እናትነት ስጦታ ነው። ሰው በአካል የተፈጥሮ ልጅ ስላገኘ ብቻ እናት መሆን አይችልም። እናት ለመሆን የእናትነት ፀጋ ሊሰጠን ይገባል፤ ሩህሩህ ልብ፤ ክፍት ጆሮ፤ ሰፊ አይን፤ ሰፊ ልብ፣ የማይታጠፍ እጅ ሊኖር ይገባል። የማይጨክን አንጀት፤ ልክ ተራግማ ተሳድባ ፊቷን ዞር አድርጋ የልቤን እንጂ ያፌን አትይብኝ የምትል አይነት እናት፤ ቢረግጧት መረገጧ የማይሰማት የኑሮ ሸክም አጉብጧት እንኳን ጫንቃዋን ድንድን አድርጋ የምትኖር ናት – እናት።
መውለድ ብቻ እናት አያስብልም ለማለት የሚያስደፍሩ፤ በአስገዳጅ ሁኔታም ሆነ በሌላ ምክንያት ልጆቻቸውን አውጥተው የሚጥሉ እናቶች በሞሉበት፤ መውለዳቸውን ሊረሱት እስከሚችሉ ድርስ አቅላቸውን የሳቱ እናቶች በበዙበት በዘመናችን፤ እናትነት መውለድ ብቻ እንዳልሆነ የሚያጠያይቁ ታላቅ እናት ምድራችን አፍርታለች።
በችግር ምክንያት ነው የወለድኩትን ልጅ የጣልኩት የሚሉ እናቶችን በምንሰማበት በዚህ ጊዜ ከሞቀ ቤታቸው የወጡት፤ ሀብት ንብረታቸውን የተውት ልጆችን በመሰብሰብ ምክንያት መሆኑ ከመሰማቱ በላይ ምን የሚደንቅ የእናትነት ፀጋ አለ። አንድም እንኳን ከአብራካቸው የወጣ ልጅ ሳይኖር የሺዎች እናት የተባሉትን እኚህን ታላቅ እናት ዋናዎቻችንን መንጠቅ የለመደው ኮሮና አሳጥቶናል።
ለልጆቼ ምን እሰጥ ምን አበላ ብለው ሳይጨነቁ ከቆሎ መሸጥ አንስቶ የተለያዩ ስራዎችን የሰሩት የአፍሪካዋ እማሆይ ተሬዛ እድሜ ጫን ካላቸው የሰነባበተ ቢሆንም የወቅቱ የአለማችን የጤና ፈተና በራቸውን ማንኳኳት እስከጀመረ ድረስ ለሞት የሚያደርስ ህመም እንዳልነበራቸው የቅርብ ሰዎቻቸው ይናገራሉ።
የክብር ዶክተር አበበች ጎበና ነፍስ ለእኔ ትለይብኛለች። የተለየች በቃ ርህራሄ ውስጥ ከእግር እስከ ራሷ የተነከረች ምንም አይነት የጭካኔ መልክ የማይታይባት ታላቅ ነፍስ ነች። የዚህችን ታላቅ ነፍስ ባለቤት ሞት ከነጠቀን ሳምንት ሞላ። ለዛሬም በሴቶች አምዳችን ለኢትዮጵያ ህዝብ እንደ እናት፣ እህት፣ አጋር የሆኑትን ወይዘሮ አበበች ጎበናን ልናወደስ ወደናል፡፡ መልካም ንባብ።
እኔም ልጆቻቸው እንደሚጠሯቸው እዳዬ ብዬ ልጣራ። እዳዬ መረታትን የማያውቁ እጅግ በጣም ጠንካራ ሴት ናቸው። ውልደታቸው በ1938 ዓ.ም ነው። የሰላሌ ፍቼ ለም ምድር ካፈራቻቸው የሀገር በረከቶች አንዷ ናቸው። እንደማንኛውም የገጠር ልጅ ከብት አግደው ውሃ ቀድተው እንጨት ለቅመው ነበር ያደጉት። መቼስ የኢትዮዽያ ሴት ልጆች በወጉ እንዳያድጉ ተብሎ የተፈረደባቸው ይመስል ገና እንደተወለዱ ነበር ለባል የተሰጡት።
በልጅነት ጫንቃ የማይሸከሙት ነገር ሆኖባቸው የጫጉላ ቤቱ እንደተጠናቀቀ ነበር የትውልድ ቀያቸውን ጥለው ወደ አዲስ አበባ የኮበለሉት። ይሄንና ይሄን መሳይ የልጅነትና የወጣትነት እድሜያቸውን ያሳለፉት እዳዬ በተለይም «እማማ» እያሉ የሚጠሯቸው ልጆች የእናትነት ፍቅርን ከእርሳቸው ያለስስት እንዳገኙ ይመሰክራሉ።
