በአገራችን ወርሀ ታህሳስ በብዙ ቀለም ይተረጎማል። በርካቶች ይህን አራተኛ ወር የጥጋብ፣ የልምላሜ፣ የፍሬያማነት መገለጫ አድርገው ይተረጉሙታል። በታህሳስ የደረሰ ምርት ይሰበሰባል። የተሰበሰበው ከአውድማው ተወቅቶ፣ ከጎታ ጎተራው ይገባል። ይህ ወር ድካም ልግመቱ የሚታይበት፣ ብርቱው ከሰነፍ የሚለይበት ጥቅጥቅ ወንፊት ማለት ነው።
ብዘዎች እንደሚያምኑት፣ መሬት የገመሰ፣ እርፍ የነቀነቀ ሁሉ ‹‹ጎበዝ፣ ጀግና›› አይባልም። በሬ ጠምዶ ጅራፍን ሲያደምቁ ፣ ሲያጮሁ መዋልም ከብርቱዎች ጎራ አያሰልፍም። ላቡን አንጠፍጥፎ፣ ጉልበቱን ገብሮ ከእርሻው ተግቶ የዋለ ብርቱ ከአያያዙ ማንነቱ ያስታውቃል።
ይህ አይነቱ አራሽ ምርቱን ከግርዱ የሚለየው ገና በጠዋቱ ነው። ማለዳውን ስለ ስራው አስቦ ተልሟልና፣ ሳይመሽበት የልቡን ይፈጽማል። የዚህ ገበሬ የጎመራ ፍሬ የሚደርሰው ደግሞ ገና ወርሀ ታህሳስ ብቅ ማለት ሲጀምር ነው።
ገበሬው በጋውን አርፎና ተዝናንቶ እግሩን ዘርግቶ አይቀመጥም። መሬቱን እንደወጉ አለስልሶ ለእርሻው ያዘጋጃል። የአምናው በረከት እንዳይጎድልበት ከልፋት ጥረቱ አይዘናጋም። በጋውን መሬቱን አርሶ፣ አለስልሶ ይቆያል። ግንቦት አልፎ ሰኔ ግም ሲል ዘሩን አዘጋጅቶ በለም መሬቱ ይበትናል።
ገበሬው ዘሩ ከመሬቱ ሲያርፍ የታህሳስ ተስፋ ይታየዋል። በዚህ ወር የሚደርሰውን ቡቃያ ከትል ከበረዶና ከአዕዋፍ እየታደገ መልካሟን ቀን ይጠብቃል። ታህሳስ ለዚህ ብርቱ አራሽ የላብ ጉልበቱ ማሳያ ነው። የጉልበቱን ድካም፣ የላቡን ወዝ ያገኝበታል።
ወርሀ ታህሳስ የብርቱዎች መታያ፤ የጎበዞች እፎይታ ነው። በዚህ ወር ገበሬው ተስፋው በእጅጉ ይበዛል። ዛሬ ላይ ቆሞ ነገውን ለማለም ታህሳስ ይሉት ወር የትናንት ጥሪቱ፣ የከርሞ አሻራው ይሆናል።
ብርቱ ገበሬ የደረሰ እህሉን በአውድማው ሊወቃ ሲያስብ እንደው በደረቁ አይደለም። የትከሻውን ድካም ለሚጋሩት ሁሉ ለምለም ምድር ካፈራው፣ የጎጆው ጸጋ ካቆየው ሲሳይ ‹‹እነሆኝ በረከት ! ›› በማለት ነው። በውቂያው ጊዜ ከበረከቱ የሚካፈሉ በቦታው ያሉቱ ብቻ አይደሉም። በአውድማው ጥግ ያለፈ፣ ያገደመ ሁሉ ሳይበላ ሳይጠጣ መሄድ አይፈቀድለትም።
በእንስራ ከተሾመው ጠላ፣ በሞሰብ ከቀረበው የጤፍ እንጀራ ሁሉም በእኩል የሚቋደስበት ጊዜ ቢኖር ወርሀ ታህሳስ ነው። ይህ ጊዜ ሰርተው የሚከብሩበት፣ በልተው የሚጠግቡበት፣ ለብሰው የሚያጌጡበት ነው። ወቅቱ የአያ በሬው ውለታ፣ የአፈር መሬቱ በረከት፣ በስነቃል የሚሞካሽበት፣ በአዝማሪ ግጥም የሚወደስበት ይሆናል።
