ዓለም አሁን ከሆነችው የተለየች እንድትሆን ማድረግ የሚችል ምንድነው፤ ማንስ ነው? ሕይወት በሁሉም ዘመን ለሁሉም ሰው ስቃይ ሆና ታልፋለች ወይስ ሳቅም ትሆናለች? ከተባለ መልሱ እንደሰው የሥራና መፍትሄ አፈላላጊነት ትጋት የሚወሰን ይሆናል፡፡ ሰው ምርጫውን በራሱ የመወሰን ኃይል አለው። ይህንን ሲያደርግም በመሥራት ውስጥ ያለውን ፈተና ተጋፍጦ መፍቻ ቁልፉን ካገኘ ብቻ ነው፡፡ በነጻነትና በሕግ ሲያደርገው ብዙ ነገሮችን ይፈታል፡፡ አልቃሽ ሳይሆን ሳቂታም ይሆናል፡፡ በእርግጥ ተፈጥሮን ያማከለ ሥራ መስራትን መዘንጋት አይገባም፡፡ ምክንያቱም ሕይወት ያለ ተፈጥሮ ጣፋጭ አትሆንም፡፡
አንዳንድ ሰዎች ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች የሕይወት ብርሃንን ይጠርጋሉ፡፡ በነሱ መንገድ ሌሎች ተጉዘው ለቁም ነገር እንዲደርሱ ፈር ቀዳጅ ይሆናሉ፡፡ አይነኬ የሚመስሉ ድርጊቶችን በመፈጸምም ወይ ጉድ ያሰኛሉ፡፡ ከእነዚህ መካከል ደግሞ ለዛሬ ለ‹‹ ሕይወት ገጽታ›› አምድ እንግዳችን ያደረግናቸው ወይዘሪት አበራሽ ታደሰ አንዷ ናቸው፡፡
እንግዳችን በስፖርቱ ዘርፍ አንቱታን ያተረፉ ሴት ሲሆኑ፤ ለበርካታ ሴት ስፖርተኞችም መነቃቃትን የፈጠሩ ናቸው፡፡ ሴቶችም ከጓዳ ወደ አደባባይ እንዲወጡ ሲደርጉም ማህበረሰቡ ይዞት ከቆየው ልማዳዊ አስተሳሰብ ጋር በመጋፈጥ ነው፡፡ ሴቶች ነጻነታቸውን አውጀው ተወዳዳሪ እንዲሆኑም ብዙ ለፍተዋል፡፡ እንዴትና ምን አደረጉ ለሚለው ምላሽና ተሞክሯቸው ለብዙዎች ትምህርት ይሆነን ዘንድም እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡
ልጅነትን እንደወንድ
ተወልደው ያደጉት በቀድሞው ባሌ ክፍለ አገር ወሻ በምትባል የገጠር ቀበሌ ውስጥ ነው። ለአምስት ዓመት ያህልም በቦታው ላይ ቆይተዋል። ነገር ግን አባታቸው ዳኛ በመሆናቸው የተነሳ ከቦታ ቦታ የመዘዋወር ሁኔታ አጋጥሟቸዋል። እናም ከአምስት ዓመታቸው በኋላ የልጅነት ጊዜያቸውን ያሳለፉት በአዳባ ከተማ ነው። ይህ እድገታቸው በነጻነት የታጀበና በአባታቸው ብርታት ሰጪነት የጎለበተ ነው። ዋናው ግን በትምህርታቸው ጎበዝ መሆን እንዳለባቸው የሚያሳስብ ነበር። ጎን ለጎን ደግሞ ፍላጎታቸውን ሳይገድቡ እንዲጫወቱ ይፈቀድላቸዋል። ሴት ልጅ አታደርገውም ተብሎ የሚታሰበውን ተግባር እየከወኑ ያደጉትም ለዚህ ይመስላል።
በማህበረሰቡ ዘንድ ለሴቶች ክልክል ናቸው የሚባሉትን እንደ እግር ኳስ አይነት ጨዋታዎች የእርሳቸው ልዩ ጨዋታ ሆነው ነበርም ያለፉት። የእግር ኳስ ጨዋታን ሴት ልጅ ቀርቶ አንዳንድ ወንዶችም ይከለከላሉ። እንግዳችን ግን ከአባታቸው በተሰጣቸው ነጻነት አማካኝነት ህልማቸው አድርገውት ጭምር ቆይተውበታል። ምንም ትጥቅ ባልነበረበትና ሱሪም ሆነ ቱታ መልበስ ለወንድ ብቻ በተፈቀደበት ጊዜ ለእግራቸው ጫማ ሳያደርጉና ቀሚሳቸውን እንደ ሱሪ ቋጥረው ከወንዶች እኩል ይጫወቱ ነበር። የአጥቂነቱን ቦታ ለእርሳቸው ምቹም ነበር። ይህ ደግሞ በወንዶች ሳይቀር ያስመርጣቸዋል። የእኔ ቡድን ውስጥ ገብታ ትጫወት በሚልም ይሻሙባቸዋል።
