ኦሎምፒክ ከሚደረግበት ቦታ የሆነ ነው። እንደ አሁን በኮቪድ ምክንያት ነፃነት ተነፍጎ መንቀሳቀስ አስቸጋሪ ባልነበረበት የኦሎምፒክ ወቅት የተደረገ ታሪክ ነው። ቤተሰቡ በሀገራቸው የሚደረገውን ኦሎምፒክ ለመደገፍ ፕሮግራማቸውን አስተካክለው ክንውኑ ወደሚደረግበት ስፍራ ይሄዳሉ። የአስራ ሁለት ዓመት ታዳጊ ልጃቸውም አብሯቸው ኦሎምፒክን እየኮመኮመ ነው። አባትና እናት የሀገራቸውን ሰንደቅ ይዘው ለሀገራቸው ተወዳዳሪዎች ድጋፍ ያደርጋሉ፤ ልጅ ግን በወጥነት ማንን እንደሚደግፍ ግልጽ አልሆነላቸውም።
ታዳጊው ልጅ በትምህርቱ መካከለኛ የሚባል ተማሪ ሲሆን፤ በታሪክ ትምህርት ማንም አይቀድመውም። የትምህርት ውጤት የሚሰጠው በታሪክ ትምህርት ቢሆን እርሱ ሁልጊዜም አንደኛ በወጣ ነበር። ወደፊት በታሪክ ዙሪያ ምርምር እንደሚያደርግም በታዳጊነት ዕድሜው ውሳኔ አድርጓል። የሀገሩን ታሪክ፣ የአህጉሩን እንዲሁም የዓለምን ታሪክ አጥርቶ ለማወቅ አጠንክሮ የሚሻ ታዳጊ።
ታዳጊው እናትና አባቱ የሚያውቁት፤ ነገር ግን እየቆለፈ ማስታወሻ የሚጽፍበት ደብተር አለችው። “ልዩዋ” ደብተር ትባላለች። ደብተሯ ብዙ ጊዜ ከቤት አትወጣም። በኦሎምፒኩ ዝግጅቶች ሁሉ ላይ ግን ደብተሩን ይይዛል። በደብተሩ ላይ ሲጽፍ ግን አይስተዋልም። እናትና አባት በልጃቸው ሁኔታ ጥያቄ ገብቷቸዋል። “ደብተሩን ትይዘዋለህ፤ ግን ስትጠቀምበት አትታይም” ብለው ይጠይቁታል። የእርሱ ምላሽ “የሚጻፍበት ሳይኖር ለምን እጽፋለሁ” የሚል ነው። አባት ቀጠል አድርገው “የሚጻፍበት ምንድን ነው ይሉታል?” የልጁ ምላሽ “አባ ለመናገር ፈቃደኛ አለመሆኔን ባለፈው ነግሬሃለሁ” ይላል። እናት “ወይ ጉድ” ብለው የአባትና ልጅን ክርክር ያስቆማሉ።
ኦሎምፒክ እየተደረገ ለሚደግፉት ሀገር ድጋፍ በሚደረግበት ጊዜ ታዳጊው በወጥነት የራሱን ሀገር አይደግፍም። አንዳንዴ የራሱ ሀገር ተወዳዳሪ እያለ የሌላ ሀገር ተወዳዳሪ ደጋፊ ሆኖ ስሜቱን ይገልጻል። አባትና እናትም በልጃቻው ሁኔታ ግርም ይላቸዋል፤ ደግሞም ይናደዳሉ። “መደገፍ ያለበት የራስ ብሔራዊ ቡድን ነው። ለምን የሌላ ሀገርን ትደግፋለሁ?” ብለው አሁንም ይጠይቁታል። የታዳጊው ምላሽ “መደገፍ የምፈልገው መደገፍ ያለበትን ነው። እቺ ሀገር ላይ እኮ የእኛ ሀገር መሪዎች በእዚህ ወቅት ይህንና ያንን አድርገዋል፤ ያንንም አድርሰዋል። እነርሱን መካስ ሲገባን ደግሞ በስፖርት እነርሱን አሸንፈን መደሰት አለብን?” ብሎ ይመልሳል። በታሪክ ጥናቱ የደረሰበትን እውነት ግምት ውስጥ ያስገባ ድጋፍ መሆኑ ነው። እናት የታዳጊው ልጃቸው ንግግር ውስጥ ለየት ያለ አገላለጽ ሲኖር መጻፍ ይወዳሉ። ከአሁኑ ንግግሩ ‘መደገፍ የሚገባው መደገፍ ያለበትን ነው’ የሚለውን ወስደዋል።
