መቼም ሽልንጌን ስለሚባለው አጭር ልቦለድ ሳትሰሙ አትቀሩም፤ እኔ አንደኛ ደረጃ ተማሪ ሆኜ አማርኛ መጽሐፍ ላይ ማንበቤን አስታውሳለሁ፤ ስዕልም ነበረው። ገጸባህሪዋ ድሬዳዋ ባቡር ተሳፋሪውን እያነጋገረች ተስማምታ ፍራፍሬ ትሸጥና ሂሳቡን ሽልንግ ትጠይቀዋለች። ሽልንጌን አምጣ ትለዋለች፤ ተሳፋሪው ሰጥቼሻለሁ ይላታል። ሲከራከሩ ባቡሩ ይነሳል።
ሴትየዋ ሽልንጌን እያለች ትከተላለች፤ ባበሩን ልትደርስት አልቻለችም፤ ሰውየው የሚወስደውን ወስዶ ከፍያለሁ ነው ያለው። እሷም ሽልንጌን እያለች እያለቀሰች በርቀት ብትከተለውም ባቡሩ ከአይኗ ተሰወረ። ያኔ ሽልንግ ትልቅ ዋጋ ነበረው፤ ይህን ጉዳይ ያነሳሁት የኔ ትልቅ ዋጋ የነበረው ሽልንግ ዛሬ አቅም አልባ ሆኖ የት ተሸሸገ ብዬ ነው።
አንድ የሳንቲምን ፋይዳ የሚያስረዳ ሌላ ታሪክ ላክል፤ በ1970ዎቹ ዓ.ም ይመስለኛል፤ ከአዲስ አበባ ወጣ ባለ አካባቢ፤ ከወደ አዲስ አበባ የመጣ እንግዳ በእንግድነት ለመጣበት ቤት ባለቤት ልጅ አንድ ብር/ ያኔ ባለወረቀት ነበር/ አውጥቶ ይሰጠዋል፤ ያ ልጅ ዛሬ ትልቅ ቦታ ደርሷል። ብሩን በደስታ ተቀብሎ ይደሰታል ሲባል፤ ልጁ ግን ከፋው፤ ብሩን አልፈልግም አለ፤ አለቀሰም፤ ውሰድ ተብሎ ቢለመን አሻፈረኝ በማለቱ ቀጠለ፤ ምነው ቢሉት እሱ የፈለገው ሳንቲም መሆኑን ገለጸ። ባለወረቀቱ ብር ገንዘብ አልመሰለውም። ሳንቲሞች ተሰጡትና ችግሩ ተፈታ። የሳንቲም ዋጋ እዚያ ድረስ ነበር። በሳንቲም ብዙ ነገር እንደሚገዛ ያውቅ ነበር።
በአገራችን ሳንቲም ትልቅ ስፍራ እንደነበረው ከታሪክም እንረዳለን። ኢትዮጵያ በዓለም ገንዘብን በመጠቀም ቀዳሚ ናት። በአክሱማውያን ዘመንም ሳንቲሞች ለግብይት አገልግሎት ይውሉ ነበር። በዘመኑ ባልደርስባቸውም፤ በቤተመዘክር ገብቼ ባልጎበኛቸውም፤ ዝናቸውን ለመረዳት ምስላቸውን ለማየት ከታደሉት ወገን በመሆኔ እጽናናለሁ።
በዳግማዊ ምኒሊክ ዘመን እንደገና ለግብይት የበቁት ሳንቲሞች የወረቀት ገንዘቦች፤ ነገሥታቱ በተቀየሩ ቁጥር እየተቀየሩ እየታተሙ ለግብይት ይበቁ እንደነበር ካነበብነውና ከሰማነው ታሪክ ልንረዳ እንችላለን። በደርግ ዘመን ብላቴና የነበርን የሳንቲሞች አቅም፣ ዋጋና ብዛታቸው በራሱ ይናገር ነበር። ዛሬ ግን አምስት፣ አስርና ሃያ አምስት ሳንቲሞቹ ደብዛቸው ከጠፋ ቆየ፤ ሽልንግን/ ሃምሳ ሳንቲምን/ ያህል ገንዘብ ተሸሽጓል፤ አፍረው ይሁን ፈርተው አይታወቅም፤ ኪሳቹ ይወቁዋቸው።
