ ዳራ በአለፍ ጠቀም እንቃኝ። “የአፍሪካ ህብረት ራሳቸውን “ ንጉሠ ነገሥት “ ብለው በሚጠሩት የቀድሞው የሊቢያ ገዥ ኮሎኔል ሙአመር አል ጋዳፊ ሃሳብ አመንጭነት እ .አ .አ መስከረም 9 ቀን 1999 በትውልድ ቀያቸው ሲርጥ ከተማ በተደረሰ ስምምነት መሰረት 55 አባል ሀገራትን በማካተት እ .አ .አ ግንቦት 26 ቀን 2001 አዲስ አበባ ላይ የተቋቋመ አህጉር አቀፍ ህብረት ነው።
ህብረቱ እ. አ .አ በግንቦት 25 ቀን 1963 በ32 መስራች ሀገራት በአዲስ አበባ ተቋቁሞ የነበረውን የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን /አአድ/ ተክቷል ። ድርጅቱ ከተቋቋመለት ዓላማ ቀዳሚ የሆነውን ከ1 ነጥብ 4 ቢሊዮን በላይ የአህጉሩን ዜጎች መብትና ነፃነት እንዲከበር ከመስራት ይልቅ የአምባገነን መሪዎች ጠበቃና መከታ በመሆኑ ተቺዎቹ “ የፈላጭ ቆራጮች ክበብ “ (Dictators’Club) ሲሉ ይሳለቁበት ነበር ። አሁን አሁን ግን መፈንቅለ መንግሥትን ከማውገዝ አልፎ ከአባልነት እያገደ፣ ማዕቀብ እየጣለ እና በመፈንቅለ መንግሥት ወደ አገዛዝ የመጡትን ምርጫ በአጭር ጊዜ እንዲያካሂዱ ከማስገደድ ጀምሮ በኃይል ለማውረድ እስከማስፈራራት ደርሷል። የወተት ቢሆንም ጥርስ እያበቀለ ይመስላል። የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን እንርሳውና የኮሎኔል ጋዳፊ የጡት ልጅ እንደሆነ የሚነገርለት የአፍሪካ ህብረት ሌላው ይቅርና አባት ሀገር ሊቢያ አፍንጫው ስር በቁሙ እንደ የአሽዋ ላይ ሰቀላ ሲፈራርስ አይቶ እንዳላየ አለፈ እንዳይባል ፤ አምባገነኑንና ለረጅም ዓመታት አገዛዝ ላይ ያረጀውን የማእከላዊ አፍሪካ ፕሬዚዳንትን እና የአፍሪካ ህብረት የወቅቱ ሊቀ መንበር የነበረውን ቴዎድሮ ኦቢያን ንጉየማ ቀውሱን እንዲፈታና በሊቢያ ዴሞክራሲያዊ ሽግግር እንዲያመጣ መላኩ ለአፍሪካ ፣ ለምዕራባውያንና ለዓለምአቀፉ ማህበረሰብ ስላቅና ልግጫ ነበር ። ህብረቱ ዲፕሎማሲያዊ በሆነ አግባብ አንድም ግጭት ፈቶ አያውቅም እየተባለ ሲተች ኑሮ የኢትዮጵያንና የትህነግን ጦርነት ለዛውም በሀገራችን ጥያቄ “ለአፍሪካዊ ችግር አፍሪካዊ መፍትሔ” በሚል በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ዕርቅ ግንባር ቀደም ሚና መጫወቱ ይበል የሚያሰኝ ነው።
የሌለን ሰላም ለማስከበር ወደ ዳርፉር ፣ ብሩንዲ ፣ ሶማሊያና ማሊ ሰላም አስከባሪ ኃይል ቢላክም ዛሬ ድረስ ዘላቂ ሰላምን ማስፈን አልቻለም ። በየመን ፣ በሊቢያ፣ ደቡብ ሱዳንና በካሜሩን የእርስ በእርስ ግጭቶች ማስቆም ስለተሳነው የውክልና ግጭት መናኸሪያ እንደሆኑ ቀጥለዋል። ከአልጀርሱ ስምምነት በኋላ ህብረቱ ላለፉት 20 ዓመታት ዞር ብሎ አይቶት የማያውቀውን የኢትዮ- ኤርትራ ፍጥጫ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ተነሳሽነቱን