የቅድመ ሙግት መደላድል፤
የጽሑፌ ርዕስ የተዋቀረባቸውን ቃላት ለመበየን በእጅጉ አስቸጋሪ እንደሚሆን ይገባኛል። አራቱ ቃላትና በመካከላቸው የተደነቀረችው “ዬ” የተሸከመችውን “የእኔ” የሚለውን ባለቤት አመላካች ምዕላድ በአግባቡ ተንትኖ ለአንባቢያን የልቡን ለማድረስ “ከልብ የሆነ” ዝርዝር ንባብና ጥናት ይጠይቃል። ይህንን ለማድረግ ደግሞ ጊዜ መፍጀቱ የማይቀር ነው።
ቢሆንም ግን አንኳሩ ሃሳብ እንደሚፈለገው ባይብራራም የጉዳዩ አሳሳቢነት ግድ ስለሚለንና በጋራ ውይይት ተላምጦ ሊደቅ እንደሚችል በማመን ርዕሰ ጉዳዩን ለመነካካት ግድ ብሎናል። ይህ ከተራራ የገዘፈ አሟጋች ርዕሰ ጉዳይ በአንድ ውይይት ለተግባቦት ይደርሳል የሚል እምነት ባይኖረንም ከዛሬ ጀምሮ ብናብላላው ክፋት ስለሌለው እነሆ ለጋዜጣው ቤተሰቦች የመንደርደሪያ ሃሳቡን እንደሚከተለው ይድረስ እንላለን።
ሞጋቹ ጥያቄ የሚጀምረው “አንድ ትውልድ የሚሸፍነው የጊዜ ርዝመት ስንት ዓመት ነው?” ከሚለው ይሆናል። እውነቱን ለመናገር ይህ አወዛጋቢ ጥያቄ በብዙዎች ዘንድ ሲጠየቅ ዓመታት ቢነጉዱም እስከ ዛሬ ድረስ ይህ ነው በሚባል ስምምነት ላይ የተደረሰ አይመስልም። ስለዚህም መልሱ በቀላሉ የሚታይ አይሆንም ማለት ነው።
“እብደትስ ምንድን ነው?” ይህም ቃል ቢሆን መዛግብተ ቃላት ከደነገጉለት ፍቺ ላቅ ያለ ሥነ ልቦናዊና ማሕበራዊ ጽንሰ ሃሳብ እንደተሸከመ እንረዳለን። ስያሜው በሐኪሞች የማይወደድ እንደሆነም አይጠፋኝም። የባለሙያዎቹ ምርጫ “የአእምሮ ሕመምተኛ” ወደሚለው እንደሚያጋድልም ይገባኛል። ለማንኛውም ብዙኃኑ በሚስማሙበት የተለምዶ አገላለጽ ተጠቅመን በሃሳቡ ላይ ጥቂት እንቆዝም።
በማንኛውም ግለሰብ ሕይወት ውስጥ የመጠን ልዩነት ይኖር ካልሆነ በስተቀር እያንዳንዱ ሰው በማያመልጠው ጊዜያዊ አለያም ዘላቂ ወፈፍታ
እንደሚለከፍ የሥነ ልቦና በሳሎች በጥናታቸው አረጋግጠናል ብለውናል። በአጭሩ እብደት በሁኔታዎች፣ በጊዜና በቦታ የሚወሰን የአስተሳሰብና የድርጊት ወለፈንዴነትና ግራ አጋቢነትን የሚወክል ጽንሰ ሃሳቡ መሆኑ ሊሰመርበት ይገባል።
“የእኔ ያልከው ትውልድ የሚወክለው ዘመንስ የትኛውን ነው?” ለዚህም ጥያቄ ቁርጥ ያለ መልስ ለመስጠት ብዕሬ መንተባተቡ አይቀርም። ይህም ተባለ ያ ችግሩ ጊዜ የሚሰጥ ስላልሆነና አደጋውም በቀላሉ መታየት ስለማይገባው የውጥር በተያዝንባቸው ዋና ዋና ሀገራዊ ጉዳዮቻችን ዙሪያ ልብ ተቀልብ ሆነን ልንመክርበት ወቅቱ ራሱ የሚሞግተን ይመስለኛል።
ይህ ጸሐፊ በውጭ ሀገር ትምህርት ላይ በነበረበት አንድ ዕለት “የአንድ ትውልድ የዘመን ስሌት ስንት ይሆናል?” የሚል ክርክር በተማሪዎች መካከል ተነስቶ እኛ ተማሪዎችም ሆንን ፕሮፌሰራችን በተቀራራቢ ሃሳብ ላይ ለመድረስ ተስኖን “ሲተኙ ነገር ያገኙ” እንዲል የሀገሬ ብሂል፤ ሙግቱ በይደር ይተላለፍ ተብሎ መወሰኑን አስታውሳለሁ።