ይህ ወጣ ያለ ባህሪያቸው ለተወሰኑ ጊዜያት በማህበረሰቡ ዘንድ ተቀባይነትን ያላስገኘላቸው እንግዳችን፤ ሴት ልጅ እንዴት እግሯን አንስታ ትጫወታለች፤ ሴት ልጅ እንዴት ከወንድ እኩል ሜዳ ትውላለችና መሰል ነገሮች በጣሙን ፈተና ሆነውባቸው ነበር። ነገር ግን በአባታቸው ብርታትና በራሳቸው ትግል ነገሩን አቁመውታል። እናታቸውም ቢሆኑ ነጻነታቸውን እንዲያውጁ ይፈቅዱላቸዋል። ነገር ግን ሙያ የሌላት ልጅም እንዲሆኑባቸው አይፈልጉምና በቤት ውስጥ ሥራ አንዳንዴ እንዲጠመዱ ያደርጓቸዋል። የዚህን ጊዜ በመካከላቸው ግጭት የሚፈጠርበት አጋጣሚ አለ። ነገር ግን ብዙም ሳይቆይ በእርቅ ይፈታል። ምክንያቱም እናት ዋነኛ አላማቸው ጫናውን አሸንፈው እንዲወጡ ነው። ለዚህም ያበረቷቸዋል። ይህ ደግሞ በራሳቸው እርግጠኛ ሆነው ምኞታቸውን እንዲኖሩት አድርጓቸዋል።
በማህበረሰቡ ዘንድ የሚገጥማቸው ፈተና የቤተሰብ ድጋፍ ባይኖር ኖሮ ይጥላቸዋል። ከህልማቸውም ያስወጣቸዋል። ነገር ግን ቤተሰብ በርቺ ሲላቸው እርሳቸውም የራሴ የሚሉትን ድርሻ ያደርጉ ነበር። አንዱና ዋነኛው በሁሉም ነገር አርአያነታቸውን ማሳየት ነው። በአካባቢው ዘንድ ሊታመኑበት የሚችሉትን ተግባር ሁሉ ያደርጋሉ። ለአብነትም መታዘዝና መላላክ አንዱ ነው። የሰፈሩ ልጅ አርአያ እንዲያደርጋቸው በዕድሜ የገፉ ሰዎችን ያከብራሉ። ለሁሉም ሰው እኩል ቦታ ይሰጣሉ። በዚያ ላይ የሴት ተብሎ የተሰጠውን ሥራ ሁሉ ከማንም በላይ ያከናውናሉ። ይህ ደግሞ ማህበረሰቡ እንዲያምናቸው አድርጓቸዋል።
ማህበረሰቡ የሚሉትን እንዲሰሙም እድል ሰጥቷቸዋል። በዚህም ሴት ልጅ ስፖርቱ ላይ ብትሳተፍ ችግር የለውም የሚለውን ሀሳብ በእያንዳንዱ ሰው አዕምሮ ውስጥ እንዲያሰርጹ ሆነዋል። ከዚያም አልፈው ተከታዮች እንዲኖራቸው አድርገዋል። ከእርሷ ጋር እንሁን በሚል ነጻነታቸውን ለሚያውጁ ሴቶች ሁሉ ህልማቸውን እንዲኖሩ በር ከፍተዋል። በባህሪም ሆነ በተግባራቸው ውጤታማና ተለማማጭ መሆናቸውም ልጆችን በስፖርቱ ዘርፍ እንዲሳተፉና የራሳቸው ጌታ እንዲሆኑ ካስቻሉ መካከል አንዷ አድርጓቸዋል። በዚህ ተግባራቸው ደግሞ በአካባቢያቸው ብቻ ሳይሆን በወረዳው ጭምር ተወዳጅና የሥራ እድል ፈጣሪ ጭምር ሆነዋል።
በሌላ በኩል እንግዳችን የመጀመሪያ ልጅ በመሆናቸውም አጋዥ መሆን ይጠበቅባቸዋልና ይህንንም በውጤታማነት የተወጡ ናቸው። ጫና የነበረባቸው ወንድምና እህቶቻቸውን ወደ ትምህርት ማምጣት ነውና ሁሉንም አሳክተዋልም። ለዚህ ስኬታቸው ደግሞ መሰረቱ እውነቱን እየተናገሩ ማደግን መልመዳቸው እንደሆነም ያስረዳሉ። ሰው ሲጣላ ማየትን አይፈልጉም። በዚህም ሁሌ መፍትሄ ፈላጊ ይሆናሉ። ይህ ደግሞ ችግርን ተጋፋጭ እንጂ ፈሪ እንዳይሆኑ አድርጓቸዋል። አስተዋይ ሴት እንዲሆኑ አስችሏቸዋልም። በአጠቃላይ ልጅነታቸው ያለፈው እንደእርሷ ሁኑ የሚባልላቸው ልጅ በመሆን ስለነበር ደስተኛ ናቸው።
