የጦርነት ወሬ ሽው ሲል ቅድሚያ ተጠቂዋም ተጎጂዋም ሴት ናት። ጦርነት በራሱ ሞትና ሰቆቃ ይዞ መምጣቱ እንዳለ ሆኖ ጉዳቱ ግን ሴቶችን ይበልጥ ሲያጠቃ ይታያል። በፍርሀትና በጭንቀት ውስጥ የምታልፈው ሴቷ ብትሆንም ቆርጣ የወጣች እለት ግን ከሷ በላይ ታሪክ ሰሪ እንደሌለ የታሪክ ሰነዶች ያስነብባሉ።
እንዲህ እንደኛው ትርፍ የሌለው ወገን ወገንን ከመጨረስ የዘለለ ለማንም የማይጠቅም ጦርነት ሳይሆን ሉአላዊነትን የደፈረ ማንነትን ሊያጠፋ የተነሳ የውጭ ወራሪን ለመመከት ከወጡ ጀግኖች መካከል ከኛዋ ጣይቱ የበለጠ ደማቅ ምስክር ያለመኖሩ እንዳለ ሆኖ ለዛሬ በዓለማችን በትልቅነቱ የሚታወቀው የሁለተኛው ዓለም ጦርነት ላይ በታላቅ የጀግንነት ገድል ከፈፀሙ የዓለማችን እንስቶች መካከል ከተለያዩ መረጃዎች ያገኘነውን እንዲህ አቅርበናል።
ቅድሚያ ከራስ ነውና በአርበኝነት ህይወታቸው ብዙዎችን አጀብ ካሰኙ ባለ ጀብዱዎች መካከል አርበኛ ሸዋረገድ ገድሌ ተጠቃሽ ናቸው። እኚህ ሴት በመንፈሳዊ ሕይወታቸው በጎ ማድረግን በዓለማዊ ሕይወታቸው ደግሞ ሀገር መውደድን፣ ለዓላማ ጸንቶ ማሸነፍን አስተምረው ያለፉ ታላቅ ሴት ናቸው። ትውልዳቸው ሸዋ ተጉለት አካባቢ ነው። አባታቸው አቶ ገድሌ በአጼ ምኒልክ ቤተመንግሥት የአገልጋይነት ሚና ነበራቸው። በቤተሰቦቻቸው እንክብካቤ አድገው በዘመኑ የነበረውን የቤተክህነት ትምህርት ተምረዋል። በአካባቢው ወግና ባሕል መሰረትም ከፊታውራሪ ደቦጭ ጋር ጋብቻ ፈፅመው የነበረ ቢሆንም ጋብቻው ግን መዝለቅ የቻለ አልነበረም። ምክንያቱ ደግሞ ሸዋረገድ በሴቶች ላይ የሚደርስን ግፍና ጭቆና አልቀበልም በማለታቸው ነው።
ጋብቻቸውን ካፈረሱ በኋላ ለምናኔ በነበራቸው ፍላጎት ለሦስት ዓመታት በደብረ ሊባኖስ ገዳም ነዳያንን እና መናንያንን በመመገብ፣ ከዚያም ወደ ኢየሩሳሌም አቅንተው ለሦስት ዓመታት አገልግለዋል፤ በኋላም በአባታቸው ጉትጎታና ልመና ወደ እናታቸው የትውልድ ስፍራ ተመልሰው በዚያ ኖረዋል።
የጉለሌ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያንን አስተክለዋል፤ በአምስት ዓመቱ የፋሽስት ኢጣሊያ ጦር ወረራ ኢትዮጵያ ለተቀዳጀችው ድል አይተኬ ሚና ነበራቸው።
በ1928 ዓ.ም ጣሊያን ኢትዮጵያን በግፍ ስትወር የአርበኝነትን መንገድ ካቀጣጠሉ ሴቶች አንዷ ናቸው። በጦርነቱ ወቅት መረጃ በማቀበል፣ መድኃኒት በመላክ እና መሣሪያ በመግዛት የማይተካ ሚና ተወጥተዋል። በዚህ የተነሳ 12 ጊዜ ታስረው የተፈቱ፣ እስከ ሞት ፍርድ የተፈረደባቸው ነገር ግን ወደ እድሜ ይፍታሽ የተቀየረላቸው አርበኛ ናቸው።
