በንጉሡ ዘመን የንግድ ሥራ በሰፊው ለሚሰሩ ዜጎች በአንጻራዊነት የተመቻቸና መንግስታዊ ገደብና ቁንጥጫ እምብዛም ያልነበረበት እንደነበረ በወቅቱ በንግድ ሥራ ውስጥ ተሳትፎ ያደርጉ የነበሩ ሰዎች ይናገራሉ።የሸቀጥ ንግድን አቀለጣጥፎ በመስራት ውጤታማ መሆን የቻለ አንድ ግለሰብ ነበር።አንድ ብሎ የጀመረውን ሱቅ የመክፈት ሂደቱን ገፍቶበት ወደ ስምንት አድርሶ እይታውን አስፍቶ ከንግድ ወደ ግብርና አዙሯል።ወቅቱ በዓለም ገብያ ጥሩ ዋጋ የሚያወጣ የግብርና ምርትን ለማምረት ይሁንታ አግኝቶ በትልቅ ተስፋ ተሰማርቷል።
ደርግ ወደ ስልጣን መጥቶ ከ500ሺ ብር ካፒታል በላይ ማንቀሳቀስ አይቻልም ሲል አወጀ።አንድ ግለሰብ ከአንድ በላይ ሱቅ ሊኖረውም አይገባም አለ።አንዳንዶቹ ሱቃቸውን በዘመድ አዝማድ አድርገው የመጣውን ከሀብት የመፈናቀል ፈተናን ሊያልፉት ሞከሩ።ሰራተኞች አሰሪዎቻቸውን ይዘው ፍርድ ቤት ማቆምም የዘውትር ተግባራቸው ሆነ።ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴው ላይ ውሃ ተቸለሰበት።ሀገር በፖለቲካው ብቻ ሳይሆን በኢኮኖሚው በተለየ አቅጣጫ ውስጥ ገባች።በሀብት ማማ ላይ ወደ ላይ መውጣት የጀመሩ ባሉበት መቆም ጥቂት የማይባሉትም ወደታች መውረድን ተያያዙት።ያ ግለሰብ አምርቶ ያገኘውን ምርት ለመሰብሰብ ቀናትን በሚጠብቅበት ጊዜ በመሆኑ ምርቱን ገበሬዎቹ ተቀራመቱት።በድንገት ነገሮች ከእጁ ላይ ብን አሉበት።
እንዲህ የመሰሉ ድንገተኛ ክስተቶች ያረፈበት አንድ ሰው በወቅቱ የሚገጥመውን ያልጠበቀውን ፈተና እንዴት ሊያልፈው ይገባል የሚለው ጥያቄ የመንደርደሪያችን ጥያቄ ናቸው።እንዲህ በመሰለ ታሪክ ውስጥ የህይወት ዘመንን አቅጣጫ የሚወስኑ ስህተቶች የሚሰሩትስ ምን ያህሉ ናቸው።
ሌላ ታሪክ፤ የጦርነት ታሪክ።ጦርነት ድንገት ተነስቶ ነዋሪዎች ከአካባቢው መሰደድ ሲጀምሩ፤ ያፈሩትን ሀብትና ንብረት ጥለው ሲሰደዱ።የሚታደግ ታዳጊ ፍለጋ ጮኸው የሚሰማቸው አጥተው አደጋ ሲጋለጥባቸው።አደጋው አይነተ ብዙ ሆኖ በቀጣይ ህይወት ላይ በህይወት የሚቀጥለው ሰው ላይ ጥላውን ሲያጠላ።ያልጠበቁት ሲሆን እንዴት ይታለፍ? ከስህተት ተጠብቆ ወደፊት ለመራመድ አቅምስ ይገኝ ይሆን? የስህተት መንገድ ከተጀመረ የማስተካከያው ወይንም የመመለሻው ትክክለኛው ጊዜስ የትኛው ነው?
