መርድ ክፍሉ
በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ወጣቱ ማህበረሰባዊ ተሳትፎ እያደረገ ሲሆን አቅመ ደካሞችን በማገዝ ረገድ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ነው። የመረዳዳትና የመደጋገፍ ባህል በሁሉም ቦታዎች እየተቀጣጠለ ሲሆን በተለይ በተለያዩ ምክንያቶች የተፈናቀሉ ወገኖችን በመርዳት ወጣቱ ግንባር ቀደም ነው። መንግስትም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የተቸገሩትን በማብላትና ቤታቸውን በመጠገን ውጤታማ ስራ እያከናወነ ይገኛል። ይህም እንቅስቃሴ በበዓላት ብቻ ሳይሆን በሌሎችም ወቅቶች ሊሰራ የሚገባው ጉዳይ ነው። የሲቪክ ማህበራት አዋጅ ከተሻሻለ በኋላ በሁሉም ቦታዎች በጎ አድራጎት ማህበራት እየተበራከቱ ይገኛሉ። በተለይ የህብረተሰቡን ችግር ከስሩ ከመፍታት አኳያ ውጤታማ ስራ እያከናወኑ ይገኛሉ።
ለዛሬ የመረጥነው በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል፣ በከንባታና ጠንባሮ ዞን፣ በዱራሜ ከተማ የሚገኘው ህፃናትን፣ ተማሪዎችንና የጎዳና ልጆችን እየደገፈ ያለው ሄኖን የበጎ አድራጎት ማህበርን ነው። ማህበሩ ከተመሰረተ ቅርብ ጊዜ ቢሆንም በርካታ ስራዎችን እየሰራ ሲሆን፤ አቅም የሌላቸውን ተማሪዎችም እየደገፈ ይገኛል። ከምስረታው ጀምሮ እስካሁን እንቅፋቶች ቢያጋጥሙትም ሁሉንም ተቋቁሞ ድጋፍ ማድረጉን ቀጥሏል። ስለማህበሩ አጠቃላይ የስራ እንቅስቃሴ ከማህበሩ መስራችና ስራ አስኪያጅ አቶ አውታሩ ተስፋዬ ጋር ቆይታ አድርገናል። መልካም ንባብ።
የማህበሩ አመሰራረትና ያከናወናቸው ተግባራት
አቶ አውታሩ ይኖርበት በነበሩበት አካባቢ ላይ ያሉ አቅመ ደካሞች የእለት ጉርሳቸውን ማሟላት አለመቻልና ልጆቻቸውን ትምህርት ቤት ለማስተማር አቅም ማጣታቸውን በመመልከታቸው ድጋፍ ለማድረግ ሀሳብ መጣላቸው። ከዛም በራሳቸው አቅም ሊሰሩ የሚችሉ የትምህርት ቁሳቁሶችን በማሟላት፣ በዓላትን ከእነሱ ጋር በማሳለፍና ለበዓላት የሚሆኑ ነገሮችን በማቅረብ ማገዝ፤ በሂደትም ማህበር ለመመስረት የሚያስችላቸውን መሰረት ጣሉ። ከዛም ማህበሩ 2008 ዓ.ም ላይ ለመመስረት ሀሳብ መጣ። በ2009 ዓ.ም ላይ ሀሳቡን በማሳደግ ጓደኞቻቸውንና ድጋፍ ሊያደርጉ የሚችሉ ሰዎችን ማነጋገር ጀመሩ። ስራቸውን ሲጀምሩ ለሶስት ልጆች የመማሪያ ደብተርና እስክርቢቶ በመግዛትና በዓላትን አብሮ በማሳለፍ ነበር። በዛው ዓመት ድጋፋቸውን በማሳደግ ለስድስት ልጆች የመማሪያ ቁሳቁስ ገዝተው ከመስጠት ባለፈም በዓላትን አብረው አሳልፈዋል።