ፍቅር ያለስስት የሚሰጡት እናት “ሀ” ብለው የበጎ ስራቸውን የጀመሩበት አጋጣሚ ይህንን ይመስላል። ወይዘሮ አበበች ጎበና በ1972 ዓ.ም ሃይማኖታዊ በዓል ለማክበር ለንግሥ ወደ ግሸን ማርያም በሄዱበት ወቅት በኢትዮጵያ በነበረው ድርቅ ምክንያት ከሞት አፋፍ የነበሩ ሁለት ህፃናት ያገኛሉ። እናትነት ገደብ የሌለው ርህራሄ መሆኑን ተፈጥሮ የለገሰቻቸው እዳዬ የሞተች እናታቸውን ደረቅ ጡት ይዘው የሚያነቡ ህፃናትን መሻገር በምን አንጀታቸው ይቻሉት። እጃቸው የቻለውን ያህል አነሱ። ሁለቱን በእጃቸው አቅፈው የተቀሩትን በልባቸው ይዘው ነበር ከአካባቢው የሄዱት።
እንስፍስፍ አንጀታቸው አልችልላቸው ያላቸው ወይዘሮ ታዲያ ህጻናቱን ወደ ቤታቸው ይዘው በመምጣት የህጻናት ማሳደጊያ ስራቸውን «ሀ» ብለው ይጀምራሉ። አንድ ሁለት እያሉ የብዙዎች መጠለያ መሆናቸው ያላስደሰታቸው በርካቶች የትዳር አጋራቸውንም ጨምሮ አበደች ቢላቸው እንኳን ጆሮ ዳባ ልበስ ብለው ለአራት አስርት አመታት በሺዎች የሚቆጠሩ ወላጅ አልባ ህጻናትን ሳይታክቱ ለዘመናት አሳድገዋል። ማሳደግ ብቻ ሳይሆን ለወግ ማእረግ አብቅተዋል።
በዚህም የክብር ዶክተር ማዕረግ የተሰጣቸው ወይዘሮ አበበች ጎበና በህጻናት ላይ በሚሰሩት በጎ ተግባር «አፍሪካዊቷ ማዘር ተሬዛ» በሚል ውብ ስም የሚጠሯቸውም አሉ። አሁን ግን ያ ጠንካራ ጉልበት ተረቶ ለሞት እጅ ሰጥተዋል።
ወይዘሮ አበበች ከዘጠኝ አመታት በፊት ፍርድ ቤት ቀርበው ነበር፤ ምን ሊሰሩ አላችሁ? እድሜ ዘመናቸውን የለፉበትም ለብዙ ወላጅ አልባ ህፃናት መጠለያ ሆኖ ያገለለገው ድርጅት በሞታቸው የተነሳ እንዲሁ እንዳይቀር ብለው ነበር። በጊዜውም ´እኔ ስሞት ድርጅቱን መንግስት ይረከበው’ የሚል ኑዛዜ ለማቅረብ ነበር። ይሁንና ይህ ኑዛዜ በህግ ደረጃ እንደማይደገፍ ይገልፃሉ። ይህን የተናዘዙትም ድርጅቱ በግለሰብ እጅ ገብቶ አሰራሩ እንዳይበላሽ እና ገንዘብ እንዳይባክን ከሚል ስጋት የመነጨ እንደሚሆን አስበው ነበር። ሞቼ ስራው ይስተጓጎላል ብለው የፈሩት እንዳልሆነ ግን የቀብራቸው ዕለት የአዲስ አበባ መስተዳድር ምክትል ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ እንዲህ በሚል ቃል አፅንተውታል።
ክብርት ዶክተር አበበች ጎበና ላለፉት አራት አስርት ዓመታት ላከናወኑት የበጎነት ስራ ምስጋና ያቀረቡት ምክትል ከንቲባዋ ̋እናታችን ስላደረጉልን በጎነት ባለእዳዎች ነን፤ ወሮታም አለብን፡፡ በመሆኑም ይህ የሚሊዮኖችን ህይወት ያለመለመ የበጎ አድራጎት ማዕከል ቀጣይ ምእራፍ ምን ይሁን? የሚለው ላይ በጋራ እንስራ፡፡ ያን ማድረግ ስንችል ነው የእናታችን ነፍስ ሰላም የምታገኘው” ብለዋል።