የኦሎምፒኩ መዝጊያው ዕለት ሰው ሁሉ በፌሽታ በሰከረበት ታዳጊው ማስታወሻውን ገልጦ አንዳች ነገር ለመጻፍ ብእሩን አነሳ እናት አጮልቀው ሲያዩ ዓይናቸው የገባው ‘ድምፅ ለሌላቸው፤ ድምፅ ላላቸው’ የሚል ጽሑፍ ላይ ነው። ማታ እቤት ሲገቡ እራት ሰዓት ላይ ታዳጊው ስለ ማስታወሻ ደብተሩ ነገራቸው።
“አባና እማ እኔ የታሪክ ተመራማሪ መሆን እንደምፈልግ ታውቃላችሁ። በታሪክ ውስጥ የተሠራው በደል ሁሉ ምንጩ ምን እንደሆነ ማወቅ እፈልጋለሁ? በሰዎች መካከልስ ተፈጥሯዊ መበላለጥ ይኖር እንደሆነ ማወቅ እሻለሁ? ድምፅ ላላቸው፤ ድምፅ ለሌላቸውም የማስተላለፍው መልዕክት እንዲኖረኝም እፈልጋለሁ። …” እያለ ቀጠለ።
ድምፅ ከ ሀ እስከ ፐ
በእዚህ ሳምንት ውስጥ በኢቲቪ ዜና ከተላለፉት መካከል ስለ ቲውተር ተጽእኖ ፈጣሪነት የተነገረው ይገኝበታል። ሰዎች ቲውተርን ተጠቅመው ሃሳባቸውን እንዲት ለመሪዎች ማድረስ እንደሚችሉና ውሳኔን ማስቀየር የሚያስችል ዘመቻ ማድረግም እንደሚቻል ዘገባው ይመለከታል። በመቀጠልም እያንዳንዱ ሰው እንዴት የቲውተር አካውንት ሊከፍት እንደሚችልና ኢትዮጵያ ለገባችበት የህልውና ዘመቻ ድምፅ መሆን እንደሚቻል ትንታኔን ይሰጣል። ይህን ያነሳነው በሁሉም አቅጣጫ ስለሚሰማው ድምፅ ለማንሳት ነው።
በእዚህ ቅጽበት በዙሪያችን ያለውን ድምፅ ለማዳመጥ ጆሯችንን ብንከፍት ወደ ጆሯችን የሚመጣ ብዙ ዓይነት ድምፅ አለ። እዚህ ጋር ስህተት ሠራን፤ ለካንስ ድምፅ በጆሮ ብቻ አይመጣም። በቲውተር ገጽ ላይ የሚነበበው ድምፅ የመጣው በጆሮ ላይሆን ይችላል፤ በጽሑፍም እንዲሁ። ድምፅ ከ ሀ እስከ ፐ ስንል በጆሯችን የምንሰማውን ድምፅ ብቻ ማለታችን አይደለም። ሁሉንም ትኩረት እንድንሰጣቸው የሚፈልጉትን ነገሮች ለማለት እንጂ።
ዙሪያችን የሚሰሙ ድምፆችን ሁሉ በምናደምጥበት ጊዜ ዕርዳታ የሚያሻውን ድምፅ መለየት እንዳለብን እንድናስብ በእዚህ ጽሑፍ ይዳሰሳል። በቴክኖሎጂ አማካኝነት ዓለም ሁሉ አንድ መንደር በሆነችበት በእዚህ ጊዜ ከአንድ ጫፍ ወደ ሌላ ጫፍ የሚሰማው የድምፅ ብዛት ከቁጥጥር ውጪ ነው። የሚዲያ ተጋላጭነቱ ለበረከተ ድምፅ ተጋላጭ አድርጎናል። ድምፅ ከሀ እስ ፐ በቀላሉ ከአጠገባችን ይደርሳል። ጥያቄው ከድምፅ ውስጥ ምላሽ የሚሰጠው ምን ዓይነት ድምፅ ነው የሚለው ላይ ነው? ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ መሆን ሲባል የሚነሳው እዚህ ጋር ነው። እኔ ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ መሆን እፈልጋለሁ የሚል ግለሰብ፤ ድምፅ ለሌላች ድምፅ መሆን የሚል ተቋም፤ ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ መሆን የሚል መንግሥት እንዲበዙልን ማሰብ ያስፈልገናል።
ድምፅ መሆን ሲባል