በመውሰድ እርቅ ማውረድ ችለዋል። ውጥረቱን አርግበዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በዚህ ሳይታበዩ የሱዳን ተፎካካሪ ኃይሎችን እና ወታደራዊ ጁንታውን አቀራርቦ በማደራደር የሽግግር ሥልጣን እንዲጋሩ እና ሰላም በማስፈን የማይተካ ሚና ከመጫወታቸው ባሻገር በሱማሊያና ኬንያ ፣ በኤርትራና በጅቡቲ እና በሌሎች ሀገራት መካከልም ሰላም እንዲወርድ ጥረት አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በግል ተነሳሽነትም ሆነ እንደ ኢጋድ ግጭቶችን በውይይት ፣ በድርድር መፍታት እንደሚቻል በአጭር ጊዜ የሄዱበትን እርቀት ስንመለከት ህብረቱ የሚጠበቅበትን ያህል አለመስራቱን ያሳጣል።
በመጪው ግንቦት ስድስት አስርት ዓመታትን ሊደፍን በጣት የሚቆጠሩ ወራት የቀሩት የአፍሪካ አንድነት ድርጅት / አ አ ድ/ ወይም የዛሬው የአፍሪካ ህብረትን / 14 ዓላማዎች ቢኖሩትም የጋዜጣው አምድ ስለማይበቃ ዋና ዋናዎቹን ከእነ አፈፃፀማቸው እንመልከት ፦
1ኛ . በሀገራትና በሕዝቦች መካከል የበለጠ መቀራረብ፣ ወንድማማችነትና አንድነት መፍጠር ፤ ይህን ዓላማ ከአውሮፓ ሕብረት እንዳለ የተገለበጠና ከወረቀት አልፎ እውን ሊሆን ሊተገበር የማይችል ሲሉ ልሒቃን ያጣጥሉታል። 55 ሀገራትንና ከ2ሺህ በላይ ጎሳዎችን ይዞ ወደ ወንድማማችነት በመጨረሻም የኢኮኖሚም ሆነ የፖለቲካ አንድነት ፈጥሮ የተባበሩት የአፍሪካ ህብረት United States of Africa / USA/ እውን የማድረግ ጉዳይ ፍጹም የሚታሰብ አይደለም በማለት የሚሞግቱ አሉ። ጋናዊው ጆርጅ አይቴ ከእነዚህ ልሒቃን አንዱ ነው።
የውጭ ግንኙነትና ዓለምአቀፍ ርዕሰ ጉዳዮችን አንስቶ በመሞገትና በመተንን በሚታወቀው ፎሪን ፖሊሲ መፅሔት “ Disband the African Union “ በሚል ርዕስ ሞጋች ሳይሆን ቀጭን ትዕዛዝ ባስተላለፈ ጹሑፉ ፤ “ ህብረቱ ጠንካራ የሆነውን ማዕከላዊነት ማላላት በአንጻሩ ደካማ አደረጃጀቱን ማጠናከር አለበት። አባል ለመሆን ግልፅና ጠንካራ መስፈርት ማስቀመጥ ያስፈልጋል። በሀገራቱ መካከል የሚኖረው ግንኙነትም በግልፅ የጋራ ራዕይ ላይ የተመሰረተና በኮንፌደሬሽን የሚመራ መሆን አለበት።
“ የህብረቱ ሪፎርም ፣ በ2020 ተኩስ የማይሰማባት አፍሪካ፣ አዲስ አጋርነት ለአፍሪካ ልማት /ኔፓድ / እ አ አ 2001 ላይ ይፋ ቢሆንም የበላው ጅብ ዛሬ ድረስ አልጮኸም። ጆርጅ ህብረቱ የራሱን ቢሮ መገንባት አለመቻሉ የውድቀቱ ማሳያ ነው ሲል ይሞግታል። አይደለም የህብረቱ አባል ሀገራት 9 ቢሊዮን ዶላር በሙስና አካብተዋል የሚባሉት የቀድሞው የሱዳኑ ፕሬዚዳንት ኦማር አልበሽር ወይም የአንጎላው ፕሬዚዳንት ሴት ልጅና 3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ዶላር እንደመዘበረች የሚነገርላት ኢዛቤል ዶስ ሳንቶስ በግላቸው ሊገነቡት ይችል ነበር ሲል ይሳለቃል።