ከሦስት ዓመት በፊት አንዳንድ ብላቴናዎች (ህፃናት)፣ ወራዙትና (ወጣቶችና) ወይዛዝርት በታክሲ መሳፈሪያዎች የብር ሳንቲም የመዘርዘር ስራ ያካሂዱ ነበር። ሳንቲሞቹን በመዘርዘር ለራሳቸው የሥራ ዕድል በመፍጠር የተጫወቱት ሚና በቀላሉ የሚገመት አይደለም፤ በዚህም አሁን ዋጋ አልባ ለሆኑት ሳንቲሞቻችን ጎንበስ ብለን ብናመሰግናቸው ምንኛ ደስ ባለኝ ነበር።
ብላቴና ሳለን ወደ ትምህርት ቤትም በሉት መዝናኛ ቤት ስናመራ ሳንቲም ወድቆ እናገኝ ነበር። የወደቀችውን ሳንቲም ዋጋ ስለነበራት ቀድሞ ለማንሳት እንሻኮት እንገፋፋ ነበር። ከአምስት ሳንቲም ያነሰ ዋጋ የነበራት አንድ ሳንቲም ደግሞ ብዙ ጊዜ እርባና ቢስ ስለነበረች መንገድ ላይ ተጥላ እናገኛት ነበር። እያየናት እናልፋታለን። ብናነሳትም ምንም የሚገዛበት ስላልነበረች፣ ስስም ስለነበረች እንሳሳላት ነበር። ምንም ግን የመግዛት አቅም ስላልነበራት መልሰን እንጥላት ነበር።
የዛኔው አንድ ሳንቲም መጠኑ የከሳ፤ ክብደቱ የሳሳና የቀለለ ውበቱ ግን የሚያሳሳና ያማረ ነበር ማለት እችላለሁ። መልኩ ብርማ ይመስላል። የዛሬውን የአንድ ብር ሳንቲም ልክ የያኔው አንድ ሳንቲም ይመስለኝ ጀምሯል። መጠኑና ቁጥሩ ቢጎላም ክብደቱ ቢበዛም አንዲት ስንጥር አይገዛም። ብሮች ተሰባስበው ካልሆነ በቀር። የአንድ ብር ሳንቲም አቅሙን ያጣውና አቅሉን የሳተው፣ ያነሰው ከወረቀት ወደ ብረት ከተሸጋገረ ብዙም ሳይቆይ ነው።
እንመራመር ካልን እኮ ከወረቀት ይልቅ የሚከብደው ብረት ነው፤ አይደል አንዴ ጎበዝ? በሃሳብም እንተጋገዝ። ግን አንድ ብሩ ከወረቀት ወደ ብረት በተለወጠ ጊዜ ሕልውናው ተናወጠ ወይ ብዬ እጠይቃለሁ ለራሴ። ዋጋ የሚያወጡ የነበሩ ፈራንካዎች ዋጋ ሲያጡ ሌላ ምን ማለት ይቻላል?
እኔ የሳንቲሙ አንድ ብር ለሸገርም ለአገርም ችግር ይዞ የመጣ ይመስለኛል። በአንድ ብሩ ሳንቲም ምክንያት አምስት፣ አስር፣ ሃያ አምስት ሳንቲሞች ከገበያ ከወጡ ቆዩ፤ አንድ ሳንቲም ከገበያ ከወጣ መቼና መቼ፤ የሚገርመው እነዚህን ሳንቲሞች ሃምሳ ሳንቲሙም/ ሽልንጉም/ መከተሉ ነው። የሚደንቀው ደግሞ ከሳንቲሞቹ ብዙም ሳይቆይ መሆኑ ነው።
ምን ስለሳንቲሞቹ ታወራለህ ትሉኝ ይሆናል። ይሄው አንድ ብሩም ዳር ዳር እያለው ነው፤ ችግሩ ሳንቲም መሆኑ ላይ ይሆን እንዴ? በቅጡ እናስበው ካልን ይሄ መዘዘኛ አንድ ብር ከወረቀት ወደ ብረት ከተቀየረ በኋላ የባሕርይ ለውጥ አመጣ፤ አቅም አጣ፤ ፈላጊ አጣ፤ ቀስ በቀስ ደግሞ እንደ ተቀሩት ሳንቲሞች እሱም ከገበያ እንዳይወጣ እሰጋለሁ።
አሁን ደግሞ ሌላው ችግር የሆነው ለኔ ቢጤ እንኳ አራት ስሙኒ አይደለም ሃያ ስሙኒ ወይም ሽልንጎች በርከት አድርጋችሁ ብትሰጡዋቸው ከተቀበሉዋችሁ ፈገግ እያሉ ሳይሆን ጭፍግግ ብለው ነው። በታክሲም ላይ አራት ስሙኒ ሳንቲም ሆነ በርከት ያሉ ሽልንጎች ብትከፍሉ ረዳቱ ላይቀበል ይችላል፤ ገንዘብ ነው ተቀበል በትሉትም አይሰማም።
