በገጠር አንዲት ድሃ ጎረቤቷ በደረሰ ለቅሶ ታዝናለች፤ ማዘን ብቻውን በቂ እንዳልሆነ ትረዳለች። በማህበረሰቡ የቆየ ባህልና ልማድ መሰረት እንጀራና ወጥ ለማቅረብ ታስባለች፤ ገንዘብ ግን አልነበራትም። የለኝም ብላ አልተቀመጠችም። እንደምንም ብላ ሦስት እንጀራ እና አንድ ድስት ወጥ ይዛ ለቅሶ ቤቱ ትሔዳለች ።
የሚቀበላት ታጣና ወደ ሐዘንተኛው ጠጋ ብላ “ሦስት እንጀራ አንድ ወጥ ይዤ መጥቻለሁ “ትለዋለች። ሰውየውም በልጁ ሞት አዝኖ ስለነበር ያለችውን ሳይሰማ ልጄ! ልጄ! እያለ ማልቀሱን ይቀጥላል፤ደግማ “ጌታዬ ይስሙኝ እንጂ” እያለች አላስለቅስ ስትለው ጊዜ ለቅሶውን አቁሞ “እባካችሁ ካመጣችው እንጀራ ላይ ወጥ አድርጉላትና ትሂድ “አለ ይባላል።
ኢትዮጵያውያን በግል ከሚያደርጉት መደጋገፍ በተጨማሪ ተሰባስበው በመረዳዳት ይታወቃሉ። በተለይ በደቦው፣ በሰርጉ ፣ በመከራው ቀን በመረዳዳት ክፉን ቀን ያሳልፉሉ፤ ልማቱን ያሳልጣሉ፤ ደስታቸውን ይገልጻሉ። በተለይ ለክፉው ቀን ልዩ የመረዳጃ መንገድ ቀይሰው ነው የሚደጋገፉት፤ በእድር ።
ዕድሮች የየራሳቸው ሕግና ደንብ ወጥቶላቸው አባላቱ ወርሐዊ ክፍያ እየከፈሉ ይረዳዱባቸዋል። ተደጋጋሚ ሀዘን ከተደራረበና ወጪ ከበዛም ድጎማ በሚል ተጨማሪ ክፍያ ይከፍላሉ ። በእድራቸው ህግ መሰረት ገንዘብ በየወሩ ይሰብስባሉ፤ ሞት ሲያጋጥም በሕጉ መሰረት ገበና ይሸፍናሉ፤ ይደግፋሉ ። ዕድር በዚህ ባህላዊና ማኅበራዊ ሚናው ዕድር በምድር ልንለው እንችላለን፤ብድር በምድር እንደሚባለው ማለት ነው።
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናት ተቋም የአማርኛ መዝገበ ቃላት ዕድር የሚለውን ቃል በአንድ አካባቢ ሰዎች ችግራቸውን በኅብረት ለመወጣት የሚያቋቁሙት የመረዳጃ ማኅበር መሆኑን ይጠቁማል ። በአብዛኛው ለሞት ጊዜ የሚቋቋም ማኅበር፣ ቡድን በሚል ይፈታዋል።
ዕድር በወሎ “ቅሬ” በሚል ሲጠራ በደቡብ ጎንደርና በጎጃም “ጓኝ” በሚል ስያሜ ይታወቃል። እነዚህ በሀዘንና በደስታ ከመረዳዳት ባለፈ ሌቦችና ዘራፊዎችን በማጋለጥ የሰፈር ሰላምን በማስጠበቅ (ዛሬ ከውጪ የመጣ ይመስል ኮሚኒቲ ፖሊሲንግ እንደምንለው ሁሉ) ከፍተኛ ሚና ነበራቸው ።
እድርተኞች ለእድራቸው ትልቅ ግምት አላቸው ። መከራን የማይፈራ ባይኖርም እነሱ ግን ይበልጥ ይፈሩታል ። ቤት የቱንም ያህል ቢሞላ የመከራ ቀንን መሸከም ይቸገራልና ነው እድር የሚገቡት ። እናም የሚበሉት፣ ያማራቸው ይቀራል እንጂ ለእድራቸው የሚከፍሉት አያጡም፤ በእድር ክፍያ ወቅትም እርጅና፣ ህመም ፣ጉዳይ ፣ወዘተ አያስሯቸውም ። ለእድራቸው ሕግ ሙት ናቸው ። አባላቱ ስብሰባ እና ቀብር ላይ መገኘት ይገደዳሉ፤ ስም እየተጠራ አባል መኖሩ አለመኖሩ ይረጋገጣል። አባሉ ካለ አቤት በማለት መኖሩን ያሳውቃል፤ ከሌለ ዜሮ በለው ይባላል። የለም ማለት ነው፤ የቀረው የገንዘብ ቅጣት ይጣልበታል።