ሸዋረገድ ገድሌ ከሀገር ወጥተው አዚናራ ወደምትባል ከሰርዲኒያ ሰሜናዊ ምዕራብ በነበረች ደሴት በታሠሩ ወቅት የአርበኝነትሥራቸውን የበለጠ ይሠሩ ነበር። ሚስጥራዊ መልዕክት አንድ የጅቡቲ ወዳጃቸው በሰጣቸው ‘‘ሞአ አንበሳ ዘእምነገደ ይሁዳ’’ የሚል ጽሑፍ ባለበት ወረቀት ከንጉሡ የተላከ መልዕክት በማስመሰል ለአርበኞቹ መረጃ ያደርሱ ነበር።
በሁለተኛው ዓለም ጦርነት ታላቅ ጀብድ ከፈፀሙት መካከል ቼንግ ቤንሁ ተጠቃሽ ናት። ይች ሴት ሞትን በፈገግታ የተቀበለች ሴት እንደነበረች ይነገርላታል። ቼንግ ቤንሁ ቻይናዊ ጀግና ነበረች። ጃፓን እ.አ.አ. 1937 ላይ አገሯን ስትወር ቼንግ ከሌሎች ጋር ሆና ወራሪውን ጠላት ከአገሯ ለማባረር ታግላለች።
ቼንግ በስለት ተወግታ ከመገደሏ ጥቂት ደቂቃዎች በፊት የተነሳችው ፎቶግራፍ ሰዎች ያለፍርሃት የትጥቅ ትግል እንዲያደርጉ መነሳሳትን የፈጠረ ነበር። ፎቶግራፉን ያነሳው ጃፓናዊ ፎቶግራፍ አንሺ የቼንግን የመጨረሻ ሰዓታት መዝግቦ አስቀምጧል።
ይች ሴት በጃፓን ጦር በቁጥጥር ሥር ከዋለች በኋላ ድብደባ ተፈጽሞባታል፤ በበርካቶች በተመሳሳይ ጊዜ ተገዳ ተደፍራለች፤ ለጠላቶቿ ግን አልተንበረከከችም። ምንም እንኳን የቼንግ ሕይወት ቢያልፍም ከመሞቷ በፊት በተነሳችው ፎቶ ላይ በፈገግታ ተሞልታ እና እጆቿን ደረቷ ላይ አጣምራ አይኖቿ ካሜራውን እያዩ ነበር።
ቼንግ በ24 ዓመቷ ነበር እ.አ.አ. በ1938 የተገደለችው። እሷን ለመዘከረም በጃፓን ወታደሮች ከ300 ሺህ በላይ ቻይናውያን በተገደሉበት ናንጂንግ ከተማ 5 ሜትር የሚረዝም ሃውልት ቆሞላታል።
ሌላዋ ጀብደኛ ኖራ ኢናያት ካሃን ትባላለች። ሰላይዋ ልዕልት ኖራ ኢናያት ካሃን የህንድ ልዕልት እና የብሪታኒያ ሰላይ ነበረች። ኖራ በ18ኛው ክፍለ ዘመን የሕንዷን ማይሱሩ ከተማ ሲያስተዳድር ከነበረው ቲፑ ሱልታን የዘር ግንድ ትመዘዛለች።
ከሕንዳዊ የእስልምና እምነት አስተማሪ እና ከአሜሪካዊቷ ተዋናይት የተወለደችው ኖራ፤ ትውልድ እና እድገቷ ሩሲያ፣ ሞስኮ እንዲሁም ትምህርቷን የተከታተለችው ደግሞ ፈረንሳይ፣ፓሪስ ነው።
የቋንቋ ችሎታዋ የብሪታኒያ የደህንነት ኃላፊዎችን ቀልብ ገዛ። ኖራ ከብሪታኒያ ተነስታ በናዚ ጀርመን ቁጥጥር ሥር ወደሚገኘው ፈረንሳይ በፓራሹት አማካኝነት ገብታ የናዚ ጀመርን ወታደሮችን እንቅስቃሴ በተመለከተ ለእንግሊዝ መረጃ አቀብላለች፣ አጋር የነበሩትን ፈረንሳይ እና እንግሊዝ መካከል ግንኙነት እንዲፈጠር ረድታለች።
ኖራ አደገኛ የሚባለውን የሬዲዮ ኦፕሬተርነት ኃላፊነትን በብቃት ተወጥታለች። በጠላት ክልል ውስጥ ላለመያዝ በተደጋጋሚ መቀመጫዋን ትቀያይር ነበር። በመጨረሻ ግን በናዚ ጀርመን ደህንነት ኃይል ተያዘች። ኖራ ለእስር በተዳረገችበት ወቅት በተደጋጋሚ ከእስር ለማምለጥ ሙከራ አድርጋለች። ለማምለጥ በሞከረች ቁጥር የሚደርስባት ስቃይ እና እስር በከፋ ሁኔታ ይባባስ ነበር።