ድምፅ መሆን ሲባል በእኛ ላይ እንዲሆን የማንፈልገውን በሌላው ላይ ባለማድረግ፤ እንዲሁም በእኛ ላይ እንዲሆን የማንፈልገው በሌላው ላይ ሲሆን እኛ ላይ ቢሆን የምናደርገውን በማድረግ አስተዋፅኦ ማድረግ ማለት ነው። የተራበ ሰው ስናይ በተራበው ሰው ቦታ ላይ ሆነን ስንመለከት ያኔ ድምፅ የመሆንን አቅም እናገኛለን። መንገድ ላይ የሚተኙ የጎዳና ተዳዳሪዎችን ተመልክተን ራሳችንን እነርሱ ቦታ ላይ አድርገን ስንመለከት ያኔ ድምፅ መሆን እንችላለን።
በአጭሩ ድምፅ መሆን ሁለት ነገሮችን ከእኛ ይጠይቃል። የመጀመሪያው በሌላው ጫማ ውስጥ መሆን ሲሆን፤ ሁለተኛው በራሳችን ጫማ ውስጥ መሆንን።
በሌላው ጫማ ውስጥ ሆኖ መመልከት እኛ ጋር ያለው ነገር ብቸኛ ሃሳብ አድርገን እንዳናይ ምናልባትም ከፍረጃ ወጥተን ነገሮችን በሚዛን መመልከት የምንችልበትን ዕድል ይሰጠናል። በዙሪያችን ያሉ ሰዎች ሁሉ ካደመጥናቸው ሊናገሩ የሚፈልጉት ድምፅ አለ፤ ወይንም እየተናገሩት ያሉት። በሌላው ጫማ ውስጥ ተሁኖ እንቅስቃሴን ማድረግ ድምፅ የመሆንን ዕድልን ይሰጣል። ሁልጊዜ ነገሮችን ከራሳ ጫማ ብቻ መመልከት የተዛባ እይታ እንዲኖረን ያደርጋል። በሌላው ጫማ ውስጥ ተሁኖ ነገሮችን የመመልከት አካሄድ ነገሮችን በእውቀትና በመረዳት ወደማድረግ ደረጃ ያወጣል።
በራሳችን ጫማ ውስጥ ተሁኖ መመልከት መቻል ደግሞ ማድረግ የምንችለውን ለማድረግ በሚያስችል ሁኔታ እንቅስቃሴ ማድረግ እንድንችል ዕድል የሚሰጠን ይሆናል። በምድራችን ላይ ያለውን ችግር ልንፈታ አንችልም። በሀገራችን ያለውን ችግር እንደ ግለሰብ ልንፈታ አንችልም። የአንድ ሰውን ችግር በራሳችን አቅም ብቻ ልንፈታም አንችል ይሆናል። በራስ ጫማ ውስጥ ስንሆነ ድምፅ መሆን በምንችልበት ደረጃ ላይ ድምፅ መሆን እንድንችል ያደርገናል። መጽሐፉ ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ የሚለውም ለእዚህ ነው። ከራሳችን በላይ ልንወደው የምንችል ባልንጀራ የለም። እንደ ራሳችን የምንወድ ከሆነ እርሱ ትልቅ አምላካዊ ጥሪን ተቀብሎ መፈጸም ነው። ድምፅ መሆን ማለት በራስ ጫማ ሆኖ ማለትም ይኸው ነው።
ለሌሎች ድምፅ መሆን በሚዛኑ ቢሆን ምድርን መለስተኛ ገነት ማድረግ በቻልን ነበር። በሌላው ጫማ ውስጥ መሆን አለመቻል በሌሎች ስቃይ ውስጥ የምንደሰት፤ የሌላው ህመም የማይሰማን ሆነን እንገኛለን። በምድራችን እንዲሁም በዓለማችን ውስጥ እጅግ አስከፊ ፈተና ውስጥ የሚገኙ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች አሉ። በተቃራኒው ደግሞ ችግር ፈጣሪ ሆነው ነገርግን በነፃነት ህይወታቸውን እየመሩ ያሉም ይገኛሉ። ሌሎቹ ደግሞ የራሳቸውን አጥር ሠርተው በሞቀው ቤታቸው ውስጥ አሉ። አንዱ ለአንዱ ድምፅ መሆን አላስፈላጊ አድርጎ በመውሰድ አጥርን አጥብቆ መኖር። ይህን ቤትም አንድ ቀን የፈተና ማዕበል ሲነካው እንዲሁ ሌላው ቤት አጥሩን አጥብቆ ያይም ይሆናል።