የመኪና አደጋ ወይንም ጎርፍ እንዲሁም ሌላ ያልታሰበ ክስተት ተፈጥሮ ከሚወዱት ጋር ሲለያዩ ልብ እንዲት እየመታ ቀጣይን ህይወት ይቀበላል? እኒህ ሁሉ አንድን ሰው ይፈልጋሉ፤ በፈተና ውስጥ ጸንቶ ለማለፍ ጥርሱን የነከሰ ማድረግ የሚችለውን በማድረግ ወደ መዳረሻው ለመድረስ የሚጥርን ሰው።እግሮቹ የጀመሩት የስህተት መንገድ ካለም ፈጥኖ ማስተካከያውን የሚያደርግ አንድ ሰው።
ለጋብቻ ጊዜያትን እየቆጠረ ላለ በእጮኝነት ውስጥ ላው ሰው ከሌላኛው ወገን የእጮኝነት ጉዞን አቁሜያለሁ መርዶ ሲሰማ፤ ነገሮች እንዳልነበረ ሲሆኑ፤ አቅጣጫ ስታው ልብ ለማንም እንዳይከፈት እንዲከረችም አድርገው ሲያልፉ የሚዳዳን የስህተት መንገድ ይኖር ይሆን? መመለሻውስ ጊዜ? እንዲህ የመሰሉ የበረከቱ ክስተቶችን አንድ ሁለት ብሎ ብዙ ማስቀመጥ ይቻላል።ድንገተኛው የህይወት አቅጣጫን ቀያሪው ክስተት እግራችንን ወደ የት አቅጣጫ ይመሩታል የሚለው ጥንካሬያችን ትርጉም ባለው ሁኔታ ይወስኑታል።ወደ በቀል፣ ወደ ልብ መዝጋት፣ ራስን ወደ መጣል ወዘተ የመሰሉ የስህተት መንገዶች ከሆኑ መመለሻውን ጊዜ የሚጠይቅ።
ስህተት ሲባል
ስህተትን ማን ያስተውላታል፤ አደጋ ካደረሰች በኋላ ደጋግመን እናስባት ይሆናል እንጂ።የማረሚያ ቤቶች ውስጥ የሚሰማው የህሊና ድምጽ ግን ብዙ ይላል። ስህተትን ለመተርጎም ስንነሳ ስህተትን በስህተትነቱ ማስቀመጥ መቻልን እናንሳ።ባለንበት በድህረ ዘመናዊነት ዘመን ነገር ሁሉ ትክክል እንደሆነ አድርጎ ለማቅረብ የሚደረግ ጥረት አለ።በትክክልና በስህተት መካከል መለያ የሌለ መስሎ በተገኘው ሁሉ መንጎድ ተገቢ ተደርጎም የተወሰደ ይመስላል።መሳሳት የሌለብን እውነት ስህተት የሚባል የህይወታችን ክፍል መኖሩን ነው።
ተማሪዋ የተማሪነት እቅዷን ሳታሳካ ልጅ ማርገዝ ላይ መድረሷ ስህተት ከመሆኑ ውጭ ምንም ሊሆን አይችልም።በኢትዮጵያ ፊልሞች ላይ የምናየው የስህተት ማመካኛ የተለመደ አንድ ምክንያት አለ፤ በመጠጥ ግፊት የሚፈጠር ስህተት።“ሁለታችንም ሳናስብበት ነው እዚህ ነገር ውስጥ የገባነው”ተብሎ አንሶላ ሲጋፈፉ አድሮ ራስን ከተጠያቂነት ለማሸሽ የሚደረግ ጥረት አለ።መጠጥን በጋራ አንድ ብሎ ሲጀመርና ሁለት እያለ ሲቀጠል አስከትሎ ምን ሊያመጣ እንደሚቻል እየታወቀ ራስን ማጽናኛ ለማቅረብ የሚደረገው ጥረት በእውነቱ ምን ያህል ወርደን ራሳችንን ለማሞኘት የምንጥረውን ጥረት የሚያሳይ ይሆናል እንጂ ሌላ ትርጉም የለውም።በህይወት ውስጥ ለምንሰራቸው ስህተቶች እውቅና መስጠት ወደ መፍትሄው ለመሄድ ግማሽ መንገድን የመራመድ ያህል ነው።