ህልምን በትምህርት
ትምህርታቸው ‹‹ሀ›› ያለው በአደጉበት አካባቢ አዳባ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው። እስከ ስድስተኛ ክፍል ትምህርታቸውን ተከታትለውበታልም። ከዚያ ወደ ወደ ጎባ አመሩ። ምክንያታቸው ደግሞ የአደጉበት አካባቢ ሰባተኛና ስምንተኛ ክፍል የለም። ስለዚህም በጎባ መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሰባተኛና ስምንተኛ ክፍልን እንዲማሩ ሆኑ። ቀጠሉና ደግሞ በዚሁ ትምህርት ቤት ማለትም በጎባ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ከዘጠነኛ እስከ 12ኛ ክፍል ያለውን ትምህርት አጠናቀቁ።
በትምህርታቸው በጣም ጎበዝ በመሆናቸውም ለኮሌጅ የሚያበቃ ውጤት አምጥተው ኮተቤ መምህራን ማሰልጠኛ ኮሌጅን ተቀላቀሉ። ይሁን እንጂ እንደገቡ የፈለጉትን የትምህርት መስክ አላገኙም ነበር። ባዩሎጂ ነበር እንዲማሩ የሆኑት። ነገር ግን ከልጅነታቸው ጀምሮ የኖሩለት ሕልም ይህንን እንዲቀበሉት አላደረጋቸውም። ስለዚህም ዳግመኛ ለትምህርት መስክ ምርጫ የሚያገለግለውን ፈተና ወስደው የልጅነት ህልማቸው የሆነውን ስፖርት ማለትም በወቅቱ ጤናና የሰውነት ማጎልመሻ ትምህርትን እንዲገቡበትና እንዲመረቁበት ሆነዋል።
ትምህርት የሁሉም ነገር መሰረት እንደሆነ የሚያምኑት ባለታሪካችን፤ ከዓመታት የሥራ ላይ ቆይታ በኋላ በዘርፉ የተሻለ እውቀት ኖሯቸው መምራት ይችሉ ዘንድ ትምህርታቸውን ቀጥለዋል። ይህም ማኔጅመንት ሲሆን፤ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብተው የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን የያዙበት ነው። በመቀጠል የተማሩት ትምህርት የስፖርት አስተዳደር የሚል ሲሆን፤ በግሪክ የተከታተሉት ነው። ስፖርትን የመሩና ባለስልጣን የሆኑ ሰዎች ከኢትዮጵያ ሁለት ሲመረጡ እርሳቸው አንዷ በመሆን የሄዱበት ነበር። በትምህርቱ ዲፕሎማ ማግኘት ችለዋልም።
ሌላው ጀርመን አገር በመሄድ የተማሩት ትምህርት ሲሆን፤ በስፖርት ፔዳጎጂ ትምህርት መስክ በዲፕሎማ የተመረቁበት ነው። በተጨማሪም ስፖርትን የተመለከቱ በርካታ ስልጠናዎችን በአገር ውስጥና ከአገር ውጭም ወስደዋል። ለአብነት በአትሌቲክስ ፤ በእግር ኳስ፤ በእጅ ኳስ፤ ጠረጴዛ ቴኒስና ግራውንድ ቴኒስ ዋና ዋናዎቹ ናቸው። ከዚህ በኋላም ይህ ነገራቸው እንደሚቀጥል ያነሳሉ። ምክንያቱም ልምድ ትምህርት እየሆነ ቢቀጥልም ያለ ትምህርት መምራትም፤ መሥራትም ፤ ስፖርተኛ መሆንም አይቻልም ብለው ያምናሉ።
ባለታሪክ ያደረገው ሥራ