በዚህ የጋራ ስምምነት ላይ በአሜንታ ተስማምተን ለሻይ እረፍት እንደወጣን ነገሩ እጅግ ስለከነከነኝ ወደ ፕሮፌሰራችን ጠጋ ብዬ “”የእርስዎን ግምታዊ ምልከታ ሊነግሩኝ ይችላሉ?” ብዬ በትህትና ስጠይቃቸው፤ ራሳቸውን ወዲያ ወዲህ እያወዛወዙና በርካታ ታሪካዊና ማሕበራዊ ጉዳዮችን እያጣቀሱ “ምናልባትም ከሃያ አምስት እስከ ሠላሳ አምስት ዓመት ሊሆን ይችላል” የሚል ፍንጭ ሰጥተውኝ ነበር። በግሌ የመምህሬ ጥቆማ ለዚህ ጽሑፍ የመነሻ ሃሳብ ግብዓት ቢሆን የሚበጅ ስለመሰለኝ ካለፈው ሦስት አሠርት ዓመታት ጀምሮ እየኖርንበት ያለውን ይህንን ወቅት እንደ አንድ የትውልድ ዘመን በመውሰድ ቅኝቴን ገድቤበታለሁ።
“ፀፀት” – ባላደረግሁት ወይንም ባደርገው ኖሮ፣ ባይሆን ወይንም ባይፈጸም ኖሮ፣ ባልተናገርኩ ወይንም በተናገርኩ ኖሮ ወዘተ. የሚያሰኘውን የውስጥ ሙግትና መብከንከንን ይወክላል። መብከንከኑ ቁጭትም ያዘለ መሆኑን ልብ ይሏል። ስሜትን ወጥሮ እንደ ሻህላ (ሻጋታ) ውስጥን የሚያመነዥከው ይህ አሉታዊ እህህታ ለቅጽበት ብቅ ብሎ የሚጠፋ ወይንም ለረጂም ጊዜ ሊሰነበት የሚችል አቅም ያለው መሆኑንም ማስታወሱ አይከፋም። የመደላድሉ ጥቁምታ እስከዚህ ድረስ ካጓጓዘን ዘንዳ ወደ ዋናው የመድረሻችን ማጠቃለያ ለመድረስ እንድንችል የንባብ ወጋችንን እንግፋበት።
የዘመናቸውን ትውልድ እብደት የሞገቱ ቀደምት ጸሐፍት፤
“ኦሮማይ” – በሚል ርዕስ እጅግ ተነባቢ የሆነ የመጽሐፍ ገጸ በረከት አበርክቶልን እንደ ተወርዋሪ ኮከብ ከስሞ የጠፋብን ነፍሰ ኄሩ ደራሲያችን በዓሉ ግርማ የራሱን ዘመንና ትውልድ የሄሰው እንዲህ በማለት ነበር። “ሩጫ ላይ ያለች ሀገር ናት። ቢከፋም ቢለማም ድርጊት! አዲሱ ትውልድ የድርጊት ትውልድ ነው። ጊዜ ያጥረናል፣ ጊዜ የለንም፣ ችኩል ትውልድ ነን። ያበደ ትውልድ። እውነት እብዶች ነን! ያሮጌው ትውልድ ሙጣጭ፤ ያዲሱ ትውልድ የበኩር ልጅ። ያንዱ መጨረሻ፤ የሌላው መጀመሪያ መሆን እብደት ነው። ያሮጣል…ንግግር! ንግግር! ንግግር! የጊዜያችን ምልክት ነው። ብዙ ንግግር ትንሽ ሥራ። የለም! ሌሎች ደግሞ ከስብሰባ ጋር ያያይዙታል። ስብሰባ! ስብሰባ! ግምገማ! ግምገማ! ብዙ ስብሰባ፣ ብዙ ግምገማ ትንሽ ውጤት” (ገጽ 13 እና 48)።
ይህ መጽሐፍ ከተጻፈ ከአርባ አመት በኋላ ያለው ይህ “የእኔ” ትውልድስ ከዘመነ በዓሉ ግርማ ትውልድ የሚለየው በምንድን ነው? የወፈፍታው ባህርይስ እንዴትና በምን ሊበየን ይችላል? በግሌ ልዩነት ያለው አይመስለኝም። “ቀልቀሎ ስልቻ፤ ስልቻ ቀልቀሎ” እንዲሉ ወይንም “ትሻልን ሰድጄ ትብስን አገባሁ” እያለ ግፍግፍ እንዳለው የጥንቱ አባወራ በግሌ ይህ ነው የሚባል መሻሻል አይታየኝም። እዚህ ድምዳሜ ላይ የደረስኩት “ጨለምተኛ” ሆኜ ሳይሆን እውነቱ ያፈጠጠ ስለመሰለኝ ነው።