ናዚ ጀርመኖች የተለያዩ ስልቶችን በመጠቀም ኖራ መረጃዎችን እንድታወጣ በርካታ ጥረቶችን ቢያደርጉም ሳይሳካላቸው ቀርቷል። ጀርመኖች ‘ሜድላይን’ ከሚባለው የሚስጥር ስሟ ውጪ ሕንዳዊ ስለመሆኗ እንኳ ማወቅ አልቻሉም።
እ.አ.አ. መስከረም 1944 ላይ ኖራን ጨምሮ ሌሎች ሶስት ሴቶች፣ ጀርመን ወደሚገኝ ማሰቃያ ካምፕ ከተወሰዱ ከቀናት በኋላ ተረሽነዋል። ኖራ ለጀብዱ ሥራዎቿ የፈረንሳይ እና ብሪታኒያ መንግሥታት ሽልማት አበርክተውላታል። እርሷን የሚዘክር ሃውልትም በለንደን ከተማ ቆሟል።
በሶስተኛነት የተቀመጠችው ጀብደኛ ሊዩድሚል ፓቨሊቼንኮ ትባላለች። ሊዩድሚል ፓቨሊቼንኮ ባሪክ እጅግ ውጤታማ ከነበሩ አልሞ ተኳሾች መካከል አንዷ ነበረች። ናዚ ጀርመን እ.አ.አ. 1941 የተባበሩት ሶቬት ህብረትን በወረረበት ወቅት 306 ጠላቶቿን ከርቀት መትታ ጥላለች። ከእነዚህም መካከል ቀላል የማይባሉት እንደ እርሷ አልሞ ተኳሾች ነበሩ።
ከአልሞ ተኳሾች ጋር የነበራት ግብግብ ‘ሌዲ ዴዝ’ የሞት ሴት፣ የሚል ስም አሰጥቷታል። የናዚ አልሞ ተኳሾች ሊያገኟት አልቻሉም፤ ይሁን እንጂ በሞርታር ጥይት ተመትታ በደረሰባት ጉዳት አልሞ ተኳሽ ሆና መቀጠል አልቻለችም። ይህ ግን አገሯ ከጠላት ጋር የምታደርገውን ፍልሚያ ከማገዝ አልገደባትም።
የተለያዩ ተልዕኮችን በመውሰድ በመላው ዓለም የተጓዘችው ሊዩድሚል በሥራዋ አማካኝነት ከወቅቱ ፕሬዚዳንት ፍራንክሊን ሩዝቬልት ጋር ተገናኝታለች።
ሊዩድሚል ለጀብድ ሥራዋ የወርቅ ኮከብ ተሸላሚ ብትሆንም ሕይወቷ ካለፈ በኋላ ከሩሲያ የታሪክ መዝገብ ላይ ስሟ እንዲሰረዝ ተደርጓል።
“የሁለተኛው የዓለም ጦርነት በሶቬት ታሪክ ውስጥ ጀግና ተብለው በታሪክ መዝገብ ላይ የሰፈሩት ወንዶች ብቻ ናቸው። ሴቶች የዛኔ የታሪክ አካል አይደሉም” ስትል የጾታ እኩልነት ተሟጋቿ ኢራይና ስላቪስካ ለቢቢሲ ተናግራለች።
ነጭ አይጥ እየተባለች የምትታወቀው ናንሲ ዌክ ሌላዋ ጀብደኛ ሴት ናት ። ይች ሴት የተወለደችው ኒው ዚላንድ ያደገችው ደግሞ አውስትራሊያ ነው። ናንሲ አደገኛ ተዋጊ እና አማላይ ሴት ናት፣ ጠጪ እና ለጠላቷ ናዚ የራስ ምታት ነበረች።
ናንሲ ገና የ16 ዓመት ታዳጊ ሳለች ከትውልድ አገሯ በመጥፋት ወደ ፈረንሳይ አቀናች። በዚያም የጥንታዊ ግብጽ ቋንቋ እችላለሁ ብላ በመዋሸት በአንድ የፈረንሳይ ጋዜጣ ላይ ጋዜጠኛ ሆና ተቀጠረች። ከአንድ ፈረንሳይ ዜጋ ጋር በፍቅር የወደቀችው ናንሲ በፍቅር ተጣምራ ትዳር ለመመስረት ብዙ ጊዜ አልወሰደባትም። በማርሴ ከተማ ሳለች ጀርመኖች ፈረንሳይን እ.አ.አ. 1939 ላይ ወረሩ።
ናንሲ የፈረንሳይ አርበኞችን ተቀላቀለች። በተለያየ አጋጣሚ በጀርመን ጦር ተከበው የነበሩ ፈረንሳያውያን ታጋዮችን እያስመለጠች ወደ ስፔን አሽሽታለች። ከብሪታኒያ በመነሳት በፓራሹት ከአውሮፕላን እየዘለለች በፈረንሳይ በርካታ ተልዕኮችን በድል ተወጥታለች። ከአንድ የጀርመን ካምፕ ጠባቂ ጋር በጨበጣ ውጊያ ድል ነስተዋለች። እስከ 500 ኪ.ሜትር ድረስ ወደ ጠላት ድንበር ዘልቃ በመግባት በማይታመኑ አጫጭር ጊዜያት ውስጥ የተለያዩ ተልዕኮችን በስኬት ተወጥታለች።
