አርቲስት ኑሆ ጎበና በምስራቋ ፈርጥ ድሬዳዋ ከተማ በ1948 ነው የተለደው። የተወለደው ምስራቅ ሐረርጌ ነው ወደ ድሬ ዳዋ የመጣው የ5 አመት ልጅ ሳለ ነው የሚሉም አሉ።
አባቱ መሀመድ ጎበና፣ እናቱ ደግሞ ፋጡማ ሀሰን ይባላሉ። ከወለዷቸው አምስት ልጆች መካከል ደግሞ አንዱ ኑሆ ነበር። በአያቱ መጠራትን የመረጠው ኑሆ መሀመድ ጎበና በቤተሰቡ ውስጥ ከነበሩት አንድ ወንድም እና ሶስት እህቶቹ ይልቅ እርሱ ወደ ሙዚቃው መሳቡ ይነገራል።
ገና በለጋ የልጅነት ዕድሜው የሚያከናውናቸውን ነገሮች ሁሉ ከሙዚቃ ጋር ማያያዝ ይወድ አንደነበር ነው አብሮ አደጎቹ የሚናገሩት። ታላቅ ወንድሙን ጨምሮ ሌሎች አብዛኞቹ አብሮ አደጎቹ ወደ ኃይማኖታዊ ትምህርት ሲወሰዱ እርሱ ግን ሙዚቃን የሙጢኝ ብሎ እስከ ህልፈተ ህይወቱ ዘልቋል። በህንድ የሙዚቃ ስራዎች ይመሰጥ እንደነበር የሚነገርለት ኑሆ፣ ዜማውን በመውሰድ በአፋን ኦሮሞ በማንጎራጎር በአቅራቢያው ባሉ ሰዎች እየታወቀ መጣ። ለዚህ ደግሞ ሀሚድ ከተባለ የልጅነት ጓደኛው ጋር በመሆን በዚያ ዘመን ቤት ለብቻ ተከራይተው እስከመውጣት እና የሙዚቃ ስራቸውን አጠናክረው መቀጠላቸው ነው የሚነገረው።
ታዋቂው ኢትኖግራፈር አፈንዲ ሙተቂ ኑሆ ጎበና እና ትዝታዎቼ በሚል ርእስ በግል ብሎጉ ላይ ስለኑሆ ከጻፈው የተወሰነውን እንውሰድ። ድሮ “ኑሕ ሙሐመድ” እያልን የምንጠራው አርቲስት በ“ኑሆ ጎበና” መታወቅ የጀመረው በደርግ ውድቀት ማግስት ነው። ሆኖም ከዚህ መጠነኛ የስም ልዩነት ጀርባ ሌላ የተወሳሰበ ታሪክ የለም። ያለው እውነታ በአጭሩ እንደሚከተለው ሊገለጽ ይችላል።
“ኑሕ ሙሐመድ” በልጅነት ጓደኞቹ እና በድሬዳዋ ተወላጆች ዘንድ “ኑሆ” በሚል የቁልምጫ ስም ነው የሚጠራው። እርሱም የካናዳ ነዋሪ ከሆነ በኋላ የቁልምጫ ስሙን እንደ “መድረክ ስም” (Stage name) ሲጠቀምበት ኖሯል። “ጎበና” ደግሞ የአያቱ ስም ነው። በካናዳ ፓስፖርት ላይ ስሙ የተጻፈው “Nuh Mohammed Gobana” ተብሎ ነው። እንደምታውቁት፤ ፈረንጆች በአሰራራቸው የአባትን ስም ይዘሉትና “Surname” የሚሉትን ሶስተኛ ስም ከሁሉ በላይ ያገኑታል። በመሆኑም አርቲስቱ የውጪዎቹን ልማድ በመከተል ከስሙ ውስጥ የአባቱን ስም ይዘለዋል። ከመድረክ ስሙ ጋር የአያቱን ስም በማያያዝ “Nuho Gobana” እያለ ራሱን ይጠራል። እኛም በዚሁ ስሙ ስንጠራው ኖረናል። አርቲስት ኑሕ ሙሐመድ (ኑሆ ጎበና) በእርግጥም በድሬዳዋ ከተማ ነው የተወለደው። እናቱ “ፋጡማ አደም” ትባላለች። አባቱ ሼኽ ሙሐመድ ጎበና ይባላሉ።