የገጠሮቹ እድሮች ከከተሞቹ የሚለዩበት ሁኔታ ያጋጥማል ። አንዱ የሚለያቸው መደበኛ ገንዘብ ያለመክፈላቸው ነው ። በአንዳንድ የገጠር አካባቢዎች ማገዶ ሰብስቦ ምጣድ ጥዶ ብዙ እንጀራ ለመጋገርና ወጥ ለማቅረብና ቶሎ ለማድረስም ይቸግራል፤ዘይት በርበሬ ምስር ሊያጥር ይችላል፤ በመሆኑም አባላቱ እንጀራና ወጥ እንዲያቀርቡ ይመደባሉ፤ ይህንንም ከየቤታቸው ይዘው ለሀዘንተኛው ቤተሰብ ያስረክባሉ።
የተለያየ ባለሙያ የሠራው ወጥ በአንድ ሰታቴ (ትልቅ ድስት )ይገለበጣል። ወጡ የተለያዩ እናቶች ሙያ የተገለጸበት እንደመሆኑ ሲቀየጥ ምን ሊባል እንደሚችል አስቡት ። በራሱ የተመጣጠነ ምግብ ሊሆንም ይችላል ።
ምግቡ እንደየአካባቢው ባህል ከቀብር መልስ ወይም በፊት ለለቀስተኛ ይቀርባል። በአንዳንድ ማህበረሰብ ዘንድ ቀብር ሳይፈጸም ምግብ ፈጽሞ አይበላም፤ በእዚህ የተነሳ መከራው የገጠማቸው የቅርብ ሰዎች የሚጎዱበት ሁኔታም አለ ። በአንዳንድ ማህብረሰብ ዘንድ ግን ይህ የለም፤ ምግብ ተበልቶ ወደ ቀብር ይኬዳል፤ ቀባሪው ወደቤት መመለስ አይጠበቅበትም ።
እድሮች የወንድና የሴት/ የጓዳ/ እድር ተብለውም ይለያሉ ። የወንዶቹ እድር ቀብር አስፈጻሚ ነው፤ መከራ ለደረሰበት የሚያስፈልጉ ቁሳቁስ ያቀርባል ። የጓዳው ደግሞ ምግብ በተራ አዘጋጅቶ የሚያቀርብ ነው ። የጓዳ እድሮች እስከ ሶስት ቀን ድረስ ከለቅሶ ቤቱ አይጠፉም፤ የወንድ እድርተኞችም ድንኳን እስከሚፈርስ ከለቅሶው ቤት አይርቁም። የሚገርም የሥራ ክፍፍል ነው።
የሚገርመኝ ድንኳን ለመጣል የሚደረገው ግብግብ ነው ። እድርተኛው የድንኳን ቁሳቁስ ተሸክሞ ለቅሶ ቤት ያደርሳል፤ ድንኳኑንም ይጥላል። ይሄ ነው ጉዱ ። በድንኳን መጣል ላይ አላውቅም የሚል የለም ። ማለትም አይቻልም። ሁሉም የራሱን ሀሳብ ይሰጣል ። አቤት ያለው መንጫጫት ። መንጫጫት የድንኳን መጣል መገለጫው ነው ማለት ይቻላል ። የዚያን ሁሉ ሰው ጫጫታ ግን በአንድ ድንኳን በመጣል አዋቂ በሆነ ሰው ጸጥ ረጭ ይላል።
የእድርተኛውን ገበና ሸፍነው የቆዩ አንዳንድ እድሮች አሁን እየተፈተኑ ይገኛሉ ። ኑሮው እየከፋና እየከረፋ መጣና ዕድሮቹ ለሀዘንተኛ የሚሆን ገበያውን የሚመጥን በቂ ገንዘብ ለመስጠት አቅም ሲያጥራቸው ይታያል ። አንዳንድ እድሮች እርጅናውም ተጫጭኗቸዋል፤ ዕድሮቹ ራሳቸው እርዳታ የሚሹ ይመስላሉ፤ ለሀዘንተኛ የሚሰጡት ገንዘብ እዚህ ግባ የሚባል አይደለም ።
