ወጣትነት ለውጥ ናፋቂነት ነው። የአንድ አገር ቀጣይነት ያለው እድገት የሚለካው ባላት ሃብትና ንብረት ብቻ ሳይሆን ያንን ተረክቦ በአደራ ለትውልድ ማስተላለፍ የሚችል ትውልዳዊ ትስስር ሲኖር ነው። ይህንንም እንደ ድልድይ ሆኖ ከአንዱ ትውልድ ወደ ቀጣዩ ትውልድ የሚያስተላልፈው ወጣቱ የህብረተሰብ ክፍል ነው። በማንኛውም አገር፣ ጊዜና ዘመን እያንዳንዱ ተተኪ ትውልድ የአገሩ ወራሽ፣ ተተኪና ተረካቢ፣ ጠባቂና ለሚቀጥለውም ትውልድ የማውረስ፣ የማስተላልፍና የማስረከብ ኃላፊነትና ግዴታ አለበት።
አገርን ከእነ ሙሉ ክብሯ ለሚቀጥለው ትውልድ ማስተላለፍ ከወጣቱ የዜግነት ግዴታዎች ውስጥ አንዱ ነው። አገር በአንድና በሁለት ትውልድ ብቻ የሚቆምና የሚያልፍ ሳይሆን የማያቋርጥ ቀጣይነት ያለው ትውልድ ሁሉ የሚቀባበለው፣ የሚጠብቀው ያለፈውንና የሚመጣውን ትውልድ ሁሉ የያዘና ያቀፈ የአገርና የሕዝብ የታሪክ ሂደት ነው። ወጣት ለአንድ አገር በሦስቱም ዘርፍ ማለትም በማህበራዊ፣ በሥነ ምጣኔ ሃብታዊና በፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ያደርጋል። ለዚህም ነው ወጣት ለአንድ አገር የጀርባ አጥንት ነው የሚባለው።
አንድ ሰው የተሳካለት ሥራ ፈጣሪ (አዲስና የተለየ የቢዝነስ ሃሳብ ወይም ዘዴ ይዞ የተነሣ) ለመሆን፣ የያዘው ሃሳብና ሃሳቡን ተግባራዊ ማድረጊያ ገንዘብ ወሳኝ መሆናቸው አይጠረጠርም። ሆኖም እነዚህ ሁለቱ ብቻ ስራ ፈጣሪው የተሳካለት የቢዝነስ ሰው እንዲሆን አያስችሉትም። የስራ ፈጣሪነት ስኬትን መቀዳጀት እንዲችል ወይም ጉዞው ወደ ስኬት የሚገሰግስ እንዲሆን ዓይነተኛ የሆኑ የሰብዕና መገለጫዎች ያስፈልጉታል። እንደ ስራ ፈጣሪ እነዚህ የሰብዕና መገለጫዎች ወይም ጠባዮች ካሉ ሊዳብሩ፣ ከሌሉን ደግሞ እንደ አዲስ በውስጣችን ኮትኩተን ልናሳድጋቸው ይገባል።
ለዛሬ ይዘን የቀረብነው ከስራ እድል ፈጠራ ድረ ገፅ ያገኘነውን የፍቅርተ አዲስ የስራ እንቅስቃሴ ነው። በአጭር ጊዜ የስፌትና ቅድ ትምህርቶች በመታገዝ የኢትዮጵያን የባህል ልብሶች በአዳዲስ ፈጠራ በማቅረብ በበርካታ የባህል ልብስ አድናቂ ዘንድ ተመራጭ ሆናለች። የመጀመሪያ ዲግሪዋንና የከፍተኛ ትምህርቷን በስነልቦና ጥናት (በሳይኮሎጂ) አጠናቃለች። በተማረችበት ሙያ ለተወሰኑ ዓመታት ከሰራች በኋላ ወደምትወደው የልብስ ስፌትና ቅድ እንዲሁም የልብስ ዲዛይን ፈጠራ ስራ ላይ ሙሉ ትኩረቷን አድርጋ በመስራት ላይ ትገኛለች። የምትሰራቸው ልብሶች የኢትዮጵያን የባህል ልብስ መሰረት ያደረገ ሆኖ በአዲስና በዘመናዊ መልክ የሚሰራ ነው።