ሼኽ ሙሐመድ በደቡብ ምሥራቅ ኦሮሚያ፣ በባሌ ዞን፣ በጊኒር ከተማ አካባቢ ነበር የተወለዱት። በ1940ዎቹ የእስልምናን ትምህርት ሊያጠኑ ወደ ሐረርጌ መጡ። ከትምህርታቸው መጠናቀቅ በኋላ “ኢጃዛ” ሲቀበሉ በድሬዳዋ ከትመው ማስተማር ጀመሩ። በዚያች የበረሃዋ ንግሥት በምትባል ከተማ ትዳር መሥርተው ሲኖሩ “ኑሕ” የሚባል ልጃቸውን በ1948 ወለዱ።
ከሼኽ ሙሐመድ ጎበና አብራክ የተወለደው ኑሆ በአባቱ ፈለግ አልተጓዘም። እርሱን የጠራው ሌላ የጥበብ ጥሪ ነው። በተጠራበት መንገድ ሲጓዝ ደግሞ ድንቅ አርቲስት ወጥቶታል። የመጀመሪያ ካሴቱን ካወጣበት ጊዜ ጀምሮ በብዙ አድናቂዎቹ በፍቅር ሲደመጥ ኖሯል። ኑሆ የሙዚቃ ስራውን የጀመረው በተወለደባት የድሬዳዋ ከተማ ነው። በድሬ እያለ የቀበሌ ኪነት ቡድን አባል በመሆን በተለያዩ የሐረርጌ ከተሞች
ስራውን አቅርቧል። በዚያ ዘመን የተጫወታቸው ዘፈኖች በሐረር ሬድዮ ጣቢያ ተቀርጸው የነበሩ ሲሆን አንደኛው ዘፈኑ በተለየ ሁኔታ በሬድዮ ጣቢያው የመዝናኛ ክፍለ ጊዜ ተደጋግሞ ይቀርብ እንደነበረ አስታውሳለሁ ይላል አፈንዲ ሙተቂ።
ታዲያ የያኔው ኑሆ ድምጽ በኋለኛው ዘመን ከምናውቀው ድምጹ ወፈር ይላል። ያንን ዘፈን ብትሰሙት የኑሆ ድምጽ መሆኑን ለማመን ይከብዳችኋል። ኑሆ ጎበና በሙዚቃው ነጥሮ የወጣውና የሙዚቃ መሣሪያ መጫወትን የለመደው በጅቡቲ ነው።
በዚያ ሳለ ከተጫወታቸው ዘፈኖቹ መካከል “Biyya too haadha too” / ሀገሬ እናቴ እንደ ማለት ነው / እና “Yaa Biyya too gaarii” / መልካሚቱ ሀገሬ ማለት ነው / የሚሉት በቀዝቃዛ ስልት የተጫወታቸው ዜማዎች በዘመነ ደርግ በሐረርና በአዲስ አበባው ሬድዮ ጣቢያዎች በአፋን ኦሮሞ ፕሮግራም ተደጋግመው ይሰሙ ነበር።
አርቲስቱ የሠራቸው የመጀመሪያዎቹ ሶስት ካሴቶች የተቀረጹት ከ1974 እስከ 1980 ድረስ በኖረባቸው ጅቡቲ እና ሳዑዲ ዐረቢያ ነው። ይሁን እንጂ ኑሆ በዘፈኖቹ አድማጩን በሙሉ ቁጭ ብድግ ማድረግ የጀመረው እንደ ፈረንጆች አቆጣጠር በ1988 ወደ ካናዳ ተሻግሮ የቶሮንቶ ከተማ ነዋሪ ከሆነ በኋላ ነው። በዚያ አገር ሳለ ነው ድምጹ እንደ ማረሻ ተስሎ በዘፈኖቹ ማስገምገም የተካነው።
ብዙዎች ኑሆን ከሱዳኑ ታዋቂ ድምጻዊ ሰይድ ኸሊፋ ጋር ያመሳስሉት ነበር፤ ይህ የሆነውም ከቶሮንቶ የለቀቃቸውን አልበሞች ከሰሙለት በኋላነው። አርቲስቱ ከሐረርጌ ባሻገር በሌሎች የኦሮሚያ ዞኖች እና በአጎራባች ክልሎች መታወቅ የጀመረው የጥበብ አፍቃሪዎች ከቶሮንቶ የለቀቃቸውን ሥራዎቹን ካጣጣሙለት ወዲህ ነው። ኑሆ በሙዚቃ ሕይወት ውስጥ ከአርባ ዓመታት በላይ አስቆጥሯል።
