ወደ ጸባኦት ያስተጋበው የደም ጩኸት፤
የአገሬ የኤሎሄ የጣር ጩኸት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየበረታ ሄዶ የጸባኦትን ደጃፍ ወደ ማስከፈት ደረጃ ላይ የደረሰበት ወቅት ይመስላል። ምክንያቱ ደግሞ ግልጽ ነው። በደም የሰከሩ፣ ለግፍ የበረቱ ጨካኝ «ሰብአዊ አውሬዎች» ከጥቂት ዓመታት ወዲህ በተደጋጋሚ ጊዜያት ከጫካ እየወጡ ንጹሐንን በመጨፍጨፍ ምድሪቱን በደም አበላ ማጨቅየትን ሥራዬ ብለው ተያይዘውታል።
በዚህ ምክንያትም አገር «ላማሰበቅታኒ!» እያለች እጆቿን ዘርግታ ወደ ፈጣሪ ስትቃትት ሕዝብም አብሮ ምድሪቱን በማላቀስ እምባችን የጋራ ቀለባችን ከሆነ ሰነባብቷል። በአንጻሩ «አውሬዎቹ ግፈኞች» በደም በጨቀየው እግርና እጃቸው ጮቤ እየረገጡና በእኩይ ተግባራቸው የወገኖቻችንን በድን እንደ ግዳይ በመጣል የደስታ «ርችት» በመተኮስ ያቅራራሉ፤ እያስተኮሱም ያሽካካሉ።
ጋላቢዎቹና ተጋላቢ አጋሰሶቹ «የደም አፍሳሽነት የግፍ ትራዠዲያቸውን ጉግስ» እየፈጸሙ ያሉት እንኳንስ ጥልፍልፉን ውል አልባ የአገራችንን የፖለቲካ እንካሰላንትያ ሊረዱት ቀርቶ «ፖለቲካ» የሚለውን ቃል እንኳን ሰምተው በማያውቁ ንጹሐን ዜጎች ላይ መሆኑ በራሱ ሰዋዊ ባህርያቸው ወደ አውሬነት ስለመለወጡ ጥሩ ማሳያ ነው። የግፋቸው ሰለባ የሆኑ ሕፃናትና እህቶች፣ አባቶችና እናቶች በደደረ መዳፍ የዕለት እንጀራቸውን ለማሸነፍ ደፋ ቀና የሚሉት ሕይወትን ያሸነፉ መስሏቸው እንጂ ሌላ ተልዕኮም ሆነ ዓላማ አልነበራቸውም።
በኢትዮጵያ ምድር የሰኔ ወር በተለየ ሁኔታ እየተጠበቀ፤ በተቀሩት ወራትም እንዲሁ እየተደጋገመ በመፈጸም ላይ ያለው በአሸባሪው ሕወሓትና በሸኔ ጥምር ሰይጣናዊ ተልዕኮ የሚመራው እልቂትና ማፈናቀል ምናልባትም ከጀርመን ናዚና ከኢጣሊያው የፋሽስት ጭፍጨፋዎች በደረጃው ከፍ ባለ የታሪክ ዐይን ተሰንዶ ከትውልድ ትውልድ ሲተላለፍ እንደሚኖር የሚያጠራጥር አይደለም።
ቀደም ባሉት ዓመታት በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች፣ በቀደም በጋምቤለ ክልል ውስጥ ትናንት ሰኔ 11 ቀን 2014 ዓ.ም ደግሞ በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ኦሮሚያ በጊምቢ የወረዳ ቀበሌዎች ውስጥ (ጉቱ፣ ጨቆርሳ፣ ስልሳው፣ በገኔ፣ እና ሌሎች መንደሮች ውስጥ) የተፈጸመው አሰቃቂ ፍጅት ከናዚ የሆሎኮስት ጭፍጨፋ በምን ሊለይ እንደሚችል ማሰቡ በራሱ አቅም ይፈትናል። «ሰብዓዊ» ነን ይበሉ እንጂ «ሲፊኒክሳዊ» (ግማሽ ሰው ግማሽ አጋንንት እንዲል የቅዱስ መጽሐፉ ታሪክ) አፍ ባልፈቱ ንጹሐን ሕፃናት ላይ አፈሙዛቸውን አዙረው ሲፈጇቸው ምን ብለው ተማጽነዋቸው ነበር?
