ሠላም ውድ የአዲስ ዘመን ጋዜጣ አንባቢያን እንደምን ሰነበታችሁ። ለዛሬ ይዘንላችሁ በቀረብነው የሳምንቱን በታሪክ አምዳችን ቀዳማይ አጼ ኃይለሥላሴ ኢትዮጵያ በፋሽስት ጣልያን ወረራ እንደተፈጸመባት በመጥቀስ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጉባዔ ጉዳዩን አይቶ ፍትሃዊ ውሳኔ እንዲያሳልፍ ላቀረበችው ጥያቄ ድርጅቱ ያሳለፈውን ኢ ፍትሃዊ ውሳኔ በመቃወም ያሰሙትን አቤቱታና የውሳኔውን ከፍተኛ የድምጽ አሰጣጥ ሂደት የምናስቃኛችሁ ይሆናል።
የፋሽቶቹ መሪ ቤኒቶ ሙሶሊኒ ወደ ስልጣን ሲመጣ እንደ ሌሎቹ የአውሮፓ ኃያላን ጣሊያንን ባለ ቅኝ ግዛት ለማድረግ ክፉ ሃሳብ አደረበት። ለዚህ ደግሞ በአፍሪካ አህጉር ነፃነቷን ጠብቃ የዘለቀችውን ኢትዮጵያን አንድም የአድዋው ሽንፈት ቂም በቀል መወጫ፤ በሌላም በኩል የቅኝ ግዛት ረሃቡ ማስታገሻ አድርጐ መረጣት።
ኢትዮጵያን ለመውረር በሰሜን ኢትዮጵያ በኩል ሲገባ ኢትዮጵያውያን ወረራውን ለመመከት ከፍተኛ መስዋእትነት ከፍለዋል። ይሁንና የመርዝ ጋዝ ጭምር ዘመናዊ መሳሪያ የታጠቀው የጣልያን ወራሪ ሀይል በኢትዮጵያውያን ላይ የተከለከለውን የመርዝ ጋዝ ጭምር በመጠቀም ዜጎችን በመጨፍጨፍ ሀገሪቱን በወረራ ይይዛል። ይህን ተከትሎም አጼ ኃይለሥላሴ ወደ ውጪ ሀገር በስደት ይሄዳሉ።
ኢትዮጵያ በፋሽስት ጣሊያን በ1928 ዓ.ም እስከ 1933 ዓ.ም ድረስ በተወረረችበት ወቅት ኢትዮጵያውያን ፋሽስቶቹን አሻፈረኝ ብለው በዱር በገደል ተጋድሎ እንዳደረጉ ሁሉ በዲፕሎማሲውም መስክ ከፍተኛ ተጋድሎ ተደርጓል። በወቅቱም የመንግሥታቱ ማሕበር በጄኔቭ ስዊዘርላንድ ባካሄደው ጉባዔ የፋሽስት ጣልያንን ወረራ አስመልከቶ ኢ ፍትሃዊ ውሳኔ አሳልፎ ነበር። በጉባኤው ላይ የተገኙት የሀገሪቱ ንጉስ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ውሳኔው ኢፍትሃዊ መሆኑን በመግለጽ የኢትዮጵያን ድምጽ በንግግር ያሰሙት ከ85 ዓመታት በፊት በዚህ ሳምንት ሰኔ 23 ቀን 1928 ዓ.ም ነበር።
አፄ ኃይለሥላሴ በጄኔቭ የመንግስታቱ ማህበር ለያኔው ሊግ ኦፍ ኔሽንስ አቤት ባሉበት ወቅት ፋሽስት ጣልያን በኢትዮጵያ ላይ ወረራ ከፈጸመች ስምንተኛ ወሩ አስቆጥሮ ነበር። ንጉሠ ነገስቱም የአገራቸውን አቤቱታ ለማሠማት ወደ ጉባኤው “አትሮኖስ” እንደቀረቡ በብዛት ወደዛው የገቡ ናቸው የተባሉ የጣሊያን ጋዜጠኞች በፉጨትና በሁካታ ንግግራቸውን አወኩት። ቱማታ ፈጠሩ።