በዚህ ረጅም ጊዜ ውስጥ አስራ አንድ ካሴቶችን (አልበሞችን) ሰርቷል። ይሁንና እኔ አፈንዲ ሙተቂ አርቲስቱ ያሳተማቸውን አልበሞች በሙሉ በአንድ ሚዛን ላይ አላስቀምጣቸውም። በኔ እይታ ከ1982 እስከ 1984 መጨረሻ ድረስ ባለው ጊዜ የወጡት ሶስት አልበሞቹ የምንጊዜም ምርጥ ስራዎቹ መሆናቸውን አምናለሁ።
ከእነዚህም መካከል በ1984 የተለቀቀው “Isin waamti Harmeen” / እናታችን ትጠራችሁዋለች/የሚለው አልበም አንዱ ነው። እነዚህ አልበሞች በግጥም፣ በዜማ፣ በሙዚቃ ቅንብር፣ በሜሎዲ፣ በድምጽ፣ በቀረጻ እና በሚያስተላልፏቸው መልእክቶች ይህ ቀረሽ የማይባሉ ናቸው።
ከአፈንዲ እንመለስ እና ትውስታችንን እንቀጥል። ኑሆ ዘመኑን ሙሉ ማለት ይቻላል ህይወቱ በስደት የተሞላ ነበር። በአፍሪካ ከጂቡቲ በተጨማሪ ኬንያ፤ ከኢስያ በየመን እና ሳኡዲ አረቢያ ከአውሮጳ ጣልያን፤ በሰሜን አሜሪካ ካናዳ እና በሌሎችም በርካታ አገራት በስደት አሳልፏል።
ኑሆ ከሶስት አመታት በፊት ከኢቢሲ ጋር በነበረው ቆይታ ላይ ሙዚቃ ከኔ ጋር ነው የተወለደው፤ ትግልም ከኔ ጋር የታገለ ይሔ ጊታር ነው በማለት ስለእሱና የሙዚቃ ቁርኝት ተናግሯል።
ቢፍቱ ገነማ በተሰኘ የኪነት ቡድን የጀመረው የሙዚቃ ስራው ላይ በነበረው ጉዞ አብዛኛውን የስደት እና የትግል ጉዞ አጋሩ የነበረችውን ጊታሩን የለመዳት እንደ ሰው በትምህርት ሳይሆን በጆሮ በመስማት ብቻ ነበር።
ስለሁኔታው ሲገልጽም ብናገር ማንም ሰው አያምነኝም ግን የለመድኩት በዚያ መንገድ ነው ይላል። የሙዚቃዎቹ ማጠንጠኛዎች በሙሉ የኦሮሞ ህዝብ አንድነት ናቸው። ስለ አንድነት ሲዘፍንም ስሜታዊ እንደሚሆን ብዙዎች ይናገራሉ።
የጀርመን ድምጽ ራዲዮ ድምጻዊ እና የመብት ተሟጋቹ ኑሆ ጎበና ሲዘከር በሚል ርእስ ባዘጋጀው ዘገባ ላይ ይህን የኑሆ የኦሮሞ አንድነት ታጋይነት በሚከተለው መልኩ ዘግቦታል። ድምጻዊ እና የመብት ተሟጋቹ ኑሆ ጎበና በሚጫወታቸው የሙዚቃ ስራዎቹ በተለይ ስለ ኦሮሞ ህዝብ መብት ዘፍኗል፤ አንድነትን ሰብኳል፤ መለያየትን ነቅፏል። ለዚህ አንዱ ማሳያ ‹‹ቶኩማ ቶኩማ›› / አንድነት ፣አንድነት/ እያለ ያቀነቀነው ሶስት ትውልድ የተቀባበለው ተወዳጁ ዜማው ነው።