ስህተት በማንም ሰው ህይወት ውስጥ ሊያጋጥም የሚችል ነው።ወደ ስህተት የገባነው ከእውቀት ማነስ፣ ነገሮችን አቅልሎ ካለማየት፣ ከሥራ ትጋት ማነስ፣ ስሜታችንን ተከትለን በመሄድ ወዘተ ሊሆን ይችላል።
ስህተትን በህይወት ግብ አንጻር ስናየው ግብ ወዳደረግነው አቅጣጫ ይዞን በማይሄድ መንገድ ውስጥ መገኘት እርሱ ስህተት ነው።ለምሣሌ ጤናማ ትዳር እንዲኖረው የሚፈልግ ሰው ገላውን አራክሶ ካገኘው ሁሉ ጋር አንሶላ ቢጋፈፍ የአምላክን ቃል መተላለፍ ብቻም ሳይሆን ዋጋ ሰጥቼዋለሁ ለሚለው የቤተሰብ ህይወት ዋጋ እንዳልሰጠው ያሳያል።በትዳር ውስጥ አብሮ ለሚኖር ሰው የሚያቀርበው የተለየ ስጦታ የሌለውም ነው።ያቀለልነው ነገር ሁልጊዜ የቀለለ ውጤትን ይዞልን ይመጣል።ባለንበት ዘመን ንጽህና ስለሞላው ቤተሰብ ማስተማር ሳይሆን ስለሚፈርስ ትዳር መቁጠር ላይ አተኩረናል።በትምህርቱ ገፍቶ ዶክትሬት ላይ ለመድረስ የሚያስብ ሰው የነገ ግቡን የሚያሳካው በዛሬው እርምጃው አማካኝነት መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ነው።በንግድም ይሁን በሌላው ዘርፍ የተሰማራ አሻግሮ ሲመለከት የሚያየው ያለው ሰው ዛሬ የሚኖረው እንቅስቃሴ ትርጉሙ ብዙ ነው።ከትልቁ ምስል አንጻር ዛሬ የማንኖረው ኑሮ እርሱ በስህተት ቢገለጽ ስህተት ላይ አይጥለንም።
ዓለማችን ስህተት በሚባሉ ጦርነቶች ውስጥ አልፋለች።ሀገራችንም ስህተት በሚል ሊገለጽ በሚችል የፖለቲካ ምልልስ ውስጥ አልፋለች ደግሞም እያለፈች ትገኛለች።ምክንያቱ እንደ ሀገር የያዘነው የጋራ ምስል ተፈጥሮ ለእዚያ አብረን መሰለፍ ባለመቻላችን ነው።ስህተት የሚለው ቃል በማንኛችንም መዝገበቃል ውስጥ የሚገኝ መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡
ስህተትን በዘላቂነት ከህይወታችን ውስጥ እየቀነስን ስንሄድ ማንሳት የሚገባን የውሳኔ አሰጣጥ ህይወታችንን ነው።ስህትትም ይሁን ትክክል የውሳኔ ውጤቶች ስለሆኑ።ስህተትን ለማስተካከል የሚኬደው መንገድም የውሳኔ መንገድ ስለሆነ፡፡
ውሳኔ
ወቅቱ የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት ነበር።ግለሰቡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርትን አጠናቆ የሚጠብቀው የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤት ስላልመጣለት በከፍተኛ ሃዘን ውስጥ የሚገኝበት ነበር።በእዚህ ወቅት ወደ ጦርሜዳ ለመሄድ ይወስናል።በተመሳሳይ ሁኔታ በሀገራችን ወቅታዊ ሁኔታ ምክንያት በሰሜኑ ጦርነት ላይ ለመሳተፍ ከዘመተው መካከል የአንድ ወጣት ታሪክ አውቃለሁ።