ድምጽ ሳታሰማ ጠላት መንደር ገብታ በመውጣት ክህሎቷ የተነሳ “ነጯ አይጥ” የሚል ስያሜን በጀርመን ጦር አሰጥቷታል። በ98 ዓመቷ እ.አ.አ. 2011 ከዚህ ዓለም በሞት የተለየችው ናንሲ፤ ለጀብድ ሥራዋ የተለያዩ ሽልማቶችን ተቀብላለች።
ታላቅ ፖለቲከኛ ፤ ዘጋቢ ፤ ሰላይ የነበረቸው ጄን ቫያል ሌላዋ ታላቅ ሴት ነች። ጄን ቫያል ትውልዷ በአፍሪካዊቷ ኮንጎ ሪፐብሊክ ቢሆንም በልጅነቷ ወደ ፈረንሳይ አቅንታለች። ጋዜጠኛ ሆና እየሰራች ሳለች ነበር ሁለተኛው የዓለም ጦርነት የተቀሰቀሰው። መኖሪያዋ የነበረውን ፓሪስን ጥላ በመሰደድ በደቡባዊ ፈረንሳይ ተደራጅተው የነበሩትን የፈረንሳይ ነጻነት ታጋዮችን ተቀላቀለች።
ጄን የምትልካቸው መልዕክቶች በኮድ የተቆለፉ ስለነበሩ ጠላት እጅ ሲደርሱ ከተራ አሀዝ እና የቃላት ድርዳራ ውጪ ትርጉም የሚሰጡ አልነበሩም። ጄን የናዚ ወታደሮችን እንቅስቃሴ እየሰለች ለአጋር አገሮች እና ለነጻነት ታጋዮቹ ትልክ ነበር። እ.አ.አ. 1943 ላይ በጠላቶቿ እጅ ወደቀች። ከዚያም የአገር ክህደት የሚል ክስ ተመሰረተባት።
በናዚ ጀመርን ከተያዘች በኋላ ወደ ማርሴ የሴቶች እስር ቤት ተልካ የጉልበት ሥራ ስትሰራ ነበር። ከእስር ቤት አምልጣ ይሆን በምህረት ተለቃ ግልፅ ባይሆንም ጄን ሁለተኛው ዓለም ጦርነት ህይወቷን አልነጠቃትም። እ.አ.አ. 1947 ላይ የፈረንሳይ ሴኔት አባል ሆና ተመርጣ ነበር።
በመልከኝነቷ የምትታወቀው ሄዲ ላማር ከጀብደኞቹ አንዷ ነበረች። የሆሊውዷ በውበቷ ገዳይ በሚል ቅፅል ስም የምትታወቀው ይህች ሴት ትውልደ ኦስትሪያዋ ሄዲይ ላማር በትወና ሥራዋ ዝናዋ የናኘ መልከ መልካም ሴት ነበረች። የሆሊውዷ እንቁ 6 ባሎች ነበሯት። ሄዲ የመጀመሪያ ትዳሯ ባይጥማት ከቬይና ተነስታ ወደ ፓሪስ ከዛም ወደ ለንደን አቀናች። በለንደንም ዝነኛ የነበረውን የጥበብ ሰው ሉዊስ ሜይር ጋር ተዋወቀች። በሆሊውድ መስራት እንድትችል የሚያስችላትን ኮንትራትም አስፈረማት። “የዓለማችን ውቧ ሴት” በማለት ያስተዋውቃት ጀመር።
የተሳተፈችባቸው 30 ፊልሞች ዝነኛ አድርጓታል። የሁለተኛው የዓለም ጦርነት ጀግና ያስባላት ግን የፊልም ሥራዎቿ አልነበሩም። የፈጠራ ሥራዋ እንጂ። የፈጠራ ሥራዋ አሜሪካ፣ ፈረንሳይ እና ብሪታኒያ የጠላቶቻቸውን መርከቦች ለማጥቃት ጥቅም ላይ የሚያውሏቸው ተተኳሾች (ቶርፒዶ) ፍሪክዌንሲዎች በጠላት እንዳይጠለፉ የሚያስችል ስርዓት ነበር።