2010 ዓ.ም ላይ ጓደኞቻቸውን በማሰባሰብ ስድስት ሆነው ስራውን ማከናወን ጀመሩ። በዚህ ውስጥ ደግሞ የተለያዩ ውጣ ውረዶች ያጋጠሟቸው ሲሆን ሁሉንም ችለው ስራቸውን መስራት ጀመሩ። ስራን የሚሰሩት ወጣቶች ቁጥር እየጨመረ ሲመጣ አዳዲሰ ስራዎችን ለማከናወን ድፍረት አገኙ። ደብተርና እስክርቢቶ፣ አልባሳት፣ ምግብ እንዲሁም ሌሎች ነገሮችን መደገፍ ጀመሩ። በ2011 ዓ.ም ላይ ይሰሩ የነበረውን ስራ አጠናክረው የቀጠሉበት ሲሆን አቅም ያላቸውን ልጆች እራሳቸውን ማስተዳደር አለባቸው በሚል ለአስራ ስድስት ጎዳና ላይ ለሚኖሩ ልጆች 14 ጋሪና ሁለት የሊስትሮ እቃ በመግዛት ወደ ስራ እንዲገቡ አደረጉ። ልጆቹም የተሰጣቸውን የስራ እቃ ይዘው በመንቀሳቀሳቸው መስራት ጀመሩ፤ ውጤት ማሳየትም ጀመሩ።
ማህበሩን ህጋዊ ሰውነት አሰጥቶ ለመንቀሳቀስ ከባድ ችግር አጋጥሟቸው ቢሆንም እነዛን ሁሉ በጥረትና በትእግስት አሳልፈዋል። ከዛ በኋላ በሚኖሩበት ዱራሜ ከተማ በይፋ መንቀሳቀስ ጀመሩ።
በ2011 ዓ.ም በማህበር ደረጃ የደም ልገሳዎችን፣ የፅዳት ዘመቻ፣ የችግኝ ተከላና መንከባከብ፤ እንዲሁም ከተማውን የማስዋብ ስራዎችን አከናውኗል። በ2012 ዓ.ም ላይ ጋሪና የሊስትሮ እቃ ተሰጥቷቸው ስራ የጀመሩ ልጆች የስራ እንቅስቃሴ አበረታች ስለነበር ተግባሩን ሰፋ አድርጎ ለማከናወን ድጋፍ ሊያደርጉ የሚችሉ ሰዎችን ማነጋገር ጀመሩ። በዛው ዓመት ቤታቸው ለፈረሰባቸው አቅመ ደካሞች የቤት እድሳት አከናወኑ። የተለያዩ የሃይማኖት ተቋማትና ባለሀብቶች ድጋፍ ያደረጉባቸው ሁኔታ ባለ 30፣ 40 እና 60 ቆርቆሮ ቤቶች ተሰርተው ለአቅመ ደካማዎች ተሰጡ።
ማህበሩ እየሰራቸው በመጣቸው ስራዎች ህብረተሰቡ እምነት እየጣለበት መጣ። ቀደም ብሎ በማህበሩ የተሰባሰቡት ሰዎች ለሌላ ዓላማ ነው የሚሉ አስተያየቶች ነበሩ። ገንዘብ የሚሰበስቡት ለራሳቸውም ለማዋል ነው የሚልም አመለካከቶች ነበሩ። እነዚህን ነገሮች ወደ ጎን በመተው ስራ ላይ ብቻ በማተኮሩ እምነት ማግኘት ችለዋል። የሰበሰቡትን ሀብት ጥቅም ላይ እያዋሉ ነው ወይ? የሚለው ሀሳብ በስፋት ህብረተሰቡ ውስጥ በመግባቱ ቤቶችን ማደስና የፅዳትና የችግኝ ተከላ ስራዎችን በተሳካ ሁኔታ ማከናወን ተችሏል።
የኮቪድ 19 ወረርሽን ወደ አገሪቱ ከገባ በኋላ ማህበሩ ህብረተሰቡን በማስተማር ረገድ ስራዎች ሰርቷል። በከንባታ ጠንባሮ ዞን፣ በሀድያ ዞን እንዲሁም በሀላባ ዞን ከአንድ ሳምንት በላይ ለሚሆን ጊዜ መኪና በመከራየት የማስተማር ስራ፣ በራሪ ወረቀቶችን በመበተን እንዲሁም በሌሎች ስራዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ ተከናውኗል። በከንባታ ጠንባሮ ዞን በአምስት ወረዳና በአምስት ከተማ አስተዳደር ውስጥ፣ በሀላባና በሀድያ ዞኖች በተመሳሳይ የግንዛቤ ስራዎች ማከናወን ተችሏል። በ2013 ዓ.ም ላይ በግጭት ምክንያት ተፈናቅለው ለመጡ ለአራት ልጆች ሶስት ጋሪ አንድ የሊስትሮ እቃ ተገዝቶ ተሰጥቷቸል። የመማሪያ ቁሰቁስ፣ በዓላትን ከጎዳና ልጆች ጋር ማሳለፍና አረጋውያንን መጦር የማህበሩ የዘወትር ተግባር ሆነ። በዚሁ መሰረትም በ2013 ዓ.ም ላይ የሁለት አቅመ ደካማዎችን ቤት ማደስ፤ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችን አጠናክሮ መስራት ተችሏል።