ንጉሡ “ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ” በሚል ርዕስ ባሳተሙት መጽሐፋቸው በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ ሲገልጹ፤ “…ሰኔ 23 ቀን 1928 ዓ.ም የ52 መንግሥታት እንደራሴዎች በተሰበሰቡበት ቤት ገብተን አሳባችንን ለመናገር ቀጠሮ ተደርጎልን ነበርና በቀጠሮ ቀን ሄደን በማንበቢያው ስፍራ ስንቆም ለወሬ የመጡ ኢጣሊያኖች ንግግራችንን ለማሰናከልና እንዳይሰማ ለማድረግ ሲሉ እያከታተሉ ያፏጩ ጀመር። በዚህ ጊዜ የሩማኒያው መልዕክተኛ ሙሴ ቲቱሌስኪ “ስለ ፍርድ ስትል እነዚህን አውሬዎች ዝም አሰኝ” ብሎ ለጉባኤው ፕሬዚዳንት ለሙሴ ቫን ዚላንድ አመለከተ። የጉባኤውም ፕሬዚዳንት ኢጣሊያኖች በብዙ መንግሥታት እንደራሴዎች ፊት የብልግና ሥራ መስራታቸውን አይቶ ዘበኞች በግድ እንዲያስወጧቸው ስላዘዘ እየያዙ አስወጧቸው። …” ብለዋል።
በጊዜው ምንም እንኳን ክስተቱ አስናዋሪ ቢሆንም፤ ንጉስ ነገስቱ ተስፋ አልቆረጡም። አዳራሹ ፀጥ እስኪልላቸው ታገሱ። ከዚህ በኋላ በአማርኛ ቋንቋ ያነበቡት ወዲያው በፈረንሳይኛና በእንግሊዝኛ እየተተረጎመ ጉባኤያተኛው ሁሉ እንዲሰማው ተደረገ።
ንግግራቸውንም “እኔ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት የዛሬ ስምንት ወር አምሳ ሁለት መንግሥታት የዓለምን መንግሥታት ሕግ የተላለፈ የአጥቂነት ጦርነት በኢትዮጵያ ላይ መደረጉን አረጋግጠው ካስታወቁ በኋላ ለህዝቤ ይደረግለታል ብለው ቃል የገቡለትን እርዳታና የሚገባውንም ትክክለኛ ፍርድ ለመጠየቅ ዛሬ ከዚህ ቀርቤያለሁ። ለእነዚህም 52 መንግሥታት የኢትዮጵያን ህዝብ አቤቱታ ለማቅረብ ከንጉሠ ነገሥቱ የሚበልጥ ሌላ ሰው አይገኝም። የዓለምን ሰላምና የአገሮችን ነጻነት ለማስከበር ከፍተኛ የቃል ኪዳን አደራ ለተጣለበት የመንግሥታት ማህበር የአንድ አባል አገር መሪ የሆነ ንጉሠ ነገሥት ወይም ፕሬዚዳንት ሌላው አባል መንግሥት በጦር ኃይል ተደራጅቶ በሕዝቡ ላይ ስለአደረሰበት አሰቃቂ የሆነ እልቂት በዚህ ጉባዔ ሲናገር ምናልባት ዛሬ መጀመሩ ነው›› በማለት ነው የጀመሩት ።
ንጉሰ ነገስቱ በመቀጠልም ‹‹ከብዙ ሺህ ዓመታት ጀምሮ ነጻነቱን ጠብቆ የኖረውን የአገሬን የኢትዮጵያ ሕዝብ፤ በአሁኑ ሰዓት የጣሊያን መንግሥት ቅኝ አድርጎ ለመግዛት በጦር ኃይልና በመርዝ ጋዝ የሚፈጽምበትን ግፍና ጭካኔ፤ ከዚህ ቀደም በሰለጠነው ዓለም ውስጥ ደርሶ ያልታየና ተወዳዳሪ የማይገኝለት መሆኑን የምገልጽላችሁ እጅግ በመረረ የኀዘን ስሜት ነው›› ብለዋል።
የጣሊያን መንግሥት ካለፈው አንድ ዓመት ተኩል ጀምሮ በኢትዮጵያና በሕዝቧ ላይ ሲወስድ የቆየው ሕገ ወጥ እርምጃ፤ ምን ያህል አሳሳቢና ምን ያህል አደገኛ እንደሆነ፤ በየጊዜው ለመንግሥታቱ ማህበር ያመለከቱባቸው ሰነዶች፤ በጽህፈት ቤቱ ተመዝግበው የሚገኙ መሆናቸውንም አስታወሰዋል ።