2ኛ . ዴሞክራሲያዊ ተቋማትን ፣ መርህንና መልካም አስተዳደር ማበረታታት ፤ ከፍ ብዬ ለመጥቀስ እንደሞከርሁት ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በዴሞክራሲያዊ ግንባታ ሒደት ጅምር እንቅስቃሴዎችን እያደረገ ቢሆንም ቀደም ባሉ በርካታ ዓመታት ግን ህብረቱ በአሁጉሩ “ ነፃ ፣ ፍትሐዊና ተአማኒ “ ያላለው ምርጫ የለም ማለት ይቻላል። ለዚህ ነው ተቺዎቹ የቀረበለትን የምርጫ ውጤት ሁሉ ወዲያውኑ ሳይመረምር ስለሚያረጋግጥ” ራበር ስታምፕ “ ሲሉ ቅፅል የሰጡት። ጆርጅ ከፍ ብዬ በጠቀስሁት መጣጥፉ ፤ “ … ህብረቱ ሌላው ይቅርና ዛሬ ድረስ በዴሞክራሲ ፅንሰ ሃሳብ ትርጉም ላይ እንኳ መግባባት አልቻለም ።… “ ይላል ።
3ኛ . በአህጉሩ ሰላምን ፣ ደህንነትንና መረጋጋትን ማስፈን፤ ይህ የህብረቱ ዓላማ አይደለም ሊሳካ ተባብሷል።” በ2020 የተኩስ ድምፅ የማይሰማበት አህጉር “ እውን ለማድረግ ከ10 ዓመት በፊት የጣለው ግብ ከሽፋል። ግቡ ሲጣል ግጭት የነበረባቸው ሀገራት ቁጥር ከ10 ያልበለጡ ነበሩ። ዛሬ ላይ ግጭት ውስጥ ያሉ ሀገራት ቁጥር ከ20 በላይ ደርሷል። እነ ሊቢያን ፣ ሶማሊያን፣ የመንን ፣ ሱዳን፣ ደቡብ ሱዳንን ፣ ማሊን ፣ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ፣ ቡርኪናፋሶን ፣ ማእከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክን፣ ቻድን ፣ ካሜሩንንና ሰሜን ናይጀሪያን በአብነት ማንሳት ይቻላል።
4ኛ . የሰብዓዊና የሕዝቦችን መብቶች በቻርተሩ መሰረት ማስከበር ፤ ህብረቱ የዜጎች ፣ የሕዝቦች ሰብዓዊ መብት በአምባገነኖች ሲጨፈለቅ ፣ ሲጣስ ጥብቅና ይቆም የነበረው ለአምባገነኖች ነው። ኦማር አልበሽር በተለይ በዳርፉር በጦራቸውና ጃንጃ ዊይድ በተባለ ሚሊሽያ ዘግናኝ ግፍ ሲፈፀም ትንፍሽ አለማለቱ ሲያሳዝነን ዓለምአቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ክስ ሲመሰርትባቸው ተላልፈው እንዳይሰጡ ሽንጡን ገትሮ ከመከራከር አልፎ ፤ ሀገራት ከዓለማአቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት እንዲወጡ ግፊት ሲያደርግ ነበር ። 5ኛ . በአህጉሩ ምርምርን በተለይ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ማበረታታት ፤ የአህጉሩ መለያ የሆኑትን ድርቅና ርሀብ ፣ የእርስ በርስ ግጭትና መፈናቀል ፣ የገነገነ ዘረፋ፣ …፤ ለመከላከል ፤ ምርታማነትን ለማሳደግ ፣ አህጉሩ የሚታወቅባቸውን እንደ ኤች አይ ቪ / ኤድስ ያሉ ወረርሽኞችን ለመከላከል፣ የቴሌኮም ኢንዱስትሪውን እና ዲጂታል ኢኮኖሚውን ለማሻሻል በአጠቃላይ የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሾን ቴክኖሎጂውን ለማበልፀግ ምን ሰራ !?