ታህሳስ ላይ ላይ የቆመ ብርቱ ገበሬ ሁሌም የእጁ ፍሬ ይበዛል፣ የአፉ ጨዋታ ይዋዛል። የእግሮቹን አፈር አራግፎ፣ የልቡን ሀሳብ የሚያወጋው፣ የቋጠረውን የሚፈታው በዚሁ የዓመቱ አራተኛ ወር ላይ ነው። በወርሀ ታህሳስ።
የወርሀ ታህሳስ ጸጋ በብርቱ ገበሬ ማንነት ላይ ብቻ አይወሰንም። ወሩ ለእረኛውና አጎዛ ለብሶ፣ ቁራሽ ለሚለምነው የቆሎ ተማሪ ጭምር ታላቅ በረከት ነው። በታህሳስ ሁሉ ጥጋብ ነውና ከማጀቱ እንስራ እንዳሻ የሚቀዳ ከሞሰቡ እንደልብ የሚቆረስ አይጠፋም። ተሜ ታህሳስን ከሌሎች ወራት አግዝፎ የሚለይበትም ልዩ ውዳሴ አለው።
በመስከረም- ደጁ ሁሉ ለምለም።
በጥቅምት – ተቀናቀንኩት።
በህዳር- ነፍሴ ወጣች ከዳር።
በትሳስ – ውሰጤን አለው ደስደስ።
‹‹ታህሳስ›› የሚለው ስያሜ የተወሰደው ‹‹ትሳስ›› ከሚለው የግዕዝ ቃል ነው። ትርጓሜውም አሰሰ፣ ሻተ፣ ፈለገን፣ ለማመላከት መሆኑን ሊቃውንቶች ያስረዳሉ። በአንዳንድ የገጠር አካባቢዎች በታህሳስ የክረምቱ ጸጋ ከነክብርና፣ ወዘናው የሚቆይበት አጋጣሚ ይኖራል። በዚህ ወቅት መሬት እርጥበቷን አትለቅም። ከነልምላሜዋ እንዳማረባት ትቆያለች። ለዚህም ይመስላል። እንዲህ የተባለው።
ዓባይ ጉደል ብለው አለኝ በትሳስ፣
የማን ልብ ይችላል እስከዛው ድረሰ።
የክረምቱ ጭጋግና ብርድ፣ ጎርፍና ዝናብ አልፎ ታህሳስ ሲገባ ወንዝና ጅረቶች ከአፈር ከደለል ማነቆ ይወጣሉ። በጥራት ኩልል ብለውም ይወርዳሉ። አስተውሎ ላያቸው ፍሰታቸው ያምራል፣ ውበት መልካቸው ይማርካል። ይህ ወቅት ታዲያ ዓይኖች አዲስ ጸጋን የሚያዩበት፣ ተፈጥሮን በአንክሮ የሚያደንቁበት ይሆናል።
ታህሳስ ከኋላው ሕዳርን ትቶ፣ ከፊቱ ጥርን አስከትሎ የሚመጣ ነውና እሴቱ በበርካታ ጉዳዮች ይገለጣል። ይህ ወር ኮረዳውና ኮበሌው ከከንፈር ወዳጆቻቸው ጋር በዓይን ሲፈቃቀዱ፣ ሲተያዩ የሚዘልቁበት ነው። ጥር ደርሶ ጥምቀት በዓል በሚከበር ጊዜም መተጫጨት፣ መግባባቱ ወደ ትዳርና ቁምነገር ይሻገራል።
እንዲህ በሆነ ጊዜ ለሰርግ ለድግሱ የሚውለው ከታህሳስ የሚገኘው በረከት ነው። ወርሀ ታህሳስ የመልካም ገጽታዎች ውጤት ነው። ድካም ልፋት ጋብ የሚልበት፣ ተስፋና ጥጋብ የሚታይበት ነውና በርካቶች በናፍቆት ይሹታል፣ ይፈልጉታል።
አንዳንዴ ደግሞ ዳመና ታይቶ ሰማዩ ይጠቁራል። ድንገቴ ጭጋግ ፀሀይን ጋርዶ ይጨላልማል። በታህሳስ ድንገት የሚመጣ ዝናብ ከቡቃያ የደረሰን ምርት ሊያበላሽ፣ ሊያጠፋ ይችላል። ይህኔ የአራሽ ገበሬው ጭንቀት ያይላል። የዚህ ወቅት ጠብታ ዝናብ የምታደርሰው ጉዳት ቀ ላል አ ይሆንም።