ሥራቸውን አሀዱ ያሉት በዚያው በትውልድ ቀያቸው ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው። በጎባ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የስፖርት መምህር በመሆን ለሦስት ዓመታት ቆይተዋልም። የልጅነት ህልማቸው ሴቶችን በስፖርት ልማት ከፍተኛ ደረጃ ማድረስ የነበረውን ተግባራዊ ማድረግም የጀመሩት በዚሁ ትምህርት ቤት ነው። ተግባሩን ሲከውኑም ከሴቶቹ ጋር አብረው ሆነው በመወዳደር ጭምር ነበር። ቀበሌ ድረስ በመውረድም ደስተኛ ሆነው አጋርነታቸውን ያሳዩ ነበር።
ጠንካራ ሥራዎቻቸው ወደ እድገት ጎዳና ያሻገሯቸው መምህርቷ፤ ወደ ኮሌጅ ከፍ በማለት በሮቤ መምህራን ማሰልጠኛ የስፖርት መምህርት ሆነውም ሰፊውን የሥራ ጊዜያቸውን አሳልፈዋል። እንደውም 10 ዓመታት እንደቆዩበትም ይናገራሉ። ይህ ደግሞ በተለይም ቡድን ማቋቋም ላይ ጠንከር ያለ ሥራ እንዲያከናውኑና ስማቸውን እንዲተክሉ የሆኑበት ተግባርም ነበር። በእርግጥ ይህ ስኬታቸው ዝም ብሎ የመጣና ብቻቸውን ያደረጉት እንዳልሆነ ያስረዳሉ። ብዙ ድጋፍ አድራጊ አካላት አግዘዋቸው ነው የተሳካላቸው። ይሁን እንጂ የሀሳቡ ጠንሳሽ እርሳቸው ናቸው። ሥራቸውን ሲሰሩ ብቻቸውን ሳይሆን መሳተፍ ያለባቸውን አካላት ያካትታሉ። ቅድሚያ የሚሰጡት ደግሞ ለማህበረሰቡ ነው። የከተማ አስተዳደሩንና የዘርፍ አመራሮችን አክለውበት ፍላጎታቸው ግቡን እንዲመታ ያደርጋሉ።
ከሁሉም ጋር ተግባብተው ነገሮችን ለመፍታት የሚጥሩ በመሆናቸውም የጀመሩት ነገር ተቋርጦባቸው አያውቅም። የሴቶች የስፖርት ቡድኑ ጠንካራ ሆኖ የቀጠለውም ለዚህ ነው። እንደውም በስፖርቱ ዘርፍ ዘርፈ ብዙ ለውጦች ማስመዝገብ የቻሉት ከዚህ አንጻር እንደሆነ ይነገርላቸዋል። የእርሳቸው የሥራ ውጤታማነት ዛሬ ሳይሆን ትናንት በነበሩ ጋዜጦቻችን ጭምር የሰፈረም ነው። በዋናነት በቅርብ ካገኘነው መረጃ ብንነሳ ከበደ በየነ በ‹‹ዛሬይቱ ኢትዮጵያ›› ይዞት በወጣው አምዱ ላይ የመጀመሪያዋና ብቸኛዋ ኢትዮጵያዊት ሴት የስፖርት ባለስልጣን በሚል ያስቀመጣቸው አንዱ ማሳያ ነው።
ሴት ሆኖ ኮሚሽነር የሚባል ነገር ባልነበረበት ወቅት እርሳቸው መስፈርቱን አሟልተው በዞን ደረጃ ስልጣን የያዙ የመጀመሪያዋ ሴት ኮሚሽነርም እንደነበሩ ዘገባው ያስረዳል።
ኮሚሽነር የነበሩበት ቦታ የባሌ ዞን ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነርነት ሲሆን፤ 13 ዓመታትን በሥራው ላይ ያሳለፉበት ነው። ይህ ሥራ መነቃቃት የፈጠረላቸውም ስለነበር የተሰጣቸውን ኃላፊነት በመጠቀም የስፖርት ዘርፉ የተሻለ አቅም እንዲኖረው ለፍተዋል። ተሳክቶላቸዋልም።
ቀጣይ የሥራ ጉዟቸው የሚያደርሰን አሁንም በኦሮሚያ ክልል የስፖርት ኮሚሽን ውስጥ የክልሉ የውድድር ስፖርቶችን ኃላፊ በመሆን የሰሩበት ነው። የተለያዩ ፌደሬሽኖችን በኃላፊነት መርተዋል። ለአብነትም ጠረጴዛ ቴኒስ፤ ግራውንድ ቴኒስ የሚሉት በዋናነት ይጠቀሳሉ። ጎን ለጎን ደግሞ ክልሉን በመወከል በርከት ያሉ ኃላፊነቶች ላይ ሰርተዋል። ለምሳሌ፡-የኦሮሚያ ሴት ስፖርት የውድድር ኃላፊ ሆነው ለሁለት ዓመታት የሰሩበት አንዱ ነበር።