እንደመውጫ በዓለማችን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እንደ እንጉዳይ በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፋ የመጣው ሕዝበኝነት populism ፣ ቀኝ ዘመምነትና አክራሪነት አህጉር አቀፍ እና ድንበር ዘለል ትብብሮችን እያዳከመ ነው ። ከ2ኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ ከ70 ዓመታት በላይ ሰላምና ጸጥታን ለማረጋገጥ የማይተካ ሚና የነበራቸው እነ አውሮፓ ህብረትና የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃል ኪዳን /ኔቶ /ችላ እየተባሉ ነው ።
በተለይ “ አሜሪካ ትቅደም ! “ የሚል ሕዝበኛ መፈክር አንግበው ወደሥልጣን የመጡት ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በተባበሩት መንግሥታት ፣ በአውሮፓ ሕብረት፣ በኔቶ እና በሌሎች መሰል ስብስቦች ላይ የተከተሉት የተንሸዋረረ አመለካከት ከፍተኛ ስጋት ፈጥሮ ነበር ። ፕሬዚዳንት ባይደን “አሜሪካ ተመልሳለች !”ብለው ባያስተካክሉት ኖሮ አደጋ ላይ ወድቀው ነበር።
የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂው ዓለምን ወደ ትንሽ መንደርነት እየቀየረ ባለበት በዚህ ወቅት አክራሪ ብሔርተኞችና ሕዝበኞች ደግሞ መለየትን ፣ መነጠልን እየለፈፉ ዓለምን ግራ እያጋቡ ይገኛል። እንግሊዝ በእነ ትራምፕ አይዞሽ ባይነት ከሕብረቱ መነጠሏ እና በፈረንሳይ፣ በጣሊያንና በምስራቅ አውሮፓ አክራሪ ብሔርተኝነት እየተጠናከረ መምጣቱ ሌላ ስጋት ሆኖ ብቅ ብሏል።ወደ የአፍሪካ አንድነት ድርጅትም ሆነ እሱን ወደ ተካው የአፍሪካ ሕብረት ስንመጣ ከውጫዊ ፈተናዎቹ ይልቅ ውስጣዊ ችግሮቹ የከፉ ሆነው እናገኛቸዋለን። አራምደዋለሁ የሚለው በሀገራት የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ያለመግባት አቋም ለችግሩ አንዱ መግፍኤ ነው። የሕብረቱ አባል ለመሆን ምንም አይነት መስፈርት አለመኖሩ ችግሩን ይበልጥ ያወሳስበዋል ።ይሁንና “የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ትግበራን ማፋጠን” የሚለው መርሁ ተግባራዊ ከሆነ ዘመኑንም ሆነ ትውልዱን የዋጀ ይሆናል። ከፍ ብዬ ለመጥቀስ እንደሞከርሁት ከአህጉሩ ከ 1 ነጥብ 4 ቢሊዮን ከሚበልጠው ሕዝብ ውስጥ አብላጫው ወጣት ስለሆነ የዚህ ታላቅ ራእይ ግንባር ቀደም ተጠቃሚ ይሆናል ተብሎ ይታመናል።
የትምህርትና ሥልጠና ፣ የብድር አገልግሎትና የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን መሰረተ ልማት ግንባታ ማጎልበት ወጣቱን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ተጠቃሚ ስለሚያደርግ ልዩ ትኩረት ይሻል ። ለወጣቱ ሰፊ የስራ ዕድል የሚፈጥሩ ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት ሰጥቶ አለመንቀሳቀሱ ፤ ወጣቱን ወደ አመራርነት የሚያመጡ ስራዎችን አለማከናወኑ ፤ የወጣቱ መሰረታዊ ጥያቄ እየሆኑ የመጡት የዴሞክራሲና የነጻነት ጥያቄዎች ላይ እግሩን የሚጎትት መሆኑ በነቃፊዎቹ ዘንድ ዘመኑንም ሆነ ትውልዱን የማይዋጅ ስብስብ በሚል ሲወቀስ ኖሯል። አሁን ግን ይህን ታሪክ የሚቀይር ጅምር እንቅስቃሴ እየተስተዋለ በመሆኑ ተስፋ ተሰንቋል።
አፍሪካንና አፍሪካውያንን ፈጣሪ አብዝቶ ይባርክ!
ሻሎም !አሜን ።አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን) fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን የካቲት 12 ቀን 2015 ዓ.ም