እንደ አንድ ህያው ፍጡር ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ መሆንን በሚገባ ተረድተን የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴያችን አካል ማድረግ አለብን። ለእዚህም በሌላው ጫማ ውስጥ መገኘት፤ እንዲሁም በራስ ጫማ ውስጥ ተሁኖ መመላለስ። በየትኛውም መንገድ ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ ለመሆን ስንነሳ ድምፅ ያላቸውን ከሌላቸው መለየቱ ተገቢነት ይኖረዋል።
የዕለት እንቅስቃሴ ውስጥ ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ መሆን ማለት ከተጣበበው ጊዜያችን ቆርሰን፤ ከጥቂቷ ገቢያችን ቀንሰን፤ ሁሉም ነገር ሳይሞላለን ወዘተ ድምፅ መሆን ማለት ነው። ሁሉም ነገር ሞልቶልን ለተቸገሩት መድረስ፤ ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ መሆን በምድር ላይ የማይቻል ነው። አንዱ ሲሞላ ሌላው ሲጎድል፤ ከአንድ የፍላጎት ደረጃ ወደ ሌላ የፍላጎት ደረጃ እያደግን ስለምንሄድ። ፍላጎት ገደብ በሌለበት አኗኗር ውስጥ እየኖርን እንዴት መቆረስ እንችላለን? እንዴየትም።
ድምፅ ያላቸው፤ ድምፅ የሌላቸው
ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ መሆን የሚያስብ ድምፅ ያላቸውንና ድምፅ የሌላቸውን ለያየቶ መመልከት አስፈላጊነት ሌላው ነጥብ ነው። ድምፅ ያላቸው የሚባሉ አካላት ድምፅ የሌላቸውን ድምፃቸውን ሊያፍኑ ይችላሉ፤ እንዲሁም ድምፅ መሆንም ይችላሉ። የኢቲቪ ዜናው የቲውተር አካውንት ክፈቱ የሚሠራው ድምፅ ላላቸው ነው። በእዚያው ቲውተር ዘመቻ አንዱ በቀኝ ሆኖ ድምፁን ሲያሰማ ሌላው ከግራ ሆኖ ድምፅ የማምከን ሥራንም ይሠራል። ልክ እንደ ጦር ሜዳ።
ድምፅ ያላቸው በትክክለኛው ቦታ ላይ ድምፅ መሆን እንዲችሉ ማሰቡ አስፈላጊ የሚሆነው ለእዚህ ነው። ድምፅ ያላቸው ሰዎችን ማወቅ፣ መቅረብ፣ ድምፅ ስለሌላቸው ማስረዳትና ድምፅ ማድረግ ሥራውን ፍሬያማ ያደርገዋል። የዲፕሎማሲ ሳይንሱም ይህንኑ እውነታ ይሠራበታል። የአፍሪካ መቀመጫ አዲስ አበባ እንዲሆን የተሠራው ሥራም በእዚሁ መልክ ነው።
ኢትዮጵያ በጣሊያን በተወረረች ጊዜ ድምፅ መሆን ይገባቸው የነበሩ፤ ድምፅ መሆን ባለመቻላቸው እንደሆነም እንዲሁ ሊታሰብ ይችላል። እውነታ በአደባባይ ተሰቅላ ለእውነት ጀርባቸውን በሰጡ ድምፃቸውን አፍነው በያዙቱ ምክንያት የሀገራችን ልጆች በግፍ እረገፉ። በሀገራችን ውስጥ ከሚፈጠሩ ግድያዎችና መፈናቅል ማግስት በማህበራዊ ሚዲያ ጎልተው የሚሰሙት የተወሰኑ አካባቢ መፈናቅሎች ናቸው ተብሎ ክስ ሲቀርብ እንሰማለን። ምክንያቱም የሌሎች አካባቢዎች ተመሳሳይ ድርጊት ድምፅ የሚሆናቸው ባለመኖሩ የታፈነ በመሆኑ።