̋እናታችን የችግሮቻችን መፍቻው ቁልፍ አንድነትና መተባበር መሆኑን ያስተማሩን እናት ናቸው፡፡ ይህንን አስመልክቶ አንድ አባባል አላቸው፡፡ ችግሮቻችንን የምንቀርፈው “በግለሰብ ደረጃ ለምፅዋት በሚወረወሩ ሽርፍራፊ ሳንቲሞች ሳይሆን በአንድነት፣ በማህበር እና በመተባበር በችግር ላይ ያሉ ወገኖቻችንን በተለይም ሴቶችን በማብቃት ነው፡፡” የሚል የተገበሩት አባባል እንደነበራቸውም አስታውሰዋል፡፡
ይሄ የግዙፍ ስብእና እሳቤ ውጤት ነው ያሉት ወይዘሮ አዳነች፤ የወገን ደራሽነታቸውን በቃልም በተግባርም ፈጽመውታል፡፡ የተለየ ሀብትና ትምህርት ሳይኖራቸው ፍቅር፣ ርህራሄ፣ ቆራጥነት እና ጥንካሬን ተላብሰው ለሰው መኖር የሰው ልጆች የመጨረሻው የብቃት ደረጃ ሚዛን መሆኑን ማሳያ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት የህጻናት ማሳደጊያው በፍቼ፣ ጉደር፣ቡራዩ እና በአዲስ አበባ ላይ ባሉ ቅርንጫፎችም ከ250 በላይ ሰራተኞች ተቀጥረው ለማህበረሰቡ ድጋፍ እየተደረገ ይገኛል። በህጻናት ማሳደጊያ ማዕከል ውስጥ ሰላሳ አራት ህጻናቶች ይገኛሉ። በማህበረሰቡ ውስጥ ድጋፍ የሚደረግላቸው በሺዎች የሚቆጠሩ ሴቶች ይገኛሉ። በተለይ ሴቶቹ የተለያዩ የሙያ ስልጠና በመስጠት ወደ ስራ እንዲሰማሩ ይደረጋል። ብድር እና ቁጠባ ላይ ድጋፍ የሚያገኙ ሴቶች አሉ።
«በማዕከሉ ስለሚያድጉ አዲስ ህጻናት ላይ ትኩረት አይደረግም» የሚሉት አቶ ቸሩ፤ ይልቁንም በማህበረሰቡ ውስጥ ሆነው ድጋፍ የሚያሻቸው ህጻናት ላይ ትኩረት እንደሚደረግ ይገልፃሉ። ይህም የሚሆነው ህጻናትን በማዕከል ውስጥ ከማሳደግ ይልቅ ከማህበረሰቡ ጋር ቀላቅሎ ማሳደግ በስነልቦና እና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ አዋጭ መሆኑ በመታመኑ እንደሆነ ያስረዳሉ። በመሆኑም በቀጣይ ጊዜያት አስገዳጅ ሁኔታ ካልተፈጠረ በስተቀር ህጻናትን በማዕከሉ ውስጥ ለማሳደግ እንደማይሞከር ይናገራሉ።
ይህ ብቻ አልበቃም እናቶች እና ህፃናት ኑሯቸው ከመደላደሉም በላይ ጤናቸው የተጠበቀ ይሆን ዘንድ አይነቱ ልዩ እና በርካታ መስፈርቶችን ያሟላ ነው የተባለ የእናቶችና የሕጻናት ሆስፒታል በአዲስ አበባ ተገንብቷል። በክቡር ዶክተር አበበች ጎበና ስም የተሰየመው ሀኪም ቤት በአዲስ አበባ አያት ተብሎ በሚጠራ አካባቢ ነው ለአገልግሎት ክፍት የሆነው።
700 ሚሊየን ብር ወጪ ተደርጎበታል የተባለው ሆስፒታል ከ400 በላይ የእናቶች ተኝቶ መታከሚያ ክፍሎች ያሉት ሲሆን፤ ይህም የመዲናዋ የእናቶች ህክምና አቅምን በእጥፍ የሚያሳድግ እንደሚሆን ተነግሮለታል።