እንደ በዓሉ ግርማ ሁሉ እሸቱ ብሩ ይትባረክ የተባሉ የማሕበራዊ ሚዲያ ሞጋችም ከዛሬ አምስት ዓመት በፊት ዘመኑንና ትውልዱን በተመለከተ የጥያቄ ውሽንፍር አዥጎድጉደው የልባቸው አልደርስ ቢላቸው “እኔን ታከተኝ የቀረውን እናንተ አክሉበት” በማለት ሃሳባቸውን በእንጥልጥል የደመደሙበትን ጽሑፍ እንደሚከተለው እጠቅሳለሁ።
“ይህ የዛሬው ትውልድ የት ላይ ነው ያለው? የድርጊት ትውልድ ነው ወይንስ ችኩል ትውልድ ነው? ጤነኛ ትውልድ ወይንስ ያበደ ትውልድ? ያቋራጭ ትውልድ ወይንስ የቀጥተኛው መንገድ ትውልድ? ፍትሐዊ ትውልድ ወይንስ ፊት አይቶ የሚያዳላ ትውልድ? የእንብላው ትውልድ ወይንስ የእንሥራ ትወልድ? ‹ሁሉን አውቃለሁ ባይ› ትውልድ ወይንስ የጥልቅ እውቀት ባለቤት ትውልድ? የጥበብ ትውልድ ወይንስ የመጠበብ ትወልድ? ሚዛናዊ ትውልድ ወይንስ ፅንፈኛ ትውልድ? ስሜታዊ ትውልድ ወይንስ አስተዋይ ትውልድ? የስብሰባ ትውልድ ወይንስ የውጤት ትውልድ? የፕሮፓጋንዳ ትውልድ ወይንስ የድርጊት ትውልድ? አጨብጫቢ ትውልድ ወይንስ ራሱን የሆነ ትውልድ? እህ ደከመኝሳ! እናንተም ጥያቄውን ጨምሩበታ…!” ይሉናል ጸሐፊው። እንኳንስ ልንጨምርበት የተዘረዘረውም ልባችንን ፍስስ ስላደረገ በምኑ ላይ ምን ይታከላል?!i።
የትውልዴ የወፈፍታ ምልክቶች፤
እውነት እውነቱን እንመስክር ካልን አብረን “የሕይወትን ጽዋ” እየተጋትን ያለነው ይህ የዕድሜዬ ማሕበርተኛ ትውልድ እብደት ከቀዳሚ ዘመናት ትውልዶች የመጠን ከፍታ አሳይቶ ካልሆነ በስተቀር የመሻሻል ምልክት አሳይቷል ለማለት ያዳግታል። ጥቅል ፍረጃ እንዳልሆነ ልብ ይባልልኝ። በውሱንነት የምጠቅሳቸው የመከራከሪያ ነጥቦቼ አወዛጋቢ ቢመስሉም “እውነቱን ተናግሮ የመሸበት ማደሩ” የከበረ ብሂል መሆኑን ስለማምንበት እየጠዘጠዘን ያለውን ማሕበራዊ እባጭ ጨክኖ ማፍረጡ ለፈውሳችን ስለሚያግዘን ደፈር ማለቱ ክፋት ያለው አይመስለኝም። ቅዱስ መጽሐፍስ ቢሆን “ጆሮ ያለው ይስማ!” በማለት ይመክረን የለ። “ሕመሙን የማይናገር በሽተኛ ፈውሱ መጋኛ” የሚለው ሀገራዊ ምሳሌም ሃሳቤን ይደግፍ ይመስለኛል።
አንድ፡- ይህ የእኔ ትውልድ የሃሳብ ልዩነቱን ለማቀራረብ ከምክክር ይልቅ ጋሻና ጦር ይዞ ይዋጣልን እያለ የፍልሚያ ሸማ ቢጣጣል ይመርጣል። “የወንድሙ ጠባቂ” ከመሆን ይልቅ ወንድም እህቱን ማሳደድ የሚያረካው ይመስላል። ባለራእዮችን ከማድመጥ እና ሕልመኞችን ወደ ግብ ከማቃረብ ይልቅ የመሰናክል ድንጋይ እየደረደረ መንገዳቸውን መዝጋትን ምርጫው በማድረግ የሚፈነድቅም ይመስለኛል።