እርግጥ ነው አንዳንድ ጠንካራ እድሮች አሉ ። አዲስ አበባ ፓስተር አካባቢ የማውቀው ዕድር የትምህርት ቤት ህንጻ ገንብቶ ያከራያል፤ እድሩ ገቢውን በማስፋቱ ለአባላቱ በዓል በሆነ ቁጥር የተወሰነ ገንዘብ ከገቢው ላይ እንዲያገኙ ይደረጋል ። ወፍጮ ቤት አቋቁመው ተጨማሪ ገቢ የሚያገኙም አሉ ። እነዚህ ጥሩ ምሳሌዎች ናቸው ። የሚያወጣውም ይህ መንገድ ነው ።
ዕድሮች አሁን ባሉበት ከቀጠሉ ወደፊት ራሳቸውም እርዳታ የሚሹ ሊሆኑ ይችላሉ ። ይህን ችግር ለማሸነፍ ከእድርተኞች ተጨማሪ ገንዘብ መሰብሰብ ውስጥ ይገቡ ይሆናል ። ካለው የኑሮ ውድነት አኳያ ደግሞ ይህን ማድረግ ይከብዳል ። እናም እድሮች ችግሮቻቸውን እንዲፈቱ እንዲሁም ይበልጥ እንዲሻሻሉ የሚያደርጋቸውን አሰራርመቀየስ ይኖርባቸዋል ።
“ድር ቢያብር አንበሳ ያስር” እንደሚባለው ከፍ ብለን እንደጠቀስነውም ተባብረው ታሪክ የቀየሩ እድሮች አሉ፤ ግን ጥቂት ናቸው ። ከእነዚህ መማር ይገባል። በአክሲዮን መደራጀት፣ ገቢ ሊያስገኙ የሚችሉ የሸማቾች ማህበራትን ማቋቋምና የመሳሰሉትን በማድረግ አባሎቻቸውን ለመደገፍ መስራት ውስጥ ሊገቡ ያስፈልጋል ። ለዚህ ደግሞ የሚመለከታቸው የመንግሥት ተቋማት ሚና ወሳኝ ቢሆንም፣ የእድር አመራሮች ከቆየ አሰራር መውጣትም ያስፈልጋል ።
በእድር በተዋጣው ልክ ነው መረዳዳትና መደጋገፍ ሊኖር የሚችለው። አሁን ባለው የአባላት ወርሐዊ ክፍያ መጪውን የመከራ ጊዜ ወጪን ብቻ አይደለም የአሁኑንም መሸፈን እያቃተ ነው ። እድርተኛው ከእድር አሁን በጣም እየጠቀመ ያለው እንደ ድንኳን ባሉት የእድር ቁሳቁስ ነው ። ገንዘቡ ቀበሩን ለማስፈጸም እያቃተው ነው ። ለቀብር ማስፈጸሚያ መዋጮ ለብቻ እየተደረገ ነው ። ይህን የሚሸከም ሥራ መሰራት አለበት ።
እስከ አሁን እድሮች የሚታሙት ወይም አልሰሩም የሚባሉት አባል ሲታመም፣ ሲቸገር መረዳዳት አልሰሩም በሚል ነው ። በቁም መረዳዳትን ዘለውታል ። ይህን ባልሰሩበት ሁኔታ ነው እንግዲህ የኑሮ ውድነት ሌላ ሥራ ይዞባቸው የመጣው ። ችግሮቻቸውን ሲፈቱ የቆዩት ልዩ መዋጮ በመሰብሰብ ወይም በወርሃዊ መዋጮው ላይ ተጨማሪ በማድረግ ነው ። ይህ ደግሞ ከአፋቸው ከፍለው መዋጮ በሚያደርጉት ላይ ጫና ሊያሳድር ይችላል ። አዲስ መንገድ መከተል ያስፈልጋል ።
አንዳንድ እድሮች አክሲዮን ጭምር እየገዙ በልማት እየተሳተፉ ናቸው፤ አንዳንዶች ደግሞ ህንጻ ሰርተው ለተለያዩ አገልግሎቶች እያከራዩ ገቢ ይሰበስባሉ። ወፍጮ ቤትና የመሳሰሉት ያላቸውም አሉ። በእዚህም አባሎቻቸውን በመከራ ጊዜ ከመርዳት አልፈው በዓመት የተወሰነ ጊዜ ገንዘብ የሚሰጡበት ሁኔታም ይታያል ። ይህ ሊበረታታና ሌሎችም ሊኮርጁት ይገባል ።
ይቤ ከደጃች ውቤ
አዲስ ዘመን ሐምሌ 3/2013