አንዲት እናት በከተማ ሴፍትኔት ዕርዳታ ማግኘት እንዲችሉ እንዲመዘገቡ ጥያቄ ይቀርብላቸዋል። ከመዝጋቢዋ ጋር ጉርብትና ስላላቸው በጎረቤታቸው የቀረበላቸውን ጥያቄ ተቀብለው ሊመዘገቡ ሲሉ የሴፍትኔት ተረጂ ማለት “የድሃ-ድሃ”ማለት ነው ተብሎ ይነገራቸዋል። በእዚህ ጊዜ ሴትዮው “የድሃ-ድሃ፤ በፍጹም አይደለሁም፤ ትንሽም ቢሆኑ የማከራያቸው ቤቶች አሉኝ፤ እንዴት ራሴን የድሃ-ድሃ አድርጌ ቆጥሬ ከሌሎች ጋር እሰለፋለሁ” በማለት ከምዝገባው ራሳቸውን ያስወጣሉ። በምትካቸው ከሚያከራዩት ቤት ውስጥ አንዱ ደሳሳ ቤት ውስጥ የሚኖሩ ነገርግን በነፃ የሚያኖሯቸውን ባልቴት አስመዘገቡ።
ይህ እውነተኛ ታሪክ ነው። እኒህ እናት በሌላውም ጫማ፤ እንዲሁም በራሳቸውም ጫማ መቆም የቻሉ እናት ናቸው። ድምፅ መሆን የቻሉ እናት። በእኒህ እናት ሁኔታ ሌሎች ሰዎች ተገረሙ። በሞራል ደረጃቸውም ላይ ተደነቁ። ሰው ሁሉ ያገኘውን ሁሉ ማግበስበስ በሆነበት ዘመን ምሳሌም ሊሆኑ የሚችሉ ሆነው አገኛቸው። የእኒህ እናት ስብዕና በአካባቢው ከፍ ያለነው። እንዲህ ዓይነት ሰዎች ደግሞ ድምፅ የመሆን አቅማቸው ከፍተኛ ነው። ድምፅ መሆን በየትኛውም ቦታና ጊዜ የሚሆን፤ በየትኛውም ሥራ ውስጥ የሚያጋጥም ነው፤ አንድ ነገርን ግን በጉልህ ይፈልጋል፤ ስብዕና።
ድምፅ መሆን ከስብዕና ጋር
መልካም ስብዕና ለእያንዳንዱ ሰው የሚያስፈልግ መሆኑ ለሁሉም ግልጽ ነው። መልካም ስብዕና ለባለቤቱም ለሰዎቹም መልካም ነው። ድምፅ መሆን የመቻል አቅም ከመልካም ስብዕና ጋር ያለውን ግንኙነት መረዳት ይገባል።
በመልካም ስብዕና የተገነቡ ሰዎች ድምፅ መሆን ሲችሉ የመሰማት ዕድላቸው ከፍተኛ ነው። መደመጥ ሁሉም ሰው በሰውነቱ ብቻ የሚያገኘው አለመሆኑን አስቀድመን ያነሳነውም ለእዚህ ነው። ሁሉም ሰው የመሰማት መብት አለው፤ ሁሉም ሰው ድምፅን የማሰማት ግዴታ አለበት፤ ነገር ግን ሁሉም ሰው እኩል አይሰማም።
በአካባቢያችን የተጣሉ ሰዎችን ለማስታረቅ የሚፈለገው ምን ዓይነት ነው? ለጋብቻ ጥያቄን ለማቅረብ የሚላኩትስ? በተመሳሳይ ሁኔታ በሀገርም ሆነ በዓለምአቀፍ ደረጃ ተሰሚነት ያለው ሰው በመሆን ውስጥ መልካም ስብእና ቦታ ይኖረዋል።
የመልካም ወጣት የስብዕና ማዕከልን የመገንባት ሥራን በምንሠራበት ጊዜ አሻግረን የምናየው ኢትዮጵያ በመልካም ስብዕና የታነጹ ዜጎች መኖሪያ እንድትሆን ነው። የዜጎች ምርታማነት እንዲሁም የእርስበርስ ፍሬያማ የሆነ መስተጋብር ከስብዕና ውስጥ የሚመነጭ ስለሆነ።
በጭንቅላት ምጥቀት የቱንም ያህል የደረሰ ሰው፣ በገንዘብ አያያዙ የቱንም ያህል ሀብታም የሆነ ሰው፣ በማንኛውም መለኪያ አንቱታን ያተረፈ ሰው ስብዕናው የተገነባ ካልሆነ ውጤት የለውም። የስብዕና ግንባታ አስፈላጊ የሚሆነው ለእዚህ ነው። መልካም ስም፤ ከመልካም ስብዕና ይመነጫል፤ ድምፅ ለመሆንም ዕድልን ይሰጣል።