ስፖርት ኢንቨስትመንት ላይ በኃላፊነት ሠርተዋል። በተጨማሪም ለመጀመሪያ ጊዜ የኢትዮጵያ ሴት ስፖርት ማህበር ሲቋቋም ምክትል ፕሬዝዳንት በመሆን ለረጅም ዓመታት አገልግለዋል። አሁን ደግሞ የራሳቸውን ሥራ ለመሥራት እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ። ትልቁ ትኩረታቸውም ሴቶች ሲሆኑ፤ ሴቶች በሁሉም ዘርፍ ብቃት ያላቸው እንዲሆኑ ይፈልጋሉና እዚያ ላይም የተሻለ ሥራ ለመስራት እቅድ እንዳላቸው ነግረውናል። ሥራቸውን አሁን ላይ ይፋ ባያደርጉትም ትልቅ ለውጥ እንደሚያመጣ ግን ያምናሉ።
ስፖርትን ከሰፈር እስከ አገር
ያለጫማና ያለ ቱታ በቀሚሳቸው እየተጫወቱ ነበር ከጊዜ ወደጊዜ በሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎች ከሰፈር ወደ ዞን ከፍ ብለው ም በ ክልል ውድድሮችን ማድረግ የጀመሩት። በውድድሩ ሁለት ስፖርታዊ ጨዋታዎችን በዋናነት ይወክላሉ። የእጅ ኳስና እግር ኳስን። ይህንን ሲያደርጉ ደግሞ ከሰበሰቧቸውና ካሰለጠኗቸው ሴት ተጨዋቾች ጋር በመሆን ነው። እናም በዞን ደረጃ ቁጥር የሌለው ውድድር ያደረጉ ሲሆን፤ ቡድናቸው ሁልጊዜ አሸናፊ ነበርም። ክልላቸውን ወክለው አዲስ አበባ ላይ ሲወዳደሩም እንዲሁ ሽንፈታቸውን አያስታውሱትም። እንደውም እንደ ክልል ሲጫወቱ ብዙ ጊዜ ኦሮሚያን አሸናፊ አድርገው ይመለሳሉ እንጂ በእርሳቸው መሪነት የተካሄደ ግጥሚያም ሽንፈት አጋጥሞት አያውቅም። ለዚህ ደግሞ በተለያየ ጊዜ ሽልማት እንደተበረከተላቸውም ያነሳሉ። ከሁሉም በላይ ግን በወረዳና ቀበሌ ብቻ ሳይሆን በክልሉም የሴት ስፖርተኞች ሚና ከፍ ያለ ቦታ ማግኘቱ ያስደስታቸዋል። ከሁሉም ሽልማቴ የሚልቀው ይህ ነውም ይላሉ።
እርሳቸው በነበሩበት ወቅት አብዝቶ ስፖርት መሥራት በተለይም ለሴቶች አይመከርም ይባላል። እንደምክንያትነት የሚጠቀሰው ደግሞ ጡትና እግር ያማል ተብሎ ነው። ነገር ግን እርሳቸው ታመው ስለማያውቁ ህልማቸውን ለመኖር ሁልጊዜ ወደፊት ይጓዛሉ። በዚህም ከሰፈር አንስተው እስከ ኮሌጅና ክልል ከዚያም አልፈው አገርን በመወከል በተለያዩ ስፖርታዊ ዘርፎች ላይ ተወዳድረው አሸንፈዋል።
ሴትነትና ስፖርት
ሴትና ስፖርትን ከማህበረሰቡ አኳያ ስናነሳው እጅግ ፈታኝና ውስብስብ ነው። በተለያዩ የአገሪቱ ክፍል ያሉ ሴቶችን ብቃትና እውቀት ማውጣት ያልተቻለውም ለዚህም ነው። ምክንያቱም ሴት ልጅ ስፖርትን መለማመድ የምትችለው ከልጅነቷ ጀምሮ ቢሆንም እውቅና ተሰጥቷት በልምምድና በእውቀት እንድትመራው አይደረግም። ለዚህም ማሳያው በተለይም በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ከሚኖርባት የሥራ ጫና ባለፈ ስፖርት የሚባል ነገር እንዳታስብ ነው የምትደረገው። እናት አባት ብቻ ሳይሆን ጎረቤትም ጭምር ይህንን ተሳትፎዋን ውድቅ ያደርግባታል። እንደውም ‹‹ሴት ወደማጀት ወንድ ወደችሎት›› የሚለው አስተሳሰብ በስፋት ይተገበራል። ለዚህ ማሳያው ደግሞ ልምምድና ነጻ መሆን እንዳትችል ይህንን ስሪ፤ ይህንን ጨርሺ፤ ይህንን …. እየተባለች ከቤት እንዳትወጣ ትደረጋለች። የጨዋታ ጊዜ እንኳን አይኖራትም።
