እንደምን አደራችሁ? እንደምንስ ውላችኋል? ቤተሰቡ፣ ጎረቤቱ፣ ቀዬው፣ ከብቱ፣ አገሩ በአጠቃላይ ሁሉም ሰላም አድሯል? ደግ። ብለው ሲመርቁ አንድ ከጎረቤቴ ያሉ አዛውንት ሁሌ እመለከታለሁ። በየቀኑ ጠዋት ማየቴን እንጂ ልብ ብዬ ትርጉም ሰጥቼ ለማጤን ሞክሬ አላውቅም። 21 ዓመቱን የደፈነ የልጅ ልጃቸውን ‹‹አንተ ጎረምሳ፤ ለምን ሰው ሰላም አትልም? ቆይ የሰላምን ጥቅም ስታጣው ታውቀዋለህ›› ይሉታል።
ለካስ በየአካባቢው ሰላም እንዲኖር ከጸሎት እስከ ተግባር መትጋት የሚጠበቅብን ለራሳችን ስንል ኖሯል። የሁላችንም የሠላም ምንጭ በሌሎች ሰላም መዋል ማደር ውስጥ ነው። በየትኛውም ጫፍ ሰላሙ የታወከ አካል ወይም ደግሞ በሰላም አለማደር ሲከሰት መፍትሔ መፈለግ ግድ ይላል። ዝም ብለው ከተመለከቱት ተራ የመጠበቅ ጉዳይ እንጂ ከእያንዳንዱ ሰፈር ደርሶ በሩን ማንኳኳቱ አይቀርም። ስለዚህ የጎረቤትህ፣ የሰፈርህ፣ የከተማህ፣ ብሎም የሀገርህ ሰላም መሆን ለአንተ ሕይወት ዋስትናን የሚሰጥ ነው።
‹‹ሰላም ሳይለኝ ያለፈው ‹የእንትን› ብሔር ስለሆንኩ ነው›› እያለ የተዛነፈ ሒሳብ የሚያሰላ ትውልድ በበዛበት ወቅት የእለት ተግባርን በደስታ፤ በፍቅርና በሰላም መጀመርን የሚያህል ደስታ በዋዛ እንዴት ይገኛል። አዎ፤ የመልካም አስተዳደር ችግር የገጠመው ሰው ውሎው ስኬታማ፣ ለሌሎች ቅን አሳቢ፣ ሰው አማኝ ሊሆን ይቸገራል።
እውነት ነው። በተውሶ ጭንቅላት እየታሰበ እንዴት ሰላምና አንድነት ሊገኝ ይችላል። ‹‹ያልበላንን እያከክንስ›› እስከ መቼ እንኑር ጎበዝ። ሆዱ እንጀራ፣ እንጀራ፣ ዳቦ ዳቦ ሲል ለሚያድር ሕዝብ ‹የእንብላ ፣ የእንጠጣ ፓርቲ› እንጂ የፖለቲካ ፓርቲ ሲፈለፈል ማደሩ ለራበው ሰው ምን ይፈይድለታል። ቁራሽ ሆኖ ሆዱ የከፈተበትን ጦርነት አይመክት። ተስፋ የጣለበትን ለውጥ በጥርጣሬ እንዲያይ በማድረግ አስተሳሰቡን ለመስረቅ ያለመ ይመስላል። የሌብነት ዘርፎችን ብዛት አያችሁት? ጉድ እኮ ነው። መቶ አስር ሚሊዮን ደረስን ብንለው መቶ ስምንት ሆኖ ለቅርምት መጣ ብሎ መተረቱ ይቀላል።