ሆኖም በዛሬው እለት የ52 መንግሥታት እንደራሴዎች የኢትዮጵያን አቤቱታ ሰምታችሁ ፍርዳችሁን ለመስጠት ስለተሰበሰባችሁ፤ የወልወል ግጭት ከተፈጠረበት ጊዜ አንስቶ እስከዛሬ ድረስ የጣሊያን መንግሥት በአገሬና በሕዝቤ ላይ የፈጸማቸውን ዋና ዋና ግፍና በደሎች እገልጽላችሁ ዘንድ እዚህ ተገኝቻለሁ።” በማለት በጉባኤው ፊት አቤቱታቸውን አቅርበዋል።
ንጉሡ ከወረራው መጀመሪያ አንስቶ እስከዚያ ጊዜ ድረስ የፋሽስት ኃይሎች በኢትዮጵያውያን ላይ ያደረሱት ጥፋትና ውድመት ሕሊና ከሚቀበለው በላይ መሆኑን አስረዱ። ፋሽስቶች ከዘመናዊ የጦር መሳሪያ በተጨማሪ ኢትዮጵያውያንን ወታደር ከሲቪል ሳይሉ፤ ሕፃን አዛውንት፤ ሴት ወንድ ሳይለዩ በተከለከሉ የጦር መሣሪያዎችና በመርዝ ጋዝ እየፈጁ መሆናቸውን አመለከቱ።
ፋሽስቶቹ በአገሪቱ ላይ ሞት እያዘነቡባት እንደሆነና ሰውን እየፈጁና ከብቱን እየረፈረፉት፤ ወንዝ አፈሩን፤ ዙሪያ ገባውን እንደመረዙትም አመለከቱ። ኢትዮጵያ እንደ ብዙዎቹ ሉዓላዊ አገሮች የዘመኑ የመንግስታቱ ማህበር /ሊግ ኦፍ ኔሽንስ/ አባል ስትሆን የጋራ ደህንነት ማስጠበቂያ ዋስትና ይሆነኛል ብላ እንደነበርም አስታወሱ።
አንዲት ነፃ የማህበሩ አባል አገር የጉልበተኛ ወራሪ ሰለባ ስትሆን ዝም መባሉ የድርጅቱ ቃል ኪዳን የት ገባ ሲሉም ሞገቱ። ኢትዮጵያ የራሷን ዘመናዊ አጥፊና ደምሳሽ መሳሪያ ከምትሠራው ፋሽስት ጣሊያን እኩል ታይታ የጦር መሳሪያ ስንቅና ትጥቅ እንዳታገኝ ያደረጉትን የድርጅቱን ባለ አቅሞች ፍርደ ገምድልነት ያለ አንዳች ማመንታት በንግግራቸው አወገዙ።
ኢትዮጵያ ተራ ጠመንጃዎችን እንኳ እንዳታገኝ ሲደረግ የጣሊያን ሠራዊትና የጦር መሳሪያ ስንቅና ትጥቅ የጫኑ መርከቦች ሲዊዝ ካናልን ሲያቋርጡ ከልካይ ተቆጣጣሪ የሌለባቸው መሆኑን በብርቱ ኮነኑት። የድርጅቱ አባል አገሮች በቃል ኪዳናቸው መሠረት ኢትዮጵያ ከጉልበተኛ የፋሽስት ወረራ ራሷን እንድትከላከል በመርዳት ቃላቸውን እንዲያከብሩ ጠየቁ።
ታላላቆቹ የሊጉ አባል አገሮች ይሄን ካላደረጉ አንድ ቀን የኢትዮጵያ እጣ እንደሚደርስባቸው በዚያው ንግግራቸው ተነበዩ። እንዳሉትም ሆነ። አውሮፓ በ2ኛው የዓለም ጦርነት ተናጠች። ይህም ነብይ ያሰኛቸውና እስካሁንም ድረስ በርካቶች የሚደነቁበት ትንቢታዊ መልዕክት እንደሆነ ይነገራል።