ቤተሰብ ፈቅዶላት ብትወጣ እንኳን ጎረቤቱ ስም አውጪ ይሆናል። የእገሌ ልጅ አይደለች፤ እንደወንድ እግሯን የምታነሳው ልጅ፤ ወንዳወንዷ…›› እየተባለ ቤተሰቡ በነገር ይሸነቁጠዋል። በዚህ ጊዜ ቤተሰብ ልጁ ዘና እንድትልና በነጻነት የፈለገችውን እንድታደርግለት ቢፈልግ እንኳን ከማህበረሰቡ ባህልና ወግ ላለማፈንገጥ ሲል ገደብ ያበጃል። ያን ጊዜ ከህልሟ የምትወጣ ብዙ ሴት ትኖራለች። ህልሟን ሳይሆን የእነርሱን ምኞት እንድትፈጽምም ትገደዳለች። በዚህ ውስጥ ግን አንድ ነገር ኃይል አለው። የቤተሰብ ፍላጎት ከማህበረሰቡ አጎል ባህል ጎልቶ መውጣት። ለልጅ እድሉን መስጠትና ፍላጎቷን እንድትኖረው ማድረግ። የማህበረሰቡን መልካም ሕግና ደንብ አክባሪ ሆና እንድትቀጥል ማድረግ ነገር ግን ህልሟን አለመገደብ ሲቻል ሁሉ ነገር በአሸናፊነት ይጠናቀቃል።
ሴቷ የተሰጣትን እድል በአርአያነት ከተጠቀመቺው እርሷን ብቻ ሳይሆን ለሌሎችንም ይዛ መውጣት ትችላለች። ምክንያቱም ማህበረሰቡ ከእርሷ በላይ የሚያምነው ሰው አይኖርም። እርሳቸውም ያደረኩት ይህንን ነውና ሴቶች እንዲሁም ወላጆች ቢጠቀሙበት ይላሉ።
ስፖርት አሁን ላይ ለሴቶች መልካም እድሎችን እየሰጠ ቢመጣም በገጠሩ አካባቢ ግን አሁንም ብዙ ጫናዎች አሉበት። አንዱ እውቅና ባይሰጠውም ስፖርተኛ መሆናቸውን አለመቀበሉ ነው። ለአብነት ሴቶች እንጨት ለመስበር ዳገትና ቁልቁለቱን ይወጣሉ ይወርዳሉም። ማልደው ተነስተው አምሽተው ይተኛሉም። ይህ ሁሉ ጊዜ ታዲያ በሥራ የሚቆዩበት ነው። ሥራ ሲሰራ ደግሞ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች ይኖራሉ። እናም ከወንዱ ባልተናነሰ ሁኔታ ስፖርቱን እነርሱም ይሳተፉበታል። ሆኖም ነጻ ተደርገው የሚተገብሩት አይደለም። በዚህም በእውቀት አይመራም፤ አይደገፍምም። ስለዚህ ሥራ ብቻ ሆኖ ይቀራል። እና ምን ይሁን ከተባለ አንድ ነገር ሊደረግበት ይገባል። በእውቅናና በእውቀት እንዲመራ ማድረግ ላይ መሰራት ይኖርበታል።
ሌላው እንቅስቃሴው ለጤናዋና ለአካሏ ያለውን ጥቅም ተረድታ የምታደርገው እንዲሆንም ግንዛቤ ማስጨበጥ ያስፈልገዋል። ይህ ከሆነ ሴቶች ከሰፈር አልፈው አገራዊ አቅም እንዲኖራቸው ይሆናሉ። በሴቶች በኩል ስፖርታዊ ልማቱ ይፋጠናል። ለዚህ ደግሞ ቅድሚያ መሰጠት ያለበት ማህበረሰቡን ማስተማር ነው። ሴቶችን በትንሹም ቢሆን በርቱ ማለት ይገባል ይላሉም። በዚህ ዓመት ከነበሩት ውጤቶች በርካታውን ድል ያስመዘገቡት ሴቶች ናቸው። እናም ይህንን እድል በስፋት ለመጠቀም ደግሞ እነዚህን ተግባራት አጠናክሮ መቀጠል ከምንም በላይ አስፈላጊ ነው። የተገኙ ውጤቶችን ይዞ ታችኛው ላይ መስራትም ያስፈልጋል። ምክንያቱም ይህ ሥራ ያልተወራላቸውን ሴቶች ያመጣል። እንዲወጡም ያደርጋቸዋል።