እናቶችና እህቶች ተንበርክከው ሲለምኗቸውስ በአውሬያዊ መንፈሳቸው ምን ተሰምቷቸው ይሆን? እነዚያ ምስኪን የመከራ ገፈት ቀማሾች ላባቸው የፈሰሰበት ንብረታቸው በአንድ ቅጽበት የእሳት እራት ሆኖ ሲመለከቱስ ስሜታቸውን እንዴትና በምን ገልጸው ይሆን? እንኳንስ ተጎጂዎቹ ዘንድ ተገኝቶ በአካል ለማጣራት ቀርቶ በርቀት ሆኖ ለመገመት እንኳን ይከብዳል።
የጫካው አውሬ የሸኔ አሸባሪ ቡድን ዳዴ በሚልበት ዕድሜ ላይ ቆሞ ሲውተረተር «ወፌ ቆመች» ባይባል ኖሮ፣ ድክ ድክ እያለ መራመድ ሲጀምርም «የወተት ጥርሱን እንዳይነቅል» በአጭሩ ቢቀጭ ኖሮ ይህ የዛሬው መከራችን ገዝፎ እንደ ወስከንባይ ባልተደፋብን ነበር።
በበደልና በግፍ የወረዛ የሕዝብ ሙሾ በእንባ፣ በግጥምና በዜማ ተለውሶ መፍሰሱ የተለመደ የአገር ወግ መሆኑ በሚገባ ይታወቃል። ይህ ጸሐፊም «ምን ነበረበት ይህ እኩይ ‹ሸኔ ይሉት› ቡድን በእንጭጭ ዕድሜው ላይ በነበረበት ወቅት ቀድሞ ቢቀጭ ኖሮ!?» የሚለውን ቁጭቱን ሊወክሉለት የሚችሉ ጥቂት ስንኞችን ከወዳጁ አንድ ግጥም ተውሶ እንዲህ ጠቅሶታል።
«ሀ» ሲባል «ሀ» ቢባል፤ ጅምሩ ቀድሞ ቢዳሰስ፣
ቀድሞ! ቀድሞ! ቢቀነጠስ፤
መፈልፈያው ቢደፈን፣ ሥሩ ማለዳ ቢበጠስ፣
የውስጥ ውስጡ የላይ ላዩ፣ ቃርሚያው በወጉ ቢነሣ፣
ባልኖረ ባልነበረ – ነበር፣ የዛሬው «ክምር» አበሣ!
የችግሩ «ችግር» ይህ ነው፤ ሽምቅታው ነው የበደለን፣
«የሣመን» ነው የነከሰን፤ የሣቀ ነው የገደለን።
ያለፈው ቀድሞ አለፈ፤ ዛሬ ለነገ እንዲነቀስ፣
ድራ-ድሩን ነው መበጠስ፣ «አስኳሉን» ነው መፈርከስ።
እንጂማ…ቅርንጫፉማ ጭራሮ ነው፣
ግንዱ ሲቆረጥ የሚረግፍ።
ግንዱም ቢሆን ግንዲላ ነው፣ ሥሩ ሲነቀል የሚነጥፍ።
«አሾክሻኪው» አፉ ሲዘጋ፤ «ወሻቂው» እጁ ሲቆረጥ፣
እርቃኑን ይቀራል የጥሻው፤ የጀግናን ክንድ ሲቀምስ።
(ምንጭ፡- «አንድ ቀን» – ሻለቃ ክፍሌ አቦቸር፤ 1982)
በመከራ የሚገረፈው ገላ ሰንበሩ ቶሎ ባይጠግግም፤ የመከራ ቀን ጀንበር አጭር በመሆኑ አገርና ሕዝብ ሊጽናና፤ ከእንግዲህ በኋላም መንግሥት እንደ ካሁን ቀደም ሳይዘናጋ ሕግ የማስከበር ሥራውን አጠንክሮና አምርሮ ሊሠራ ይገባል።
ዛሬ መከራ ወድቆባቸው በመቶዎች በሚቀጠር አሀዝ በጭካኔ የተጨፈጨፉት ኢትዮጵያውያን በምዕራብ ኦሮሚያ እግራቸውን የተከሉት ከ1977 – 1978 ዓ.ም በተከሰተው ድርቅ ምክንያት ከአንዱ የአገራቸው ክፍል ወደ ሌላው የአገራቸው ክፍል በሠፈራ ፕሮግራም የተሰባሰቡ እንጂ ከባእድ ምድር የፈለሱ «መጤዎች» አልነበሩም። ጨፍጫፊዎቹ ህሊና ቢፈጥርባቸው ኖሮ እንኳንስ ሕይወታቸውን ሊቀጥፉ ቀርቶ በክፉ ዐይን ባላዩቸው ነበር። ስለምን? የጅማሮው ታሪክ እንዲህ ይታወሳል።