ማህበሩ ከደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል ጠቅላይ አቃቤ ህግ ቢሮ ህዳር 1 ቀን 2013 ዓ.ም ክልል አቀፍ ህጋዊ ፈቃድ ማግኘት ቻለ። ከዚህ በኋላ ቢሮ መከራየትና ህጋዊ አሰራሮችን በመከተል፣ ደረሰኝ በማዘጋጀት ሀብት የማሰባሰብ ስራ ተጀመረ። የአባላት ቁጥርም 57 መደበኛ አባላትና 74 የክብር አባላትን ማፍራት ችሏል።
የህብረተሰቡ አቀባበል
ህብረተሰቡ ማህበሩ ስራዎችን በጀመረበት አካባቢ ለመቀበል ከብዶት ነበር። ሰዎች በተዛባ አመለካከት ውስጥ ሆነው የማህበሩን ስራ ችላ በማለት ያልፉት ሁሉ ነበር። በጊዜ ሂደትም ህብረተሰቡ የማህበሩን ስራ ሲመለከት እገዛ ወደ ማድረግ ገባ። በአሁን ወቅት ማህበሩ የተሻለ ስምና አቀባበል አለው፤ ህብረተሰቡም በተሻለ መንገድ ማህበሩን እየተረዳ ይገኛል። ማህበሩ ከማንኛውም የመንግስት አስተዳደር ምንም አይነት የገንዘብ ድጋፍ አላገኘም። በቅርቡ ፕሮግራም ለማዘጋጀት ውይይት የተደረገ ቢሆንም እስካሁን ድረስ ምንም አይነት ድጋፍ ከአስተዳደሩ አልተገኘም። እስካሁን ባለለሀብቱንና የሃይማኖት ተቋማት ከማህበሩ ጎን ሆነው ድጋፍ እያደረጉ፤ ግለሰቦችም ለማህበሩ አጋርነታቸውን በማሳየት ላይ ናቸው።
ማህበሩን ያጋጠሙ ችግሮች
በድሀው ስም ሀብት የሚያሰባስቡ፣ ከአፉም ነጥቀው የሚበሉ ግለሰቦችና ተቋማት በመኖራቸው ምክንያት “ማህበሩ የሚሰበስበውን ገንዘብ ምን ላይ እያዋለ ነው?” የሚል ጥያቄ ከህብረተሰቡ ይቀርብ ነበር። በተለያዩ መንገዶች የማህበሩን እንቅስቃሴ የሚመለከቱ ጉዳዮች ላይም ሀሳብ ይሰነዘር ነበር። በዚህም ማህበሩ በህብረተሰቡ ዘንድ ተዓማኒነትን የማጣት ነገር አጋጥሞት ነበር። ለማህበሩ የገንዘብ ድጋፍ የሚያደርጉ ሰዎች የሚያነሱት ጥያቄ ከባድ ነበር። ይህም ማህበሩን ከባድ ሁኔታዎችን እንዲጋፈጥ አድርጎት ነበር። አባላቱ በወጣትነት እድሜ ላይ የሚገኙ በመሆናቸው ችግሮቹን በትእግስት በማለፍ ማህበሩ አሁን ያለበት ደረጃ ላይ ለመድረስ ተችሏል።
የማህበሩ ቀጣይ እቅድ
ማህበሩ በቀጣይ በርካታ ስራዎችን ለማከናወን እቅድ ይዟል። ‹‹ሄኖን›› ቀደም ብለው ሲሰሩ የነበሩ ስራዎችን በማስቀጠል፤ የተለያዩ አልባሳትን ለመስጠትና የምግብ ዋስትናቸው ላልተረጋገጠላቸው ለማረጋገጥ፣ ጎዳና ላይ የሚኖሩ ልጆችን ለማንሳት፣ የፅዳት ዘመቻዎችን ለማካሄድና የደም ልገሳ ለማድረግ እቅድ ይዟል። በተጨማሪም ማህበሩ ሲመሰረት በዋነኝነት ድጋፍ ሲያደርግላቸው የነበሩ ሰዎች እራሳቸውን ማስተዳደር እንዲችሉ የማድረግ፣ ሌሎችም የሰው እጅ ከመጠበቅና የሰው ፊት ከማየት በራሳቸው ሰርተው የሚኖሩበት እድል የመፍጠር ሀሳብ ነበር፤ እሱን እውን ለማድረግም እየተሰራ ይገኛል።