የአገር አበርክቶ
በእርሳቸው ምክንያት ሴት ስፖርተኞች መፈጠራቸው እጅጉን የሚያስደስታቸውና ውጤታማ ሆኜበታለሁ የሚሉት የመጀመሪያው አበርክቷቸው ነው። መዳወላቦ ወይም ባሌ ስቴዲዬምን በሕዝብ ተሳትፎ ማሰራታቸውም እንዲሁ ከሚጠሩባቸውና ከሚነሱበት አበርክቶ ትልቁን ድርሻ የሚይዘው ነው። አልቆጠሯቸውም እንጂ እንደ ዶዶላ ፤ አዳባ ላይ ያሉት በርካታ ትንንሽ የሚባሉ የስፖርት ጥርጊያዎች እርሳቸውን አጉልተው የሚያስጠሯቸው መልካም ሥራዎቻቸው ናቸው።
አብዛኛውን ሥራ ሲከውኑ ማልደው እየወጡ ምሽት ላይ ወደቤታቸው በመመለስ ስለነበር ማን እንደርሳቸው ለአገሩ ሰራ ይባልላቸዋልም። እንደውም ከዚህ ትጋታቸው ጋር ተያይዞ ወደ ስታዲዬሙ የሚወስደው መንገድ ጭምር በስማቸው ተሰይሞላቸዋል ማለትም ‹‹የአበራሽ ሜዳ›› እየተባለም ይጠራል። በእርግጥ የስቴዲዬሙ ጉዳይ ሲነሳ ሦስት ሰዎችን በአብነት ያነሳሉ። እነዚህም ዳኛቸው ሽፈራው፤ ጀማል ኡስማንና ያሃያ አማን ሲሆኑ፤ ሁልጊዜ ያመሰግኗቸዋል። ስታዲዬሙን አገራዊ ጨዋታዎች እንዲያካሂድ ያስቻልኩት እኔ ብቻ ሳልሆን በቀዳሚነት ሕዝቡና እነዚህ ሰዎች ናቸውም ይላሉ።
የእንግዳችን ሌላው አበርክቶ እጅግ የሚደንቀውንና በአገር ደረጃ የማይታሰበውን የሮቤ መምህራን ማሰልጠኛ የግራውንድ ቴነስ ቦታ ማሰራታቸው ነው። በዞኑ ያሉ እስቲዲዬሞችንም ቢሆን ማሻሻያ እንዲደረግላቸውና እንዲከበሩ ያስቻሉ ናቸው። ሌላው ሴቶችን በሚጋብዝ የትኛውም ሥራና ስብሰባ ላይ በመሳተፍ ተሞክሯቸውን ማካፈላቸው ሲሆን፤ ለዚህ በተደጋጋሚ ስትጋብዛቸው የነበረቺውን የኢትዮጵያ ሴት ስፖርት ማህበርን ኃላፊ ስንታየሁ ፍቅረዮሐንስ ያመሰግኗታል። ምክንያቱም የእርሳቸው ተሞክሮ ብዙዎችን አነሳሺ እንደሆነ ያውቃሉና ነው።
በማንኛውም አገራዊ ጉዳይ ላይ ማለትም የሴቶችን ንቃተ ህሊና በመጨመር ላይ ስልጠናዎችን መስጠትም አንዱ አበርክቷቸው ነው። እንደውም በብሪቲሽ ካውንስል አዘጋጅነት የሚከናወኑ በርካታ ስልጠናዎችን በየአገሩ እየተዘዋወሩ መስጠታቸው አንዱ ማሳያ እንደነበር ያስታውሳሉ። በተጨማሪም ሴቶች ወደ ስፖርቱ ዓለም እንዲቀላቀሉ በወቅቱ የነበሩ አንጋፋ የስፖርት ጋዜጠኞችንና ሚዲያዎችን በመያዝ ማህበረሰቡ ለስፖርት ያለውን አቅም እንዲያጎለብትና ስለ ስፖርት ምንነት ግንዛቤ እንዲጨብጥ ማድረጋቸውም ከአበርክቷቸው መካከል የሚጠቀስ ነው።
የስፖርት አደረጃጀትን ከዞን እስከ ቀበሌ ድረስ በመዘርጋትም ትልቅ ሥራ የሰሩ ናቸው። ክልል ሳይቀር ተሞክሯቸውን ወስዶ እንደተጠቀመበትም ይነሳል። አደረጃጀቱን ሲፈጥሩም ቅድሚያ የሚሰጡት ለባለሙያ ነው። ይህ ካልተሳካለቸውም ተጠያቂ አካል በማስቀመጥ ተደራጅተውና ለስፖርቱ ልዩ ትኩረት ሰጥተው እንዲሰሩ ያደርጋሉ። ይህ ደግሞ በብዙዎች ዘንድ ያስመሰገናቸውና ተወዳጅነትን ያተረፉበት ነው።