ያን መሰሉ የሠፈራ ፕሮግራም ሲከናወን በከፍተኛ መንግሥታዊ ኃላፊነት ላይ የነበሩትና እቅዱን በማስፈጸሙም ረገድ ትልቅ ድርሻ የነበራቸው ጎምቱ ባለሥልጣን በቅርቡ ባሳተሙት መጽሐፍ ውስጥ የወለጋ ሕዝብ ወገኔ ብለው የሄዱትን ወንድም እህቶቹን እንዴት ይቀበላቸው እንደነበር የገለጹበት ሁኔታ በእውነቱ እጅግ ልብን የሚነካ ነው።
«በመኖርና ባለመኖር መካከል የሚገኙትን ወገኖቻችንን የመርዳት የዜግነት ግዴታ አለብን በማለት ነበር የወለጋ ገበሬዎች ፕሮግራሙን ከልባቸው የተቀበሉትና የደገፉት። …የወለጋ ገበሬ ከዳር ዳር ተንቀሳቅሶ ለሰፋሪዎች እነዚያን የመሰሉ ሁላችንም ያደነቅናቸውና የኮራንባቸውን መንደሮች መስርቶ ለሰፋሪዎቹ ቤት ብቻም ሳይሆን ወገባቸውን የሚያሳርፉበት አልጋ፣ ከብርድ ራሳቸውን የሚከላከሉበት ብርድ ልብስ፣ ወደፊት አምርተው እህል የሚያስቀምጡበት ጎተራ፣ ለእዚያ እስኪበቁ ድረስ በጎተራው ውስጥ ለስድስት ወር የሚሆን ቀለብ አልፈው ተርፈው ለስድስት ወራት የሚሆን ቡና ጭምር አከማችተው ነበር ወንድሞቻቸውን የተቀበሉት።» (የሻምላው ትውልድ፤ ፋሲካ ሲደልል፤ ገጽ 315።)
ታሪካዊው እውነታ ይህ ሆኖ እያለ ዛሬ «ባለጊዜ» የሆነ መስሎት በወገኖቻችን ደም እጁን የሚታጠበው የሸኔ ቡድን የተጎነጨው የግፍ ደም፤ የመጥፊያው ምክንያት እንደሚሆን ወደ አእምሮው ተመልሶ ያሰበ አይመስልም። በተለይም በትውልድ እልቂት ተጠያቂ የሆነውና የፍትሕ ሰይፍ ሊያርፍበት ከጫፍ ላይ ለደረሰው የአሸባሪው ሕወሓት ቡድን መጋለቢያ የሆነው የሸኔ በማን ሳንባ እንደሚተነፍስና በማን አእምሮ እንደሚያስብ በግልጽ የታወቀ ነው።
ጨካኞች በአገር ክብር፤ በወገን መኩራት የሚሉት አስተሳሰብ የሚዞርባቸው አይደለም። እነርሱ ሆዳቸውን አምላካቸው፣ ነውራቸውን እንደ ክብራቸው እየቆጠሩ ስለሚኖሩ «ብሔሬ» የሚሉትን ወገን ስሙን እንጂ በጎ ተግባሩን አይኖሩበትም። አልፎም ተርፎ በአገር ላይ ከተሰለፉ ባእዳን የውጭ ጠላቶቻችን ጋር ተሰልፈው ማበራቸው የከንቱነታቸው ተቀዳሚ መገለጫ ነው።
ለምሳሌ፡- በሰኔ አስራ አንድ ቀን የፈጸሙትን የግፍ ጭካኔ ቀድሞ እንዲያስተጋቡላቸው የተዋዋሉት የግብጹን “Dail News” ጋዜጣ እና ከሌሎች መሰል የሚዲያ ተቋማት ጋር መሆኑ የሚረጋገጠው ድርጊቱ በተፈጸመ በጥቂት ደቂቆች ውስጥ የእልቂቱ ዜና እንዲሰራጭ መደረጉ ነው። በዚህን ዓይነት ቅንብር የደም ቃልኪዳን የተማማሉት «ደማቸውን ደመ ከልብ» ያደረጓቸውን ወገኖቻችንን ለመጨፍጨፍ ብቻማ ሳይሆን አገሪቱን ወደማያባራ የመተረማመስ አዘቅት ውስጥ ከቶ ከጌቶቻቸው ዘንድ ተስፋ የተገባላቸውን ዳረጎታቸውን ተስገብግቦ ለመቀበል በመጓጓት ጭምር አቅደው ነበር።