ፍቅርተ ለልብስ ቅድና ስፌት የምትጠቀምባቸውን የኢትዮጵያን ባህላዊ ጨርቆች ከሚያመርቱ ሸማኔዎች ጋር ያላት ግንኙነት በስራ ብቻ የተወሰነ አይደለም። ከራስዋ ስኬት አልፋ በሽመና ሙያ ለሚተዳደሩት ቤተሰቦችና ልጆቻቸው ስኬት ትተጋለች። በተለይም በሽመና ስራ ላይ የሚታየውን የህፃናት ጉልበት ብዝበዛን ለመከላከል በስነ-አእምሮ ወይም በስነ-ልቦና ምርምር (ሳይኮሎጂ) ሙያዋ ከፍተኛ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ትገኛለች።
በወጣትነት ዕድሜዋ የሶስት ልጆች እናትና ስኬታማ ሥራ ፈጣሪ መሆን በመቻሏ በዙሪያዋ ያሉ ሰዎች እንደሚገረሙ የምትናገረው ፍቅርተ፤ ‹‹የሠራተኛ እናት ዋናው ትግል በኢኮኖሚ ከማደግ ባለፈ ለልጆቿስ ምን ያህል ጊዜ መስጠት ትችላለች የሚለው ነው›› ትላለች። ሴቶች ካሉባቸው ተደራራቢ የቤተሰብ ኃላፊነቶች መካከል ልጅ ማሳደግ አንዱ ነው። ለበርካታ ሴቶች ወደ ሥራ ቦታ ልጆቻቸውን ይዘው መምጣት የማይመች ሁኔታ አለው። ቤት ትተው ለመምጣትም ቀላል አይሆንም። ሴቶችን ባሉበት በሚመቻቸው ቦታ ሆነው እንዲሰሩ አቅማቸውን ማጎልበት የተሻለ ነው። የራሷን ሥራ ለመሥራት የወሰነችው ለዲዛይን ካላት ፍቅር ባሻገር ለልጆቿ የእናትነት ጊዜዋን እንደፍላጎቷ መስጠት እንዲያስችላት ነው።
በድርጅቷ ውስጥ የሚሰሩ እናቶች በኢኮኖሚ ራሳቸውን እንዲችሉ በጣም ይበረታታሉ። በተለይም ሥራቸውን ልጆቻቸው አጠገብ ሆነው መሥራት እንዲችሉ ማቅረብ የምትችለውን ሁሉ እንደምታቀርብላቸው ዲዛይነር ፍቅርተ ትናገራለች። ፍቅርተ እና ቤተሰቦቿ ዲዛይን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር የተመሰረተው በ2009 ዓ.ም ነው። ወደ እዚህ ሥራ ከመግባቷ በፊት ተምራ ትሰራ የነበረው በዴቨሎፕመንታል ሳይኮሎጂ የሥራ መስከ ሲሆን በዘርፉ የመጀመሪያ እና ሁለተኛ ዲግሪዋን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተቀብላለች። ምንም እንኳን ከልጅነቷ ጀምሮ ‹‹እሷን ተዋት መቆራረጥ ትወዳለች›› እስክትባል ድረስ የዲዛይን እና የስፌት ፍቅሩ ቢኖራትም በስነ-ልቦና ትምህርት እስከመጨረሻው በመዝለቅ አስተማሪ ለመሆን አቅዳ ነበር።
ይሁን እንጂ ካቀደችው ይልቅ የ9ኛ ክፍል ተማሪ ሳለች ጀምሮ በእናቷ የስፌት ማሸን የራሷን ዲዛይን በመሥራት በትምህርት ቤታቸው ውስጥ ይዘጋጁ በነበሩ የፋሽን መድረኮች ላይ ስትሳተፍበት የነበረው የልጅነት ፍላጎቷ አሸንፎ ዛሬ ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ዘመነኛ የባህል ልብሶች ዲዛይነር እና አምራች ለመሆን በቅታለች። ከቀድሞ ሥራዋ ያተረፈችው ገንዘብ ስላልነበራት ሥራውን ለመጀመር ሳታስብ ባለቤቷ በሰጣት 20 ሺህ ብር የመሥሪያ ቦታ ተከራየች። ለስነ-ልቦናው ትምህርት ፍቅሩ ስለነበራት የራሷን ሥራ በጀመረችባቸው ወራት ጊዜ እያመቻቸች ትሠራው ነበር። ንግድ ፍቃድ አውጥታ፣ ሥራ ብላ ባላተኮረችበት ጊዜ የዩኒቨርሲቲ ተማሪ እያለች የዲዛይን ሥራዎቿን በትውውቅ ለአንዳንድ ሰዎች ትሠራ ስለነበር ድርጅቷን በከፈተችበት ወቅት ቀድሞ የገነባችው ትውውቅ ገበያ ለማግኘት አግዟታል።