የሸገሮች የሰላም ነፋስ ደግሞ ከአራቱም የሀገሪቱ ጠርዞች የሚነፍስ ነው። በዚህ የተነሳ አዲስ አበቤው ለቁዘማ ተጋላጭነቱ የሰፋ ሆኗል ይባላል። ሌላው ሁሉ ቢቀር ገንዘቡን ተሰርቆ ሲቆዝም ይውላል ይላሉ ውስጥ አዋቂዎች። እንደው ከተነሳ አይቀር በ‹‹ሰርቆ አደሮችም›› ዘንድ ሪፎርም ተሰርቷል መባሉን ሰምታችኋል? ነገረ ሥራቸው ተቀይሯል ይባላል።
እንደ ድሮው ፈራተባ እያሉ ኪስ መዳበስ፣ ስልክ መመንተፍ ቀርቷል። ቦታና አሳቻ ሰዓት መርጦ በደፈጣ የአካል ጥቃት ሰንዝሮ የንብረት ዝርፊያ መፈጸም ለጊዜው ተጠናክሮ ቀጥሏል። ጥሩ ብር መያዙ በተጨባጭ ከተረጋገጠ የሰዓት ገደቡ ግድ አይሰጣቸውም። አሁን ላይ የትኛውም አካባቢ የክልል ከተሞችን ጨምሮ ስርቆት ወደ ዝርፊያ መልኩን ቀይሮ፣ ደረጃውን አሳድጎ ይከወናል።
ፅድት ያለ የመደበኛ ሥራ አካል ተደርጎ መቆጠር ጀምሯል። ‹‹እኔኮ ጥሩ ነገር ካልሆነ አልነካካም። ለሥራ ሳውዲ ዓረቢያ አለያም ዱባይ ደርሼ እመጣለሁ›› የሚሉ ዝነኛና ኩሩ ሌቦች መበራከታቸው ይነገራል። የዚህ አይነቶቹ የተለወጡ ሞዴል ሌቦች ወይስ ሞዴል ሥራ ፈጣሪዎች ምን ይባሉ ይሆን? መልሱን ለእናንተ ትቸዋለሁ። ለማንኛውም በእነሱ አጠራር ‹‹ ብቁ ሿሿ›› ይሰኛሉ።
‹‹አዲስ አበባን ማታ ከ1፡00 ጀምሮ ፈረቃው የተቀየረ እስኪመስል ድረስ ከጫፍ ጫፍ ሌቦች ያጥለቀልቋታል›› ሲል ጓደኛችን የታዘበውን አጫውቶኛል። ‹‹በተናጠላዊ ፍተሻ ሳይሆን በተደራጀ አሰሳ የኢኮኖሚያዊ ፍላጎታችንን እናሳካለን›› በሚል መሪ ቃል ንቅናቄውን የሚመራ ይመስላል።
የአንበሳው.. ተሞክሮ
በአንበሳ አውቶብስ ተሸከርካሪ ተሳፍረናል። እንደው በስም ብቻ በሩቁ ለምታውቁት በግብሩም አንበሳ አውቶብስ ድንቅ ነው። በነጻነት የማሰብና የመናገር መብት ተከብሯል። የብሔር ፖለቲካ ከባለቤቶቹ በላይ ይፈተፈታል። ምን የማይነሳ አጀንዳ አለ ሁሉም በሽበሽ ነው። ምንጭ ግን ከአንድ ወሬ በላይ አንድን ሰው መጠየቅ አይቻልም። ደጋግመው የወሬ ምንጭ የመጠየቅ አመል ካለብዎ ያስወግዱ፤ ያጣላዎታል። ምክንያቱም በዚህ ወቅት የሀገራችን ወሬዎች የሚጨለፉት ከአንድ ኩሬ ነው ከፌስቡክ።