እዳዬ በህይወት ዘመናቸው ላበረከቱት በጐ ተግባር ለፈፀሙት አርአያነት ያለው አኩሪ ሥራ የሰብዓዊነትና የሴቶች ህያው አርአያ የበጐ ተግባር ከተለያዩ ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ተቋማት ታላላቅ ሽልማቶችንና እውቅናዎችን አግኝተዋል፡፡ ከሽልማቶቹም መካከል
• ከጅማ ዩኒቨርሲቲ በሂውማኒቲ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ
• ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሜዳሊያ እና የክብር የምስክር ወረቀት
• በሁለተኛው የዓለም ምግብ ፕሮግራም ዓለም አቀፍ የሴቶች ቀን የክብር ተሸላሚ
• ከተባበሩት መንግስታት የኢትዮጵያ ማህበር፣ ከቤተሰብ ፌዴሬሽን ለዓለም ሰላም እና ከተባበሩት መንግስታት የበጎ ፈቃደኞች ፕሮግራም ዋንጫ እና የምስክር ወረቀት
• በCCRDA የብር እዮቤልዩ ክብር በዓል ላበረከቱት ከፍተኛ አስተዋፅኦ የእውቅና ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት
• ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የክብር የምስክር ወረቀት እና ዋንጫ
• ከኢትዮጵያ አየር መንገድ የክብር የምስክር ወረቀት፣ ሜዳሊያና ዋንጫ
• ከኢንትርሪሊ ጅየስ ኤንድ ኢንተርናሽናል ፌዴሬሽን ፎር ዎርልድ ፒስ የሰላም አምሳደርነት የምስክር ወረቀት
• በሰብአዊ እርዳታን በመደገፍ የቡድን ስፔን ሽልማት
• ከሴቶች ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮች አበረታች ማእከል የምስክር ወረቀት
• ለአፍሪካ ዘላቂ ልማት ፋይዳ ላለው አርአያነትና ተነሳሽነት ሥራቸው የማዕከላዊ አፍሪካ የክልል አሸናፊ በመሆን የምስክር ወረቀት እና ዋንጫ
• ዓለም አቀፍ ሽልማት “ከለንደን ወርልድ ዌር ቢዝነስ አዋርድ”
• በአፍሪካ ደረጃ ማዘር አፍሪካ (እናት አፍሪካ) ከደቡብ አፍሪካ
• ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት በተለያዩ ጊዜያት ዋንጫዎችንና ምስክር ወረቀቶችን
• ከአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ከንቲባ ጽህፈት ቤት በተለያዩ ጊዜያት ልዩ ልዩ ሽልማቶችን
• ከተለያዩ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች የማበረታቻ እና እውቅና ሽልማቶችን ወስደዋል፡፡
በተጨማሪም ከተለያዩ አለም አቀፍ ድርጅቶች ልዩ ልዩ የማበረታቻ እውቅና ሽልማቶች በዋናነት የሚጠቅሱ ሲሆን፣ ሌሎች ከመቶ በላይ እጅግ በርካታ ሽልማቶችንም አግኝተዋል፡፡ የእዳዬን ነፍስ በቀኙ ያስቀምጥልን፣ በአፀደ ገነት ያኑርልን በማለት ተሰናበትን።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ሐምሌ 4/2013