ይህ ወጣት በሚኖረው ኑሮ ደስተኛ ያይደለ እና የቤተሰብ ሸክም እንደሆነ ራሱን የሚቆጥር ነው።ለሀገራዊ ጥሪው ምላሽ ሰጥቶም ዘመተ።እኒህ ሁለት ግለሰቦች የወሰዱት ውሳኔ አማራጭ በማጣት ህይወት ውስጥ ራሳቸውን ስላገኙ ሞትም ቢሆን ለሀገር ሞቶ ማለፍ የተሻለ ነው ብለው የወሰዱት ውሳኔ ነው።በሌላ አንጻር ደግሞ የሞቀ ስራ ያላቸው የተደላደለ ኑሮ የሚኖሩ እንዲሁ ለሀገራዊ ጥሪ ምላሽ ለመስጠት የዘመቱ እንዳሉ በሚዲያ ሰምተናል።ሁለቱም ለተመሳሳይ ጉዳይ ውሳኔን ያሳለፉ ቢሆንም ውሳኔ የወሰኑበት ልብ ግን የሚለያይ መሆኑን እናያለን፡፡
ከሰሞኑ ከቀይመስቀል የተሰማ ትኩረትን የሚስብ ዜና አለ፤ የጠፉ ሰዎች ዜና።ዘገባው ከ44 ሺህ በላይ ሰዎች በአሁኑ ወቅት በመላው አፍሪካ እንደጠፉ መረጋገጡን የዓለም አቀፉ የቀይ መስቀል ኮሚቴ (አይሲአርሲ) ዓለም አቀፉን የመጥፋት ቀንን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል ይላል። ዘገባው የወጣው ዓለም አቀፉን የመጥፋት ቀንን አስመልክቶ መሆኑን ተመልክተን የመጥፋት ቀን ጀርባ ስላሉት መጥፋቶች እናስብ።መጥፋትን ውሳኔ የሚያደርግ ሰው በሚጠፋበት ጊዜ እየወሰደው ያለው እርምጃ በትክክልና በስህተት ውስጥ ለመመልከት ማሰብ ያስፈልጋል።
አሳዛኙ ነገር 45 በመቶ የሚሆኑት ጠፊዎች ህፃናት መሆናቸው ነው።ህጻናቱ ተገደው የሚጠፉ ወይንም በሌሎች ስህተት ሰለባ የሚሆኑ መሆኑን እናስብና 55 በመቶ የሚሆኑት ህጻናት አለመሆናቸው በተወሰነ ደረጃ በመጥፋቱ አስበውበት የሚያደርጉት መኖራቸውን ያሳየናል።በእርግጥ ከነዚህ ከጠፉት 82 በመቶ ያህሉ በግጭት ከሚናጡ ከተባሉ ሰባት አገሮች ብቻ መሆናቸው ውጫዊ ፈተና ለመጥፋት ውሳኔን ለማድረግ ገፊ መሆኑን ያሳየናል።
ውሳኔ የህይወታችን የእለት ተእለት እንቅስቃሴ መወሰኛ መንገድ ነው።በቤተሰብ ጋር በምንኖበት ጊዜ ቤተሰብ እየወሰነልን እንራመዳለን።በራሳችን መወሰን በምንችልበት እድሜ ውስጥ ደግሞ እንዲሁ እየወሰንን እንራመዳለን።ውሳኔ በሌሎች በኩልም ይሁን በራስ በኩል ሊመጣ የሚችል በተግባር ድርጊቱ ወደ ስህተት ወይንም ወደ ትክክለኛ አቅጣጫ ሊያመራን የሚችል ጉዳይ ነው።
ቀዳሚው ስህተት ተግባራዊ ስህተት ሳይሆን የውሳኔ ስህተት ነው።አንድ ሰው መንታፊ ሆኖ ለመኖር ራሱን አዘጋጅቶ በመንታፊነት ህይወት ውስጥ አደጋ ደርሶበት ህይወቱን ያጣል።ይህ ሰው ስህተት የሰራው ህይወቱን እንዲያጣ ባደረገው የመንታፊነት ወቅት ሳይሆን ገና ከመጀመሪያው የመንታፊነት ስራውን የራሱ ስራ አድርጎ በወሰደበት ወቅት ነው።