በስብዕናቸው ጠንካራ የሆኑ ዜጎች ባሉበት ሀገር ውስጥ ሀገራዊ ምርታማነት እንዲሁም በምዕራቡ ዓለም የባህል ወረራ ተጽእኖ ውስጥ የመግባት ዕድላቸው አነስተኛ ሆኖ እንመለከታለን። ሀገራችን በስብዕና ላይ አተኩራ ከሠራች፤ የሚደመጡ ሽማግሌዎች ይኖሯታል። ካልሆነ ግን አሁን ያለንበት የስብዕና ማሽቆልቆል ቀጥሎ አደገኛ ሁኔታ ውስጥ ሊከተን ይችላል።
ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ መሆንን እንደ ማህበረሰብ ማስፈን ብንችል በሴቶች ላይ የሚደርሰውን አላስፈላጊ ጾታዊ ጥቃት መመከት በቻልን ነበር። በየመስሪያቤቱ እንደ ነዳጅ የሥራ ማንቀሳቀሻ የሆነውን ሙስናን ትርጉም ባለው ሁኔታ በቀነስን ነበር። በየቤተእምነቱ ከእምነት የሆነ ተጽእኖ ፈጣሪ የሆኑ ምእመናንን ማፍራት በቻልን ነበር። በኢትዮጵያ ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ መሆን እንደሚገባ መዘርዘር አንባቢውን ማድከም ነው። በየአካባቢው ድምፃችንን የሚሹ ዜጎች አሉ። ድምፅ በመሆን ውስጥ መልካም ስም ሥራውን ይሥራ።
የታዳጊው ደብተር እንደ መውጫ
በመነሻችን ላይ ያነሳነው ታዳጊ የሚመዘግብባት ደብተር ለቤተሰቡ እንደ ልዩ ደብተር ተቆጥራ ለዓመታት ቀጠለች። ታዳጊው ወጣት ሆነ፤ ታዳጊው ወደ ጉልምስና ዕድሜው አቀና። ትንሿ ደብተር የተሰኘም መጽሐፍ ጻፈ። እናትና አባትም የትንሿን ደብተር ምስጢር ከልጃቸው መጽሐፍ ውስጥ አገኙ። መጽሐፉ የሰው ልጆች መካከል በተፈጥሮ ልዩነት ይኖር እንደሆን አመላካች የሆኑ ነጥቦችን በመመዝገብ ልዩነት ፍለጋን የተሄደበትን እርቀት ያሳያል። የአሁኑ ጎልማሳ የቀድሞ ታዳጊ ድምዳሜ ሁሉም ሰው በተፈጥሮ አንድ ነው፤ ማንም ከማንም አያንስም፤ ማንም ከማንም አይበልጥም፤ ዕድል ግን ይለያያቸዋል የሚል ነው። ማንም ሰው ሀገር መርጦ አልተወለደም፤ ያደጉት ሀገራት የተወለደ ሰው ዕድል ገጠመው ይላል። ማንም ጎሳ መርጦ አልተወለደም፤ በልዩ ሁኔታ ሊደሰትም ሆነ ሊያዝን አይገባውም ይላል። በሰዎች መካከል ያለው ልዩነት፤ በተለያዩ ውሃ መጠጫ ቡርጭቆዎች ቀለም እንደመለያየት ነው ይላል። በሀገራት መካከልም ያለው ልዩነት አንዱ ሰው በምድር ላይ ሲኖር ለአስተዳደራዊ ህይወቱ ይጠቅመው እንደሆነ እንጂ የተለያዩ ፍጡራን ስለሆኑ አይደለም ይላል። በመጨረሻም እኔ እዚህ ሀገር የተወለድኩ ብሆንም የመላው ዓለም ሰዎች ወንድም ነኝ ብሎ ራሱን ይጠራል። ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ ለመሆን ስንነሳ ምንም ዓይነት ገደብ መካከላችን አይኑር የሚለው መልዕክቱም አብሮ ቀርቧል።
በአገልጋይ ዮናታን አክሊሉ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 8/2013