የአንድ ብሩን ሳንቲም አምጣ ብሎ ሊንጣጣ ይችላል። በሕግ መቀበል ግዴታ እንዳለባቸው ብናቅም ከላይ የጠቀስኩዋቸውን በክፍያ መልክ ሳንቲሞች ለመቀበል ፍላጎት የላቸውም። የአስር ሳንቲሙን በብዛት ለመክፈል ብታስቡም አልቀበልም ሊላችሁ ይችላል፤ ለዚያው ጭምት ከሆነ ነው፤ ዋልጌ ከሆነ ደግሞ በጸያፍ ስድብ ሲያሻውም ድብድብ ሊሰነዝር ይችላል።የኔቢጤ ከሆነም የጠቀስኩዋቸውን ሳንቲሞች በርከት አድርጋችሁ ብትሰጡት በንቀትና በአግራሞት ቀና ብሎ እንደሚያያችሁ አትጠርጥሩ።
ነገሩ እየከፋ መጥቷል፤ በታክሲ ላይም የአንድ እና ሁለት ብር መልስ ቢኖራችሁ ላይመልሱላችሁ ይችላሉ። የሶስት ብር መንገድ ተሳፍረው አምስት ብር ሰጥተው ሁለት ብር ይመለስልኛል ብለው ሲጠብቁ ረዳቱ ጭጭ ይሎታል፤ ሁለት ብርን እንደ ያኔው አንድ ሳንቲም እያዩት ነው።
አንድ ሚኒባስ ታክሲ 12 ሰው ይጭናል፤ ከእያንዳንዱ ተጓዥ ላይ አንድ ብር ቢያስቀር 12 ብር ያገኛል፤ ሁለት ብር ቢያስቀር ደግሞ 24 ብር ማለት ነው። እሱ ሲጠራቀም እንደሚጠቅሙ ያውቃል፤ እኛ ሲጠራቀም ይጠቅማል ብለን መልስ ስትጠይቅ ዝም ይሉናል፤ ረዳቶቹ የሚመልሱትም እያላቸው የለም ይሉናል፤ ሊዘረጥጡህ ይሞክራሉ፤ ይህን ስል አሁንስ አንድ ብር ሁለት ብር መልስ የሚጠይቅ መስመር ላይ መግባት እያስጠላኝ ነው ሲል የሰማሁት አንድ የታክሲ አሽከርካሪ ታወሰኝ።
ሁሉም የሳንቲም ቀበኛ ሆኗል፤ የአንበሳ የከተማ አውቶቡስ ቲኬት ቆራጮችም ዘንድ ስትሄዱ እንደዚያው ነው። ቲኬት ቆራጮች ሳንቲም የለንም የዕለት ተዕለት ምላሻቸው ከሆነኮ ቆየ። እናንተም የአንድ ብሩን ሳንቲም ካልያዛችሁ የሦስት ብሩን የአንበሳ የከተማ አውቶቡስ መንገድ አምስት ብር ወዳችሁ ፈቅዳችሁ ትከፍላላችሁ። ሳንቲሙ ሲታተም ለአገልግሎት እንዲብቃቃ ሳይሆን ቀርቶ ይሆን? አገልግሎት ሰጪዎችስ ሳንቲም የለንም ማለት ግን ይችላሉ ?
እናም የአምስት፣ አስር፣ ሃያ አምስት ሳንቲሞቹ ደብዛ መጥፋት ሲገርመን የሽልንጎቹም ደብዛ ጠፋብን፤ ይህን መንገድ የሳንቲም ብሮቹም እየሄዱበት ናቸው። ለዚያውም ራመድ ራመድ እያሉ። ግሽበቱ እንደ አገር ሊያጋጥም የሚችል ሊሆን ይችላል። ፍጥነቱ ግን የሚያም እየሆነ ነው። በዚህ ጉዳይ ላይ የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎችም መንግስትም ቢመክሩበትና መፍትሔ ቢያመለክቱ የተሻለ ይመስለኛል።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 17 /2014