ጥቂት የማይባሉ ወጣቶች በሴተኛ አዳሪነት፣ በሱሰኝነት፣ በተበላሸ ትዳር፣ ወዘተ ውስጥ እንዴት እንደገቡ ሲናገሩ በአግባቡ አስበውበት አለመሆኑን ያስረዳሉ።ሰው መሆናችን ቢያንስ በራሳችን ጉዳይ ላይ አስበን መወሰን እንድንችል መሆኑን መዘንጋት የለብንም።በቀላሉ የምንገባበት ማንኛውም ነገር በቀላሉ የምንወጣበት ላይሆን ይችላል።በመሆኑም የውሳኔ ህይወት ዋናው የህይወት አቅጣጫን በትክክል ወይንም በስህተት መስመር ውስጥ እንዲራመድ የሚያደርገው መሆኑን መረዳቱ ይኑረን።
ከአንድ ተራ ግለሰብ እስከ ሀገር መሪ ድረስ የውሳኔ ስህተት ይፈጠራል።የውሳኔው ስህተትም አላስፈላጊ ዋጋን ሊያስከፍል ይችላል።መውጫ መንገዱ አሁንም በውሳኔ ነገሮችን ለማስተካከል መሞከር ነው።ዛሬ ላይ ስህተት የሆነ ነገር፤ ነገ ላይ ትክክል ሊሆን ስለማይችል፤ ዛሬ ላይ ለማስተካከል መምረጡ የተሻለ ነው።የተሻለው ቀን ዛሬ ነው።የመዳን ቀን ዛሬ ነው እንዲል መጽሐፉ።
ስህተትን በስህተትነቱ መቀበል ተችሎ በውሳኔ በር አድርገን ትክክለኛውን መንገድ ለመራመድ ስንጀምር የሚገጥመን ጥያቄ የአቅም ጥያቄ ነው።ውሳኔያችንን ወደ ተግባር የመቀየር አቅም።ከስህተት መንገድ ተመልሶ ወደ ትክክለኛው መንገድ ለመግባት የሚያስፈልግ አቅም እንዲሁም ወደ ስህተት ላለመሄድ የሚያስፈልግ አቅም።ቅርብ ያለ ከሚስል እስከ እሩቅ የሚታይ አቅም።
አቅም
የገንዘብ አቅም ገዝፎ የወጣ በሰዎች መካከል ልዩነት መፍጠሪያ መሳሪያ ሆኖ እናያለን።“ገንዘብ ካለ በሰማይ መንገድ አለ” የሚለው አባባልም የሚጠቁመው ብዙ ነው።የመንግሥት አገልግሎትን ለማግኘት እጅ መንሻ ጠጋ አድርጎ ካልሆነ ነገር ሁሉ የማይታሰብ ሆኗል ብለው የሚያማማርሩትም ጥቂት አይደሉም።ከደህና መወለድም በአባባሎቻችን ውስጥ ስፍራ የተሰጠው ሆኖም የሚገኝ ነው።ከገንዘብና እውቀት የትኛው ይሻላል የሚሉት ክርክሮች ተማሪ እያለን የምናደርጋቸው ክርክሮች እንዲሁ ብዙ አስተምረውናል።
ለዛሬው ጽሁፍ ለአቅም የምንሰጠውን ትርጉም አሻሽለን አቅም ግን ገንዘብ አይደለም፤ አቅም እውቀትም አይደለም፤ አቅም ጥሩ የሚባል ዘመድም ሆኖ ቤተሰብም አይደለም፤ ወዘተ ብለን የአቅም ትርጉምን አጥብበን እንነሳ።አቅም በውጫዊ ትርጉምነታቸው ልንጠቅሳቸው የምንችላቸውን በሙሉ አይደሉም ብለን ከዘጋን በኋላ ግን አቅም ማለት ምንድን ነው ለሚለው ጥያቄ ምላሽ ሊኖረን ይገባል።እንደ አስፈላጊነቱ አይደሉም ያልናቸውም እንዴት አስፈላጊ እንደሆኑ ከጠበበው ትርጉሙ ተነስተን ብናስባቸው አይከፋም ይሆናል።
አቅም ማለት በአንድ ሰው ውስጥ ያለ መነሳሳት፣ እችላለሁ የሚል መንፈስ፣ ሊያደርግ የተነሳውን ለማከናወን የማይችል ውስጣዊ ጥንካሬ እንዲሁም ነገን አሻግሮ በማየት ውስጥ ዛሬን መኖር መቻሉ ነው ብለን እንተርጉመው።በአጭሩ ውስጣዊ አቅም! ውስጣዊ!!!