አጋጣሚው እንዴትና ለምን ሆነ አይባልም። ሁኔታው ቀድሞ ሲ ጠረጠር የ ደረሰ ሰብል ፈ ጥኖ ይሰበሰባል። ዝናቡን ቀድሞ፣ ጥፋቱን የሚያሸንፍ ኃይል ይሰማራል። በዚህ ወቅት ቋንቋዎች አንድ ይሆናሉ። ልዩነቶች፣ አለመግባባቶች ይጠባሉ።
ይህ ጊዜ ለስራ የተጣመሩ እጆች ድል የሚነሱበት፣ መተባበር መግባባቱ የሚያሸንፍበት ነው። አንድነት ኃይል በሆነ ጊዜ ለውድመት የሚመጣ አጥፊ ቀድሞ ይከስማል። ለክፋት የተሰበቀ ጦር ከስሩ ይሰበራል። እውነታው ይህ ሲሆን ልፋት ድካም ሁሉ ከመሬት አይወድቅም። የቀረበ ተስፋ ወድቆ አይሰበርም። ሁሌም ቢሆን አንድነት ፍሬያማነትን ይገዛል፣ መተባበር፣ የአገር መልክን ይለውጣል።
አስተውሎ ለመረመረ አንድ የመሆን፣ የመጣመር ምስጢር በታህሳስ ወር ይመሰላል። ትርጓሜው በዚህ ሲቃኝ ማንነትን ይጠቁማል። በጽኑ ብርታት በፍሬያማነት ይገለጣል። ታህሳስ የአብሮነትና የጥንካሬ መገለጫ ነው። በዚህ ወር ልፋት ከውጤት የሚታይበት ነውና ሁሉም በመልካም፣ በበጎነት ይጠብቀዋል።
በአንድ የተቃኘ ማንነትም ልክ እንደ ወርሀ ታህሳስ ነው። በቀላሉ ንፋስ አይገባውም፣ በዋዛ ፈተና አበግረውም። እንደ ድንገቴው የታህሳስ ዝናብ ደርሶ ማንነትን የሚፈትን፣ አንድነትን፣ የሚያላላ፣ ቢኖር መፍትሄው በእጅ ነው። ችግሩ ስር ሳይሰድ፣ ተጠናክሮ ሳይፈትን ‹‹ሳይቃጠል በቅጠል›› ይሆናል።
አንድነት ኃይል ነው። ከመነጣጠል፣ ከመለያየት ይልቃል። መግባባት፣ ችግርን በጋራ ለመፍታት ድንቅ መፍትሄን ያቀርባል። አገራችን በአንድ ተባብረን ተዋደን ካደርንባት ቡቃያዋ ለሁላችን ይበቃል። ፍሬዋ ለመላው ህዝብ ይደርሳል። በረከቷን በእኩል ተካፍለን፣ ተስማምተን መብላት ካልሆነልን ግን የምድር በረከቷ እሳት እንዳየው ጭድ ነው። ለአንዳችንም ሳይሆን ለባዕዳን ጥቅምና ፍላጎት ይውላል።
ወገን እንደታህሳስ ጸጋ በአንድ ቆሞና መክሮ ኃያልነቱን ቢያሳይ ግን በረከቱን ይሰበስባል። ችግሩን ያስወግዳል። እንጀራው ከሞላው የሞሰብ ቱርፋት አይጎድልም። ከለምለም እንጀራው እጁ አይሰበሰብም። ሁሉም ከገበታው በእኩል ይቆርሳል።
አዎ! ከድካም ልፋቱ ማግስት ለቅሶ ሀዘኑ ጠፍቶ ደስታና ሳቅ ይሆናል። ከመኸሩ፣ ከሰብሉ በረከት ጀርባ የሰርጉ ከበሮ፣ የበአል እስክስታው አይጎድልም። ልክ እንደ ታህሳስ ጸጋ፤ በተስፋ እንደሚያኖረው ታላቅ ወር።
መልካምሥራ አፈወርቅ
አዲስ ዘመን እሁድ ታኅሣሥ 9 ቀን 2015 ዓ.ም