ቶርፒዶዎቹ ፍሪኩዌንሲያቸውን በመቀያየር በጠላት እንዳይታፈኑ ወይም እንዳይጠለፉ አስችላለች። ምንም እንኳ ለፈጠራ ሥራዋ እውቅና ባይቸራትም፤ የፈጠራዋ ግብዓት የሆኑ ሃሳቦች በብሉቱዝ እና ዋይፋይ ቴክኖሎጂዎች ላይ ተንጸባርቀዋል።
ለአገሯ በርማ ነጻነት ድምጿን ከፍ አድርጋ ትናገር ነበር ማይ ዪ ሌላዋ ጀብደኛ ነች። የማይ ዪ ትግል የጀመረችው ጃፓኖች በሁለተኛው ዓለም ጦርነት ወቅት በርማን ከመውረራቸው በፊት ነበር። የእንግሊዝን ቅኝ ገዢነት ተቃውማለች።
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅትም በእግሯ በጠላት የተያዙ ስፍራዎችን እያቆራረጠች ጎራዴ እና መርዝ በበልቃጥ ይዛ ትጓዝ ነበር። በሕንድ ጃፓኖች ምን ያህል በበዛ ጭካኔ ሕዝቡን እያሰቃዩ እንደሆነ የሚገልፅ በራሪ ወረቀቶችን በርማዎች በሚገኙበት ስፍራ ትበትን ነበር።
በፓራሹት መውረድ ስልጠና የወሰደችው ዩ ምንም እንኳ የመጀመሪያ ልጇን ከወለደች በኋላ ከትዳር አጋሯ ጋር ወደ በርማ ለመመለስ ብታቅድም፣ የመጣላትን እድል ለሌላ ተዋጊ አሳልፋ በመስጠት ጦርነቱ ካለቀ በኋላ እ.አ.አ. በጥቅምት 1945 ተመልሳለች። ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ቢሆን ለነፃነት እና ከዚያም በኋላ ወታደራዊ መንግሥትን ታግላለች።
ሴት አንበሳ የሚል ቀፅል ሰም ያላት ራሱና ሰይድ ሌላዋ ታላቅ ሴት ናት። ኢንዶኔዢያዊቷ ራሱና ሰይድ በዚህ ዝርዝር ውስጥ ካሉት ጀግኖች ለየት ያለች ነበረች። በኢንዶኔዢያ የነጻነት ትግል ውስጥ ትልቅ ቦታ እንደነበራት ይነገርላታል።
ለእሷ ዋነኛ ጠላቷ ወራሪው የጃፓን ኃይል ሳይሆን የደች ቀኝ ገዢዎች ነበሩ። ገና በወጣትነቷ ነበር ወደ ፖለቲካ በመግባት የራሷን ፓርቲ የመሰረተችው። ፓርቲውም የኢንዶኔዢያ ሙስሊም ማህበር የሚባል ሲሆን ሃይማኖትና ህብረ ብሄራዊነትን የሚሰብክ ነበር።
በአንድ ወቅት የቅኝ ገዢው የደች ባለስልጣናትና ወታደራዊ ኃላፊዎችን የሚወርፍ ንግግር በማድረጓ ደግሞ ብዙዎች አይረሷትም። በዚህም ሴቷ አንበሳ የሚል ስያሜ ማግኘት ትችላለች። ይህንን ንግግር ባደረገችበት ወቅት ወዲያው በቁጥጥር ስር የዋለች ሲሆን ለ 14 ወራትም ታስራ ነበር።
ጃፓኖች በጦርነቱ ተሸንፈው ከኢንዶኔዢያ ከወጡ በኋላም አገሪቱ ነጻነቷን ማግኘት አልቻለችም። የደች ቅን ገዢዎች ተመልሰው መጥተው ነበር። በዚህም ምክንያት ለአራት ዓመታት የዘለቀና ብዙ ደም ያፈሰሰ ጦርነት ተደርጓል።
ታዲያ ራሱና ሰይድ በዚህ ጦርነት ላይ ቁልፍ ሚና እንደነበራት ይነገራል። በዋና ከተማዋ ጃካርታም አንድ መንገድ በእሷ ስም ተሰይሟል።
በዋሉበት ሜዳ ማትረፍን ከሚያውቁት የዓለማችን ጀግኖች መካከል እነዚህን ጠቃቀስን እንጂ በየቤቱ ያልወጡትን ቤት ይቁጠራቸው።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ሐምሌ 11/2013