የአቅምን ምልዑ ትርጉም ወደ ውስጥ መውሰድ ተገቢ ነው።ውስጣዊ ጥንካሬ ወይንም ውስጣዊ ጥራት ስህተት ከመስራት ለመቆጠብ፣ ስህተትን ለመቀነስ እንዲሁም ከስህተት መንገድ ለመመለስ ወሳኙ ነገር ነውና።ገንዘብን ያለ ውስጣዊ አቅም የተቀበሉ ሰዎች ገንዘቡ ሲያጠፋቸው ልናይ እንችላለን።ስልጣንን ያለ ውስጣዊ አቅም የተቀበሉ ሰዎች ስልጣኑን ሰዎችን ማገለገያ ሳይሆን መበደያ ሊያደርጉት ይችላሉ፤ ደግሞም ሲያደርጉትም አይተናል እያየንም ነው።ቤተሰብነትን፣ ጓደኝነትን ወዳጅነትን ወዘተ ያለ ውስጣዊ አቅም መጠቀም የሚያስችሉ ሰዎች በስንፍና ወይንም በህይወት ጉድለታቸው ላይ ተደላድለው እንዲቀመጡ የሚያደርግ ነው፡፡
አዲስ አመት ሲመጣ ለራሳችን የምንገባቸው የትናንትን ስህተት ለማስተካከል መሄድ የምንፈልጋቸው መንገዶች አሉ።ጥያቄው እኒህን ለማድረግ የሚያስችለን አቅም ምን ያህል ይመዝናል የሚለው ነው።ውስጣዊ አቅማችን ደግሞ ከፍ ያለውን ስፍራ ይዞ።ውስጣዊ አቅም አስፈላጊነት ላይ የሚያምኑ ሰዎች ብዙ ናቸው።ውስጣዊ አቅም እንዴት ይገነባል የሚለው ጥያቄ ግን አብሮ መታየት አለበት።ውስጣዊ አቅም ግንባታ ለሰውነታችን በምንሰጠው ቦታ ሊጀምር ይገባል።ሰው በመሆናችን ውስጥ ያለውን እምቅ አቅም በመረዳት ውስጥ።የቱንም ያህል ችግር አለበት የሚባል ሰው አንዳች አቅም ያለው መሆኑን መጠራጠር አይገባም።
ወደ ኋላ የመመለስ ፈተና
ጭንቅንቅ ባለ ትራፊክ ውስጥ አንዳንድ መኪኖች ወደ ኋላ ሳይንሸራተቱ ወደፊት መሄድ ሳይችሉ ሲቀሩ ይስተዋላሉ።በእዚህ ጊዜ በኋላ ላለው መኪና ሼፌር አስጨናቂ መሆኑ ግልጽ ነው።እርሱም ወደ ኋላ እንዳይሄድ መኪናዎች ተደርድረው የተጨናነቁ በመሆኑ፤ ዝም እንዳይል ከፊት ያለው መኪና ወደ ኋላ እየመጣ በመሆኑ።የተሻለው መንገድ በተቻለው መንገድ ሁልጊዜ ከፊት ካለው መኪና ጋር ክፍተትን መፍጠር ወይንም እርቀትን መጠበቁ ነው።
እርቀትን መፍጠር በተቻለው መጠን ለመንቀሳቀስ መንሸራተት የግድ የሆነበት መኪና አደጋ ሳያደርስብን ራሳችንን መካለከል ክላክስ እያደረግን አጽንኦት ለመስጠት ይረዳናል።በህይወት ውስጥ ወደፊት ለመሄድ ስናስብ ወደኋላው እየመጣ አደጋ ሊያደርስብን የሚችል ነገር ሊኖር ይችላል።እርቀትን መፍጠር የምንችለው በውስጣዊ አቅማችን እና ነገሮችን በጥበብ ማስኬድ በመቻላችን ነው።
በአንድ ስህተት በሆነ መንገድ ውስጥ ተደላድሎ ተቀምጦ ዘመንን ከመጨረስ ለመውጣት ጥረት እያደረጉ እስከመጨረሻው መዝለቅ የተሻለ ነው።ወደ ኋላ የመመለስ ፈተና በሱስ ውስጥ ብቻም ሳይሆን በሌሎችም የህይወት አቅጣጫዎቻችን ያጋጥመናል።መፍቻ ቁልፉ የውስጥ አቅምን መሰረት ያደረገ የለውጥ ጉዞ መሆኑን መረዳት ነው።
ከስህተት መውጫው የተሻለው ቀን ደግሞ ዛሬ ነው ካልን፤ ዛሬ ላለን ውስጣዊ አቅም እውቅና ሰጥተን ሃይላችንን አሰባስበን ለጦርነቱ ራስን ማዘጋጀቱ ተገቢ ነው።ድል ማስመዝገብ ስንጀምር መነቃቃቱ ደግሞ የበለጠ ድላችንን ስር እንዲሰድ ያደርገዋል።በሰውነት ውስጥ ከፈጣሪ ያገኘነው አቅም አለ።ለእዚህ አቅም እውቅና እንስጥ ፈጣሪም ከአጠገባችን እንዲሆን በጸሎታችን እርዳታውን እንሻ።ስህተትን ለማስተካከል እርምጃን ለሚራመድ ሰው ጥረቱ ብቻውን እንደ ድል መቆጠር አለበትና ያ ሰው ብርቱ ነው።ዛሬ ከትናንት ስህተታችን ተጠቃሚ እንሁን፤ ዛሬ።
በአገልጋይ ዮናታን አክሊሉ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 29/2013