ጦርነትን ከባህላዊ እስክስታ እኩል እያስተያየ ሲፎክርም አቅሉም፣ ነፍሱም አይገስጹትም። የወገን መፈናቀልና መንከራተት “የብሔርና የቋንቋ ክብር መገለጫ” እንደሆነ፣ የብዙዎችንም ስደት “የአሸናፊነቱ” ምልክት አድርጎ በማየት ሲኩራራ ማስተዋል እብደት ካልተባለ በስተቀር ምን ሊባል ይችላል። ያውም ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰ የማንነት ቀውስ።
ሁለት፡- የትውልዴ መንፈስ በዘመን አመጣሹ ቴክኖሎጂ ተበክሎ ክፉኛ የታመመም ይመስለኛል። እስከ ዛሬ ድረስ መድኃኒት ያልተፈጠረለትና ወደፊትም ፈዋሽ መድሐኒት ሊፈጠርለት ይችላል ተብሎ ተስፋ የሚጣልበት አይመስልም ግሎባላይዜሽን ብዙውን የትውልዴን ሠራዊት ለእብደት ዳርጎ ሕመም ላይ የጣለው በአጭር ዓመታት ውስጥ ነው። ስማቸው ብዙ፤ ግብራቸው ተመሳሳይ በሆኑ “እሳት አቀጣጣይ፣ መርዝ ረጭ” የማሕበራዊ ሚዲያ ወረርሽኞች ያልተጠቃ ዜጋ ለማግኘት ብዙ ማሠሥ የሚያስፈልግ አይመስልም። አንድ ሰው እንዳሉት “አእምሮው በማሕበራዊ ሚዲያ በሚሠራጩ ክፉ መረጃዎችና ክፋቶች ያልተበከለ ዜጋ ማግኘት የሚቻለው ያልተወለዱ ጽንሶች ባሉበት የእናት ማህጸን ውስጥ ብቻ ነው።”
በአንድ እጁ ሞፈር በሌላ መዳፉ የእጅ ስልኩን በማሽሞንሞን “ምን ተባለ? ማንስ ምን ደረሰበት?” የሚሉ አልባልታዎችን ሲያሥሥ የሚውል የሀገሬ አርሶ አደር ቁጥሩ ቀላል የሚባል አይደለም። ከሕጻን እስከ አዋቂ፣ ከቤት እመቤት እስከ የቤተሰብ አጋዥ “ሠራተኛ”፣ ከምሁር እስከ ተማሪ፣ ከወታደር እስከ ወዝ አደር፣ ከነጋዴ እስከ “ምንግዴ” ሥራ ጠል፣ ከዳኛ እስከ ጠበቃ፣ ከወጣት እስከ ባለ ሽበት ወዘተ. ከላይ የጠቀስነው ጸሐፊ “እህ! ደከመኝሳ!” ብሎ ጽሑፉን እንደደመደመ ሁሉንም ዘርዝሮ ለመጨረስ ልብ ያደክማል።
ከላይ የተዘረዘሩትም ሆኑ ሳናስታው ሳቸው የዘለልናቸው በርካታ የማሕበረሰቡ ቤትኞች በማሕበራዊ ሚዲያው የሚጠቀሙት በእርግጡ አዎንታዊ ጠቃሚ መረጃዎች አጓጉተዋቸው ነው ወይንስ ለሌላ አሉታዊ መሻት? ጠቅላይ ምላሽ ለመስጠት ተገቢውን ጥናት ማድረግ ግድ ስለሚል አንባቢያን የራሳቸውን ግምት ቢሰጡ ይበልጥ የተሻለ ይሆናል። በቅርቡ የሜታ (ፌስ ቡክ) ኩባንያ “የኢትዮጵያዊያን የማሕበራዊ ሚዲያ አጠቃቀም አሉታዊ ገጽታው እየሰፋ ስለሆነ በእጅጉ አሳስቦኛል” በማለት ያወጣው ሪፖርት እንደ ሀገር ዘመኔንና ትውልዴን በሚገባ የሚገልጽ ይመስለኛል።
“በአሉታዊዎቹ ላይ ከማተኮር ይልቅ ስለምን ደግ ደጉን የማሕበራዊ ሚዲያ ጥቅም አትዘረዝርም!?” ተብሎ እንደሚጠየቅ አይጠፋኝም። ለዚህ ክስ የማቀርበው መከራከሪያ ከአሁን ቀደም የማሕበራዊ ሚዲያ አጠቃቀማችንን በተመለከተ “በረከተ መርገም” በማለት ያቀረብኩት ጽሑፍ የጠቀሜታውን ብርታትና የአሉታዊ ስፋቱን ልክ የዳሰሰ ስለሆነ ተመልሼ አልከልሰውም። ሞጋቾቼ ያንን ጽሐፍ መለስ ብለው እንዲያነቡ እመክራለሁ።