“… ዛሬ ባለንበት ሰዓት ከሁሉ ይበልጥ የዓለምን ሕዝብ እጅግ ሊያስጨንቀውና ሊያሳስበው የሚችለው፤ የዓለም መንግሥታት ተስማምተው ለሰላም የሚያወጧቸውን ሕጎች፤ በጉልበትና በማን አለብኝነት መንፈስ እየተነሱ የሚደመስሱ መሪዎች መፈጠራቸው ነው›› ሲሉ ገልጸዋል። በዚህም አኳኋን የፋሽስት መንግሥት ዛሬ በኢትዮጵያ ላይ የሚፈጽመውን ግፍ ነገ በሌሎች ሀገሮች ላይ ለማድረግ ምን ያግደዋል? ተብሎ የሚቀርበው ጥያቄ ነው። ለዚህም አስጨናቂ ጥያቄ ዛሬ መልስ ካልተገኘለትና አጥቂዎችን ለመቋቋም ተገቢው እርምጃ ካልተወሰደ፤ አደጋው በድሀ አገሮች ላይ ተወስኖ የሚቀር ሳይሆን፤ ታላላቆቹ መንግሥታት እንደሚደርስባቸው ሊያስቡበት ይገባል። … ከሥነ ፍጥረት ሕግና ከሰብዓዊ መንፈስ ውጪ፤ ያ ሁሉ አሰቃቂ ዕልቂት ቢደርስበትም፤ ሰላማዊና ሃይማኖተኛ የሆነው ያገሬ የኢትዮጵያ ሕዝብ፤ ለነጻነት የሚያደርገው ተጋድሎ እስከ ዕለተ ሞቱ የጠነከረ ስለሆነ፤ በየጫካው በዱር በገደሉና በየበረሀው እየተዘዋወረ በመዋጋት፤ ጠላቱን ማስጨነቅ አላቋረጠም ሲሉም አብራርተዋል።
እኔም በኢትዮጵያ ግዛት ውስጥ ጠላት ለመያዝ ሞክሮ ባቃተው በአንድ ልዩ ቦታ፤ አዲስ አበባ ያለውን መንግሥቴን ካዛወርኩ በኋላ ነው ወደ ጄኔቭ የመጣሁት፤ እውነትን ብቻ ተመርኩዤ አቤቱታዬን ለእናንተ ለማመልከትና የመንግሥታት ማህበርን እርዳታ አግኝቼ የነጻነት ትግሌን ወደምቀጥልበት ቦታ ለመሄድ መሆኑን እንድታውቁልኝ እፈልጋለሁ:: ስለዚህ በንግግሬ መደምደሚያ ላይ የምጠይቃችሁ፤ ለሕዝቤ ምን ይዤለት እንደምመለስ መልሳችሁን እንድትሰጡኝ ነው።” ሲሉ ለህዝባቸው የሚገልጹትን ምላሽ እንዲያሳውቋቸው ጠይቀዋል።
ቀዳማዊ አጼ ኃይለሥላሴ ንግግራቸውን ለቋጩበት ጥያቄ ከመንግሥታቱ ማህበር ያገኙት ምላሽ ግን ልብ ሰባሪ ነበር። አምባሳደር ዘውዴ ረታ “የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግሥት” በተሰኘ መጽሐፋቸው የ16ኛው የመንግሥታቱ ማህበር ጉባኤ ሊቀ መንበር ቫን ዚላንድ በኢትዮጵያ ግዛት አሁን ያለው የፋሽስት ይዞታ በይፋ እንዲወገዝና ለወደፊትም ምንም አይነት እውቅና እንዳይሰጠው የሚጠይቀውን የሀገራችንን የመጀመሪያ ረቂቅ ውሳኔ ለጉባኤው አላቀርብም ብሎ መከልከሉን ጽፈውታል። የፋሽስት መንግሥት በሊግ ኦፍ ኔሽን ተፈርዶበት የነበረው የኢኮኖሚ ጭቆና / ማዕቀብ እንዲነሳ ተወሰነለት:: የጣሊያን ፋሽስት በወረራ የያዘው ይዞታ እውቅና እንዳያገኝ ኢትዮጵያ ያቀረበችው ጥያቄ በጉባኤው ውድቅ ተደረገ ሲሉም በመጽሃፋቸው አመልክተዋል።
ምንም እንኳን ጉባዔው የሚጠበቀውን በጎ ምላሽ ባይሰጥም፤ በዘመኑ አፄ ኃይለሥላሴ በጄኔቭ ባሠሙት ፀረ ፋሽስት ንግግር ታይም መፅሄት ‹‹የዓመቱ ታላቅ ሰው›› ያላቸው መሆኑ በታሪክ ሰፍሮ ይገኛል።
አዲሱ ገረመው
አዲስ ዘመን ሰኔ 27/2013