በመልካም የእርሻ ማሳ ላይ አረም ከየት መጣ ሳይባል እንደሚፈላ ሁሉ፤ በአገርና በሕዝብ መካከልም ያልተጠበቁ ዘግናኝ ክስተቶች እንደሚፈጸሙ ይታመናል። ይህንን መሰሉን የእኩያን እቅድ ቀድሞ በማክሸፉ ረገድ ግን የሕዝብን ሰላምና ጸጥታ ለማስከበር ቀዳሚውን ኃላፊነት መውሰድ የሚገባው መንግሥት ቀድሞ የቤት ሥራውን መሥራት እንደሚገባው ተደጋግሞ ተመክሯል፤ ሲበረታም መገሰጹ አልቀረም።
ዓላማ ቢስ ቡድኖች ሁሌም ኢላማቸው/ ታርጌታቸው ምስኪኑንና ለፍቶ አዳሪውን ዜጋ ማጥቃት ነው። ፈሪ ሰው የሚያደምጠው ኅሊናውን ሳይሆን ቅዠቱን ነው። ስለዚህም ሁሌም እንደባነነ ነው፤ ደግሞም እንደቀባዠረ። ጭንቅላቱ ትራስ ሳይነካ እንደተቅበዘበዘ ውሎ የሚያድረው በከንቱ ያፈሰው የንጹሐን ነፍሶች ወደ ፈጣሪያቸው የሚያደርጉት እሪታና የፍርድ መማጸኛ እንዳባነነው ነው።
ለዚህ አገላለጽ በጥሩ አብነት የሚጠቀሰው የቅዱስ መጽሐፉ ቃየል ነው። ቃየል የወንድሙን ደም በከንቱ ቅንዓት ካፈሰሰ በኋላ ፈጣሪ በመለኮታዊ ነጎድጓድ ድምጹ የጠየቀው እንዲህ በማለት ነበር፤ «ወንድምህ አቤል ወዴት ነው?» እርሱም ለኃያሉ ፈጣሪ የመለሰው የእብሪት መልስ፤ «አላውቅም የወንድሜ ጠባቂው እኔ ነኝ!?» ፈጣሪም በፊናው ውሳኔውን እንዲህ በማለት አሳወቀው፤ «የወንድምህ የደሙ ድምጽ ከምድር ወደ እኔ ይጮኻል ።
አሁንም ደሙን ከእጅህ ለመቀበል አፍዋን በከፈተች በምድር ላይ አንተ የተረገምህ ነህ። ኮብላይና ተቅበዝባዥም ትሆናለህ።» ቃየልም በራሱ አንደበት ያረጋገጠው ያንንነው የፈጣሪን እርግማን ነበር። እንዲህ ሲል፡- «በምድርም ላይ ኮብላይና ተቅበዝባዥ እሆናለሁ።የሚያገኘኝም ሁሉ ይገድለኛል።» (ኦሪት ዘፍጥረት ምዕ. 4)
አሸባሪው ሸኔም ሆነ ጋላቢው ሕወሓት ወይንም በውጭ አገራት ተጠልለው አለንላችሁ የሚሏቸው የእኛዎቹ የእንግዴ ልጆችና ባዕዳን ሴረኞች የመጨረሻ ፍጻሜያቸው አንድም እርስ በእርስ መበላላት ወይንም እንደ ጉም ብን ብሎ መጥፋት ነው። እንዴት? ምላሹ ባይዘረዘርም አይጠፋቸውም። መላው ሕዝብም ቢሆን እንደ ሌሎቹ ብሔራዊ ንቅናቄዎች እነዚህን የክፋት ኃይላት ለመፋለምና ለማጋለጥ ሆ! ብሎ ሊነሳ ግድ ነው።
ክፉዎች ፍጻሜያቸው እንደ ትቢያ ብን ብሎ መጥፋት ቢሆንም የሕዝብ የተቃውሞ ድርሻም ቀላል የሚባል አይደለም። ጨካኞች ታሪክም አሻራም አይኖራቸውም። ለሞቱት ኀዘናችንን፣ ልባቸው ለቆሰለ መጽናናትንና ድጋፍ ለሚፈልጉ አለኝታነታችንን ለማረጋገጥ በአንድ ልብ ሆነን መንቀሳቀሱ ግን ጊዜ የሚሰጠው አይደለም። ሰላም ይሁን!
በ(ጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሰኔ 18 /2014