በጥቂቱ ለማስታወስ ካስፈለገ ግን ከዘመን ጋር መኳረፍም ሆነ መጣላት እንደማይቻል ይገባኛል። የማሕበራዊ ሚዲያ በጎነትም አይጠፋኝም።
ያለ እርሱ ኑሮን እንግፋ ማለቱም “ወደ ጥንታዊ የጋርዮሽ ሥርዓት እንመለስ” የማለት ያህል ነው። እኔው ራሴም ብሆን የማሕበራዊ ሚዲያው ተጠቃሚ መሆኔን አልክድም። መሟገቻዬ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ አስገብሮናል፣ ሳናውቅ አዋቂ እንድንመስል እየቀረጸን ነው፣ መልካም ሥነ ምግባርን የሚያዋርዱ፣ ሃይማኖትን የሚያረክሱና ኅሊናን የሚያቆሽሹና ሰብእናን የሚያዋርዱ አረሞች ወረውናል።
ልጆቻችን በአደገኛ ሱሱ ተማርከው ከእጃችን እያመለጡን ነው። አብዛኞቹ የማሕበራዊ ሚዲያው ተጠቃሚዎች በሚገባቸውም ሆነ በማይገባቸውም ርዕሰ ጉዳዮች ዋና ተንታኝ፣ ተቺና ተሳዳቢ ወደመሆን መለወጣቸውን ስናያ እየዘንን ዘመኑን መኮነናችን አልቀረም። ሁላችንም እንዳሻችን እንድንፈነጭ መድረኩ በሠይጣናዊ ክህነት አርክሶናል ለማለትም ይቻላል። ይህ የእብደት ጥግ ተደርጎ ካልታየ ሌላ ምን ማሳያ ሊኖር ይችላል።
ሦስት፡- የሰላምና የፍቅር ተምሳሌት ተደርጎ የሚታመነው ነገረ ሃይማኖት የጠብና የሙግት፣ “የይዋጣልን” አጀንዳ ማራመጃ፣ የመከባበሪያና የመጽናኛ መልእክት ሳይሆን የዛቻና “የቆይ ጠብቀኝ!” መፎከሪያ ሆኖ ስናስተውል “አብደናል” ከማለት ውጭ ምን ማለት ይቻላል። ቅዱስ ወንጌሉን ለወንጀል፣ የተከበረው ቁርዓን ለማጥቂያ እንዲውል ማድረግ በምድርም ብቻ ሳይሆን በተስፋ በሚጠበቀው የሰማይ ቤት ጭምር የሚያስጠይቅ የከፋ ኃጢያት መሆኑ መዘንጋቱ ለእብደታችን ዋና መንስዔ ነው ቢባል አገነናችሁ ያሰኛል?
አራት፡- ፖለቲካችን ወፍፎ እኛን ዜጎችን ካወፈፈን ዓመታት ተቆጥረዋል። ኢኮኖሚው ጨርቁን ጥሎ ካበደ ሰነባብቷል። ማሕበራዊ ተራክቧችን ስንጥቁ እየሰፋ መሄድ ከጀመረም ቆይቷል። “እህ ደከመኝሳ! እናንተም ጨምሩበታ…!” እንዳለው ጸሐፊ ይህ አምደኛም ብእሩም ልቡም ድክም ማለቱ አልቀረም።
ዛሬ የምንዘራውና ለእብደት የዳረገን ክፉ ዘርፈ ብዙ ማሕበራዊ አረም በአጭሩ ተቀጭቶ መረጋጋት እስካልተቻለ ድረስ ጦሱ በዚህ ትውልድ ላይ ብቻ ተወስኖ የሚቀር አይሆንም። እብደቱ ወደ ነገው ትውልድም ተሸጋግሮ ኢትዮጵያችን “በአእምሮ ሕሙማን ሆስፒታልነት” እንዳትፈረጅ ልባችን ልብ ሊገዛ ይገባል። በቁጣና በቂም የጋለው መንፈሳችን ቀዝቅዞ ይስከን። ለበቀል የተመዘዘው ሰይፋችንና ለጥፋት ያነጣጠረው የጠብመንጃ መሣሪያችን ቁልቁል ይዘቅዘቅ። ሰላም ለሀገራችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ!
(በጌታቸው በለጠ/ዳግላስ ጴጥሮስ)
አዲስ ዘመን ጥር 17 ቀን 2015 ዓ.ም