ከአጠገቤ የተቀመጡ አንድ እናት ሲያማርሩ ሰምቼ ቀልቤን ሳቡት። ‹‹ምነው ምን ገጠመዎት እናቴ›› ብዬ ጠየቅኳቸው። እሳቸውም ‹‹መላዕክቱ መሪያችን እናት እናት ይላሉ። ከታች ያሉት ባለስልጣኖቻቸው ግን ከአይጥ እኩል ቆጥረውናል። እየውልህ ልጄ በዘመመች የቀበሌ ቤት ውስጥ ነው የምኖረው እናም የአይጥ መንጋ ማረፊያ አሳጣኝ። ፍቀዱልኝና በሸራም ቢሆን በአቅሜ ልሸብባት። በቁሜ አይጥ ቀርጥፎኝ፤ የሰው መሳለቂያ መሆኔ ነው ብዬ ብጠይቃቸው ‹አይቻልም፤ አይቻልም፤ ካልሆነዎት ያስረክቡን። ሜዳ ላይ የወደቁት ምን ይበሉ› ብለው አንጓጠው አባረሩኝ። ‹ከላይ አልጋ ከታች ቀጋ› የሆነ ነገር ገጥሞኛል›› አሉኝ።
በሞቴ ጆሯችሁን አውሱኝ ልንገራችሁ፤ እኔ በበኩሌ የአንበሳን ያህል አዛኝ፤ ለአዲስ አበቤ አላየሁም። በአራት ሽልንግ ስንት ሀገርና ወሰን አቋርጦ እንደሚሸኝ የሚያውቀው ያውቀዋል። የዚችን ምስኪን ከተማና ሀገር ቀዳዳዎች ሊሞላ ወፍ ሳይንጫጫ ጀምሮ ይባዝናል፤ ምን ይሄ ብቻ ከባዱ የኑሮ ሸክም አልቃና ብሎ በትከሻቸው ጋልቦ ላጎበጣቸው፣ ከከተማዋ ጫፍ እስከ ጫፍ ቢማስኑም ኪሳቸው አልጠረቃ ላላቸው ለፍቶ አደሮች፣ በእድሜም ሆነ በእክል አቅምና ጉልበት ሊከዳ ለሚዳዳቸው ሁሉ እናት የሆነ ሸካፊ ነው፤ አንበሳ አውቶብስ።
ታማኝም ነው። እንደው በዘመኑ ወረርሽኝ ተለክፈን አዕምሯችንም፣ አይናችንም በጎ በጎውን አላስብና አላይ ብሎናል። አንድ ቀን አንበሳ ሳይጭነው ያለፈ ተሳፋሪ የእከሌ ብሔር በመሆኔ ነው ማለቱ የማይቀር ይመስለኛል። ኧረ እንደው እንቅፋት የመታውም ‹‹እንትን በመሆኔ ነው›› ሳይል አይቀር። ወገኖቼ ገንዘባችን ብቻ ሳይሆን አስተሳሰባችንም እኮ ለስርቆት ተዳርጓል።
እያንዳንዱ ሰው ወደ ተንታኝነት መቀየሩን ሰምታችኋል? ያውም እኮ ፖለቲካ ነው የሚተረትረው። እያንዳንዷ ከአንደበታችን ጠብ የምትል ቃል ፖለቲካዊ ትርጉሟን እንጂ የተተነፈሰችበትን አውድ ማን ከቁብ ይቆጥረዋል።
አረማመዳችንም ቢሆን በጥንቃቄ ሒሳብ ተሰልቶ እግራችንን ልናንቀሳቅስና አካባቢያችንን ቃኘት ቃኘት አድርገን አዋሳኙ ሰው አልባ በሆነ ባዶ መሬት ላይ ልናሳርፍ ይገባል። አለበለዚያ በወቅቱ የፖለቲካ ተንታኞች እይታ ውስጥ መውደቃችን የማይቀር ነው። ፍዳም ያስከፍላል ፤ደግሞ ይሄ ምኑ የፖለቲከኛ ተንታኝ አይን ያርፈበታል እንዳትሉኝ።