በጎዳና ላይ ለሚገኙ ልጆች የጋሪና የሊስትሮ እቃ ገዝቶ በመስጠት እራሳቸውን እንዲያስተዳድሩ የማድረጉ ስራን የማስቀጠል እቅድ አለ። ከዚህ ጋር በተያያዘ በቀጣይ ዓመት ተዘዋዋሪ ፈንድ በማዘጋጀት ውጤታማ ስራ ለማከናወን ሀሳብ አለ። ለምሳሌ ለአንድ እናት አምስት ሺህ ብር በመስጠት ምንም አይነት ወለድ ሳይኖረው ሰርተው የሚከፍሉበት መንገድ ለመፍጠር ማህበሩ ሀሳብ አለው። ብድሩ የሚሰጣቸው ሰዎች ሰርተው እንዲከፍሉ በማድረግ ሌሎችም እንዲጠቀሙ ለማስቻል ያግዛል። ይህን ስራ ለማሳካት ከቀበሌና ከህግ ክፍሎች ጋር በመነጋገር በህጋዊ መንገድ ከህዝብ የሚሰበሰበው ገንዘብ ጥቅም ላይ እንዲውል ለማድረግ እየተሰራ ነው።
ሌላው ደግሞ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመርቀው መጥተው ስራ በማጣት በከፋ ድህነት ውስጥ የሚገኙ ወጣቶችን በማደራጀትና ስልጠና በመስጠት የመስሪያ ቦታ እንዲመቻችላቸው በማድረግ እንዲሁም ብድር እንዲያገኙ በማመቻቸት ወደ ስራ እንዲገቡ ለማድረግ ማህበሩ እቅድ አለው። የልህቀት ማዕከል ለመገንባት ውጥን የተቀመጠ ሲሆን በማዕከሉ ከውጭ የሚገቡ ማሽነሪዎችን፣ ለግብርናና ለህክምና የሚውሉ እቃዎችን ከመገጣጠም ባለፈ በአገር ውስጥ በሚገኙ ቴክኖሎጂ ፈጣሪዎች ወደ ስራ የማስገባት እቅድም አለ። በሁሉም ዘርፍ የፈጠራ ስራዎችን እንዲሰሩ በማድረግ ለአገሪቱ በማበርከት በውጭ ምንዛሪ የሚገዙ ማሽነሪዎችን የማስቀረት አላማ አለው። በአገሪቱ ውስጥ እየተፈጠሩ የሚገኙ የቴክኖሎጂ ምርቶችን ወደ ተግባር ለማስገባት እገዛ ያደርጋል።
በምንም አይነት ሁኔታ ዜጎች ጎዳና ላይ እንዳይወድቁ ለማድረግና አሁን በጎዳና ላይ የሚገኙትን ለማንሳት ፕሮጀክቶች ተነድፈው ወደ ተግባር ለመቀየር ዝግጅት እየተደረገ ነው። ሌላው ደግሞ በከፍተኛ ወጪ ወደ ውጪ ሄደው የሚታከሙትንና ሄደው መታከም የማይችሉ ህሙማንን በአገር ውስጥ (የበጎ ፈቃደኛ ሀኪሞችን ትብብር በመጠየቅ) ነፃ የህክምና ዘመቻዎችን በዓመት ሁለት ጊዜ ለማካሄድ የታሰበ ሲሆን፤ በቀጣይ ዓመት ለመጀመርም ሀሳብ አለ። የአረንጓዴ አሻራ እንቅስቃሴን በተያዘው ክረምት ወራት በስፋት ለመስራት ዝግጅት እየተደረገ ሲሆን ማህበሩ የራሱን አረንጓዴ መናፈሻ ለመስራት አቅዷል። በመናፈሻው ውስጥ ወጣቱ እንዲዝናናበት፣ እንዲያነብበት፤ በተጨማሪም ሌሎች ጠቃሚ ስራዎችን እንዲሰራበት ይደረጋል።
ማህበሩ አንባቢ ትውልድ ለመፍጠርና የትምህርት አጋዥ መፃህፍትን በቅርብ እንዲያገኙ ለማድረግ በተለያዩ ከተሞች ቤተ መፃህፍትን የመገንባት እቅድ አለው። ቤተ መፃህፍቱን ሲገነባ ከወጣቶችና ከተለያዩ ተቋማት የተገኙ መፃህፍትን በመሰብሰብ፤ እንዲሁም የጎደሉትን በግዥ በማሟላት ወደ ስራ ይገባል።
አዲስ ዘመን ሰኔ 25/ 2013