ድርጅቷን ስትከፍት ምንም ሠራተኛ አልነበራትም። ቀስ እያለች በአዲስ አበባና ጨንቻ አካባቢ ከሚገኙ የሽመና ሠራተኞች እና የህብረት ሥራ ማህበራት ጋር በጋራ መሥራት ጀመረች። አሁን 40 ሠራተኞች አሏት። ከእነዚህ ውስጥ 95 በመቶ የሚሆኑት እናቶች ናቸው። ‹‹እኔ ልጆቼን ለመቅረብ እና ጊዜ ለመስጠት ስል ነውና ይሄንን ሥራ የጀመርኩት እናቶችን ከቤታቸው ሆነው እንዲሰሩ አደርጋለሁ። በርካታ ሴቶች ልጅ ሲወልዱ ከሥራ ይቀራሉ። ኑሮ ደግሞ በአንድ ሰው ገቢ ብቻ በቂ ስለማይሆን በኢኮኖሚ ቤተሰባቸውን ለመደገፍ ወጥተው ይሠራሉ። ልጆች በዚህ ወቅት እንክብካቤ ይጎድልባቸዋል። አለፍ ሲልም ጉዳት ይደርስባቸዋል። ይሄ ደግሞ ለእናቶች በጣም ከባድ ነገር ነው። ለልጆቻቸው ሲሉም ሳይሰሩ ቤት እንዲቀመጡ የሚያደርጋቸው ይህ ነገር ነው። ሊያጋጥሙ ከሚችሉ ሌሎች ችግሮችም በተጨማሪ ህጻናቱን ጡት ለማጥባት እና እናት አጠገባቸው መሆኗ ግድ ነው።›› ትላለች።
ይሄንን ለስነ-ልቦናው ቅርብ በመሆኗ እንዲሁም በዘርፉ ላይ ስትሠራም የእናቶችን ጉዳይ በቅርበት ስለምታውቅ በቀላሉ ትረዳለች። ስለዚህ ልጆቻቸውን አጠገባቸው ሆነው እንዲያሳድጉ እና የሚገጥሟቸውን ችግሮች ለመቀነስ ስትል እሷ ወደ እነሱ ትሄዳለች እንጂ እነሱ ወደ እሷ አይመጡም። የሹራብ ሥራ የሚሠሩት ሴቶች ዲዛይኑ ከወጣላቸው በኋላ በየቤታቸው ሠርተው የሚያስረክቡ ሲሆን የስፌት ሥራ ለሚሰሩት ደግሞ ቤት ሆነው የሚሰሩበት ማሽን ተሰጥቷቸዋል። ብዙ ሰዎች ቁጥጥር ሳይደረግባቸው ውጪ ሆነው ሲሰሩ እምነት የሚጥልባቸው ሰው ባይኖርም እሷ ግን እምነት ትጥልባቸዋለች። በምርት ሥራ ዋናው ነገር ሥራው የትም ይሰራ የትም በጥራትና በጊዜው መሰራትና መድረሱ ነው። ሠራተኞች የሚከፈላቸው ደግሞ ሠርተው ባደረሱት ልክ ነው። ለሷ ዋጋ ያለው ቦታው ሳይሆን ውጤቱ ነው። እንዲያውም በጊዜው በሰዓት ገባችሁ አልገባችሁ ከሚል የቁጥጥር ሥራ እንዳቀለላት ትናገራለች።
ወደ እዚህ ሥራ ስትገባ በግሏ ዲዛይን ሰርታ ልብስ ከመሸጥ በተጨማሪ በዙሪያዋ ላሉ ሰዎችም ራሳቸውን ችለው ማደግ የሚችሉበትን መንገድ ማመቻቸትም ዓላማዋ ነበር። ይህንን አሰራር እና የገበያ ሰንሰለት ለመፍጠር እንዲሁም ለማሰልጠን ረጅም ጊዜ ወስዶባታል። ያልተለመደ ቢሆንም እሷ እየሰራንበት ነው። እርስ በእርስ ተያይዞ ለማደግ መረዳዳት የሚሰራ ቢዝነስ ነው። እሷ ጋር ተቀጥረው የነበሩ አሁን