አንድ እንሁን፤ አንድ እንሁን፣ የኦሮሞ ልጆች አንድ እንሁን እስላም ክርስትና እኛን ላይለያዩን እምነት የግል ነው ሁላችሁም ተረዱ የፈጣሪን ስራ ለእርሱ እንተወው በጎሳ እና በወንዝ መከፋፈልን እንተው እያለ ይቀጥላል ኑሆ ኑሆ ጎበና በተለይ የመብት ጉዳዮችን በተመለከተ በሚያስተላልፋቸው መልዕክቶች ጥርስ የተነከሰበት የንጉሱ ስርዓት ተገርስሶ ደርግ ስልጣኑን እንደተቆጣጠረ ነበር።
በዚህም በኑሆ እና ጓደኛው ስራ ያልተደሰቱት የደርግ ባለስልጣናት በ1968 ዓ/ም ለጥቂት ቀናት አስረዋቸው እንደነበረ ታሪኩን በቅርበት የሚያውቁ ይናገራሉ።
ኑሆ አራት አስርት አመታት ገደማ በስደት ከኖረ በኋላ ወደ አገሩ ተመልሶ የነበረ ሲሆን፣ የጤናው ሁኔታ እና የኑሮ አለመመቻቸት ነገሮችን ከባድ አድርገውበት ነበር። ያጋጠመውን የጤና መታወክ እየታከመ ቆይቶም ጥር 10 ቀን 2014 ዓ.ም ከዚህ አለም በሞት ተለየ።
ዜና እረፍቱ እንደተሰማም ብዙዎች የተሰማቸውን ሀዘን የገለጹ ሲሆን፣ ከነዚህም መሀከል የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ይገኙበታል። ከንቲባ አዳነች በፌስቡክ ገጻቸው ባሰፈሩት መልእክት ‹‹ተወዳጁና ታዋቂው አርቲስት ኑሆ ጎበና በማረፉ ጥልቅ ሃዘን ተሰምቶናል።
አርቲስት ኑሆ ለኦሮሞ ኪነጥበብ ዘርፍ እድገት ዘመን የማይሽረው አስተዋፅኦ ማበርከት የቻለ የህዝብ ልጅ ነው። ለቤተሰቦቹ ለወዳጆቹና ለመላው አድናቂዎቹ በሙሉ መፅናናትን እመኛለሁ! ብለዋል። የኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በበኩሉ ባስተላለፈው የሀዘን መግለጫ መልእክት፡ አርቲስት ኑሆ ጎበና በአፋን ኦሮሞ ኪነ ጥበብ ዘርፍ እድገት ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸል።
አርቲስቱ በአፋን አሮሞ እና በሌሎች ቋንቋዎች በርካታ ጥዑመ ዜማዎችን ለአድማጭ ማበርከቱንም ተጠቅሷል። በጥበብ ስራዎቹ የኦሮሞ ህዝብን ጥያቄዎች ነቅሶ በማውጣት ለህዝብ የኖረ አንጋፋ አርቲስት መሆኑንም ነው ያመለከተው።
አርቲስቱ በወጣትነት ዘመኑ የደርግ እና የጨቋኙ ሕወሓት ቡድን ስርዓት ህዝብ ላይ ሲያደርስ የነበረውን በደል በመቃወም ሲታገል መኖሩም በመገለጫው ተነስቷል። ክልሉ በአርቲስቱ ህልፈት የተሰማውን ሀዘን ገልጾ÷ ለወዳጅ ዘመዶቹ እና ለአድናቂዎቹም መጽናናትን ተመኝቷል።
ጥር 12 ቀን 2014 ዓ.ም በአዳማ ከተማ አበበ ቢቂላ ስታዲየም የአስከሬን ሽኝት ከተደረገ በሁዋላ ወዳጅ ዘመዶቹና አድናቂዎቹ አንዲሁም የኦሮሚያ ክልል ባለስልጣናት በተገኙበት የቀብር ስነስርአቱ ተፈጽሟል።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ጥር 22/2014