ሕዝብን፣ አመራርን ፤ ባለሙያንና ልዩ ፍላጎት ያላቸውን ልጆች ይዘው በመስራታቸው ብዙ ችግሮችን መፍታት የቻሉ መሪም የነበሩት ባለታሪካችን፤ የወረዳና የቀበሌ እንዲሁም የዞን አመራሮች ሽጉጣቸውን አስቀምጠው ጭምር ቡድን ውስጥ በመካተት እንዲጫወቱ አድርገዋል። የገንዘብና የሰው ኃይል ችግር ሳይገጥማቸው የሚፈልጉትን ነገር አድርገው ክልሉን በስፖርቱ ዘርፍ የተሻለ አቅም እንዲኖረውም አስችለዋል። በተለይ የአምስቱ አጎራባች ክልሎች የስፖርት እንቅስቃሴ ላይ የሰሩት ሥራ ዛሬ ድረስ የሚያስመሰግናቸው እንደነበርም ያነሳሉ።
መልዕክት
ሴቶች ከማጀት ወደ አደባባይ ሊወጡ ይገባል። ሴቶች በተሳተፉበት ሜዳ ሁሉ ውጤታማ ስለሆኑ ጊዜያቸውንም ማጥፋት ያለባቸው በሕይወት ጥሪያቸው ላይ ነው። ህልማቸውን ለመኖር ሲንደረደሩ በርካታ ውጣውረድ፤ እሾህና አሜኬላ ሊያጋጥማቸው ይችላል። ሆኖም በጊዚያዊ ችግሮች ሳይበገሩ ህልማቸውን ለመኖር ሌት ተቀን መስራት ይኖርባቸዋል።
በዚህ ዓመት የመጣው ስፖርታዊ ድል በለቅሶና በሀዘን ውስጥ የነበርነውን ሕዝቦች ያሳቀ ነው። አንድ ስንሆን ይህንን ድል ብቻ ሳይሆን ጠላትን ጭምር እንደምናሳፍር ያየንበትም ነው። ምክንያቱም በሁሉም ክልሎች የተወከሉ አሸናፊዎች ስለነበሩን እኩል ደስታችን ጮኸዋል። ተስፋችንም ለምልሟል። በፍቅር እንባም ተራጭተናል። በእርግጥ ስፖርት ሲጀምር የአንድ ብሔር፤ የአንድ አገርና የአንድ ሃይማኖት ደስታ ብቻ አይደለም። የሁሉም ሰው የጋራ ደስታ ነው። የሁሉም ሰው ስብራት መጠገኛና ሰላምን ማረጋገጫ ነው። ያዘነውን የሚያረጋጋ፤ የተጎዳውን ቀና የሚያደርግ ነውም። ስለሆነም ይህንን ባህሪውን አሸንፈው በመጡት አትሌቶች ከፍ ማድረግ ይገባል ሲሉም ይመክራሉ። በከተማ ብቻ ሳይሆን በየክልሉ እየዞሩ ሰላምን መስበኪያ ማድረግም እንደሚገባ ይገልጻሉ።
አገራችን በተራ አሉባልታ እየተዋከበች ነው። ይህ ግን አይደለም ማሻገር አያራምደንም። እናም ሰው ሆኖ ሁሉ ነገሩ ይመሳሰላል ሊባል አይችልምና ልዩነቶችንን ተቀብለን አንድነታችንን አጉልተን ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ መሥራት ከሁላችንም ይጠበቃል። ለዚህ ደግሞ ሁሉም አንድ ነገር ላይ ኢላማውን ማድረግ ይኖርበታል። ኢትዮጵያን ከፍ ማድረግ ላይ። ለዚህም ኃይሉን አንድነት ላይ ማሰባሰብ ይኖርበታል። አንድነት ጠላትን ያኮሰምናል፤ ጥንካሬን ይጨምራል፤ ወዳጅነትን ያሰፋል፤ እድገትን ያጎናጽፋል። ስለሆነም ኢላማችን ከአላማችን ጋር አዛምደን ለአገራችን ሁላችንም እንስራ በማለት የማሳረጊያ መልእክታቸውን ያስተላልፋሉ። እኛም መልእክታቸውን እውን እናድርገው በማለት ለዛሬ አበቃን። ሰላም!!
ጽጌረዳ ጫንያለው
አዲስ ዘመን ነሐሴ 22 /2014