የራሳቸውን ፍቃድ አውጥተው እየሰሩ ያሉ እናቶች አሉ። ከኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በፊት ሥራቸው ጥሩ እየሄደ ነበር። የአገር ውስጥ ገበያው ወቅትን መሰረት ያደረገ በመሆኑ ትኩረቷን በይበልጥ በውጪው ገበያ ላይ ነበር። ካፒታሏም ወደ አንድ ነጥብ አምስት ሚሊየን ብር ማሳደግ ችላም ነበር። ይሁን እንጂ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ወደ አገር ውስጥ ከገባ በኋላ ትልቅ ኢኮኖሚያዊ ተፅዕኖ አሳድሮባታል።
ባለፈው ዓመት የካቲት ወር ላይ ከፈረንሳይ ተቀብላ የመጣችውን ትልቅ ትዕዛዝ ጨምሮ ብዙ የውጭ ገበያ ምርቶች ተቋርጠውባታል። በአገር ውስጥም ቢሆን ወቅትን ጠብቆ ይመጣ የነበረው የሰርግ ሥራ በኮቪድ -19 ስርጭት ምክንያት በርካታ መርሃ ግብሮች በመሰረዛቸው የሱቅ ኪራይ ወጪን እንኳን መሸፈን ባለመቻሏ በአዲስ አበባ ቦሌ አካባቢ የሚገኘውን ሱቄን ለመዝጋት ተገዳለች። ወቅቱ ለእሷ በጣም አስደንጋጭ ጊዜ ነበር። ከሚያሳድረው ኢኮኖሚያዊ ጫና በተጨማሪ የራሱ የሆነ የስነልቦና ተፅዕኖ ነበረው። በተለይ የፋሽኑ ኢንዱስትሪ እጅግ ሰፊ ሰንሰለት ያለው በመሆኑ በጣም የተጎዳ ነበር፤ እሷን ጨምሮ ሌሎች በዘርፉ ላይ የሚገኙ ሰዎች ለራሳቸው መሆን እና በልተው ማደር ላይከብዳቸው ይችላል። ነገር ግን የጠላፊዎች እና የሽመና ሠራተኞች ሥራ ግን ሙሉ ለሙሉ ተቋርጦ ነበር። ምን ያህል ሊከብድ እንደሚችል ማሰብ አያቅትም። ከጊዜው ጋር ተስማምታ ሥራዋን ማስቀጠል እንዳለባት የገባት ፍቅርተ የወሰደችው ፈጣን እርምጃ ነበር። እሱም በጊዜው የሚያስፈልጉትን የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብሎችን ባላት ገንዘብ ተጠቅማ መሥራት ነበር።
ያሉኝን ሠራተኞች ሳልቀንስ ተጨማሪ የሥራ ዕድል ፈጥሬ እና ማሽኖችን ጨምሬ የማስክ ሥራዬን አጠናክሬያለሁ። የኮሮና ቫይረስ ባይጠፋም እንኳን ሰው መልበሱን አያቆምም። የሥራ ፈጣሪነት ዋናው መለኪያ ከክስቶች ጋር ተላምዶ እና ፈተናዎችን ተጋፍጦ ማምለጫ መንገድ ማዘጋጀትና የሥራ ማስቀጠያ ዘዴን መፈለግ ነው። ለሀገር ውስጥ ገበያ የሰርግ ልብሶች አዋጪ አለመሆናቸውን ስለተረዳሁ ዕለት ተዕለት መለበስ የሚችሉና ዋጋቸው ተመጣጣኝ የሆኑ ዘመነኛ የባህል ልብሶችን ለማምረት ዕቅድ አለኝ። የፋሽን መድረኮች መዘጋጀት ባይችሉ እንኳን ሰዎች ልብሶቻችንን ኢንትርኔት ላይ መግዛት ይችላሉ። አሁን እያመረትኩ ካለው የአፍና የአፍንጫ መሽፈኛ ጭምብል ሥራ በተጨማሪ የተቋቋምኩለትን ዓላማ እንዴት ጎን ለጎን ማስቀጠል እንዳለብኝ አቅጄ እየሰራሁ ነው።›› ትላለች።
መርድ ክፍሉ
አዲስ ዘመን ሰኔ 27/2013