ምክንያቱም እግር አነሳሳችን በቀኝ ከነበረና መሬቱ ላይ ስናሳርፍ ኮቴ ቢጤ ለጆሮ ከበቃ ‹‹አይዞህ፤ እኔን መታህ፤ ጎዳህ›› የምትባል አይምሰልህ። ይልቁንስ አሃ ብሔሬ እንዲህ መሆኑን አውቆ ነው። ዘሬ፣‹‹ብሔሬ…ወዘተ እንትን በመሆኔ እኮ ጠልቶኝ ነው። እንዲህ አድርጎ መርገጥ ነበር ማለቱ እኮ ነው። ንቀውናል እኮ!›› በእነዚህ ላይ እማ ዋጋ ከፍለን ትግል በማድረግ ማሳየት አለብን…ወዘተ። በማለት በፌስቡክ የፖለቲካ ምሩቃን ለትንታኔ እንደሚበቃ ሹክ ልበላችሁ። ኧረ ነገሩስ ከሹክሹክታም በላይ ሆኗል፤ ጸሐይ የሞቀው ሀቅ ከሆነ ዋል አደር ብሏል።
ረዘም ላለ ጊዜ በመካከላችን የእሾህ ችግኞች ሲተክሉ የኖሩ እኩዮች እንደነበሩ አይካድም።አሁንም ቢሆን የህዝብን ተከባብሮና ተዋድዶ የመኖር እሴት ጠላሸት በመቀባት ትርፍ የሚያፈነፍኑ መኖራቸው ይነገራል። በዚህ የተነሳ በመካከላችን አስተሳስሮን ለዘመናት የቆየውን አስተሳሰብ በከፋ ደረጃም ባይሆን ሰርቀውናል።
ገንዘብህ የተሰረቀ እለት መሳፈሪያ ሊቸግርህ ይችላል። ለድህነት፣ ለረሃብና ለጠኔ ሊዳርግህ ግን ፈጽሞ አይችልም። አስተሳሰብህ ለስርቆት የተዳረግክ ዕለት ግን ተስፋህ ጠላሸት ይቀባል፤ ማንነትህ ይበረዛል፤ ካሳደጉህ ሰዎችና ጎረቤቶችህ በእንትንነትህ ወይም በእንትንነታቸው ትራራቃለህ፤ ትለያያለህ። መለያየትን የሚወልድ ሊጨነግፍና ሊመክን የሚገባው ክፉ በሽታ የወረርሽኝ ያህል መዛመቱን የሚናገሩ በርካቶች ናቸው። ይህ ታዲያ የክፋት ጥግ አይሆንም ትላላችሁ?
ሕዝቡ ገንዘቡን ከሚሰርቁት ዘራፊዎች ባልተናነሰ አስተሳሰቡን እያምታቱ በመስረቅ ላይ የተሰማሩትን መከላከል ይኖርበታል ባይ ነኝ። ሰው ሆኖ በተፈጠረበት ብቻ መዋደድና በአንድ ኢትዮጵያዊነት ጥላ ሥር መሰባሰብ ይገባል። ለዚህ ደግሞ ዶክተሩ የተለሙት ትልም ሁነኛ መፍትሔ እንደሆነ በርካታ ዜጎች መስክረውለታል።
‹‹የአንድ ዓመት ግብራቸው ሺ ዓመት በእጃቸው የዳበሱ ያህል ፈውስ አምጥቷል›› ያሉት የእኛ ዜጎች ብቻ አይምሰሏችሁ በየዓለማቱ ጫፍ ሰው መሆን ያስተሳሰራቸው ፍጡራን ጭምር እንጂ። ለዓለም የሚበቃ አስተሳሰብ ባለቤቶች የሆንን ትልቅ ሕዝቦች በአንዳንድ ፖለቲከኞች የሻገተ አስተሳሰብ ሰብዓዊ ባህርያችንን ለቀን እና አስተሳሰባችንን ተሰርቀን ከሰው ተራ አንሰን ልንገኝ ፈጽሞ አይገባም እንላለን። ቸር እንሰንብት።
አዲስ ዘመን መጋቢት 26/2011
ሙሐመድ ሁሴን