የምርጫ ሰሞንም አይደል? ስለ ምርጫ አንድ ሁለት ብንባባል አይከፋም ብዬ ነው። የምርጫ ጉዳይ ሲነሳ ሴቶች በተገቢው መልኩ አልተወከሉም የሚባሉ ቅሬታዎች በተደጋጋሚ ይነገራሉ። ሴቶች ካለመወከላቸውም በተጨማሪ በመራጭነት የሚሳተፉ ሴቶች ቁጥርም አነስተኛ መሆኑ በተደጋጋሚ ይነሳል። ለዚህ እንደ ምክንያት የተለያዩ ነገሮች ቢነሱም በአገራችን ሕገ መንግሥት ግን ማንም በፆታ ምክንያት ልዩነት ሳይደረግበት መምረጥም መመረጥም ይችላል።
የኢፌዲሪ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 38 የመምረጥና የመመረጥ መብትን የተመለከተ ድንጋጌ ሲሆን አንቀጽ 1 ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ… በጾታ ላይ የተመሰረተ ልዩነት ሳይደረግበት የመብቱ ተጠቃሚ እንደሚሆን ደንግጓል፡፡ በዚህ ድንጋጌ ላይ ከተዘረዘሩት የልዩነት መነሻዎች መካከል ጾታ አንዱ ነው፡፡ በዚህ መሰረት ዜጐች በመምረጥና በመመረጥ መብት ላይ ተጠቃሚ በሚሆኑበት ጊዜ በሴቶች ላይ በጾታ አማካኝነት ምንም ዓይነት ልዩነት ሊደረግባቸው እንደማይገባ የሚያመለክት ነው፡፡ በዚህም መሰረት የሴቶችን አቅም በመገንባት ፖለቲካዊ ተሳትፎአቸውን ለማሳደግና ወደ ውሳኔ ሰጪነት ለማምጣት መንግሥት በየደረጃው በተለያዩ ዘርፎች ከሚያደርጋቸው ጥረቶች በተጓዳኝ በሁሉም ዘርፍ ተወዳዳሪ ሆኖ ለመገኘት ራሳቸው በማብቃት ረገድ ከራሳቸው ከሴቶች ያላሰለሰ ጥረት ይጠበቃል።
ታዲያ በዘንድሮው በ6ኛው አገራዊ ምርጫ ሴቶች የሴቶችን ተሳታፊነት የጨመረና የተሻለ ቀን መምጣቱን ያመላከቱ ተስፋ ሰጪ ጅምሮች የነበሩበት መሆኑን ለመቃኘት ችለናል። በምርጫው መቃረቢያ መዲናችንን ያጥለቀለቁ በየመንገዱ የተለጠፉ ፓርቲዎችን ይምረጡ የሚሉ ታፔላዎች ላይ በርካታ ሴቶችን መመልከት እጅግ ተስፋ ሰጪ ጅምር ነው።
በአገራችን የምርጫ ታሪክን ስናነሳ በቂ ባይሆንም የዘንድሮው ሴቶችን በማሳተፍ ከሁሉ ልቆ እንደሚገኝ ተመልክተናል። አስርተ ዓመታትን ወደ ኋላ ተጉዘን በንጉሱ አገዛዝ ዘመን የነበረውን ቁጥር በምንመለከትበት ወቅት ከ240 የፓርላማ አባላት መካከል 2ቱ ሴቶች የነበሩ ሲሆን በደርግ ጊዜ ደግሞ ከ835 የሸንጎ አባላት መካከል 14 ብቻ ሴቶች ነበሩ።
ከአስር አመታት በኋላ ወይም ኢትዮጵያ ለመጨረሻ ጊዜ ባደረገችው ምርጫ በምክር ቤቱ መቀመጫን በማሸነፍ ያገኙ ሴቶች ቁጥር ከፍተኛ መሻሻልን አሳይቷል። የሴቶች ውክልና በምክር ቤት ወደ ኋላ 26 ዓመታትን ተመልሰን የ1987 ዓ.ም ምርጫን ብንመልከት በዚህ ዓመት በተደረገው አገር አቀፍ ጠቅላላ ምርጫ 536 ወንዶች የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫን ማሸነፍ የቻሉ ሲሆን የሴቶች ቁጥር ደግሞ 10 እንደነበር እንመለከታለን።
በዚሁ ወቅት የነበረውን የክልል ምክር ቤቶችን አሸናፊዎች ስንመለከት ደግሞ 1ሺህ 355 ወንዶች በዘጠኙ ክልሎች ባሉ የክልል ምክር ቤቶች ውስጥ መቀመጫ ማግኘት መቻላቸውን ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተገኘው መረጃ ያሳያል። በዚሁ ዓመት በዘጠኙ ክልሎች መቀመጫ ያገኙ የሴቶች ቁጥር 77 ነው።
በ2007 ወይም በአሁኑ ወቅት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤቶች ሴቶች ያላቸው ቁጥር 212 ወይም በመቶኛ ሲሰላ 38.8 በመቶ ነው። የክልል ምክር ቤቶችን ስንመለከት ደግሞ በወቅቱ አገሪቷን ያስተዳድር የነበረው ኢህአዴግ እና የተለያዩ አጋር ድርጅቶች ሁሉንም መቀመጫዎች ያገኙ ሲሆን ከነዚህም መካከል 800 ወይም በመቶኛ 40.3 በመቶ የሚሆኑት ሴቶች ናቸው።
ምንም እንኳን በምክር ቤቶች ያለው የሴቶች ውክልና ቁጥር መሻሻል ቢያሳይም በወሳኝ ቦታዎች አለመቀመጥ፣ የይስሙላ ተሳትፎና ቁጥር ማሟያ መሆናቸው የሚነሳ ጉዳይ ሆኗል ሲባል ይደመጣል።
በርካቶቹ የፓርቲዎቻቸውን ፕሮግራም ከማስፈፀም በዘለለ አጀንዳዎችን በመቅረፅም ሆነ ፖሊሲዎችን በማርቀቅ ደረጃ ምንም ዓይነት ተሳትፎ እንደሌላቸው ይናገራሉ። በተለይም የሥርዓተ ፆታ የኃይል ሚዛን ውስብስብና ዘርፈ ብዙ ችግሮችን ለመፍታት መዋቅራዊ የሆኑ የፖሊሲ ለውጦች ያስፈልጋሉ በሚባልበት ወቅት ሴቶች የራሳቸውን ዕጣ ፈንታ፣ በራሳቸው መወሰን አልቻሉም ይባላል። ከሆነ ሊታረም የሚገባው ተግባር ነውና በዚህ በኩል እኛ ሴቶች ኃላፊነታችንን ልንወጣ ይገባል።
በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ እንደ አንድ ትልቅ ምዕራፍ የሚታየውን የ1997 የመራጭ ሴቶች ቁጥር ለመመልከት ስንሞክር ግንቦት 07 ቀን 1997 ዓ.ም በተካሄደው የሕዝብ ተወካዮች እና የክልል ምክር ቤቶች አባላት ምርጫ ላይ 27 ሚሊዮን 372 ሺህ 888 ሰዎች የተመዘገቡ ሲሆን ከነዚህም ውስጥ የሴቶች ቁጥር 13 ሚሊዮን 087 ሺህ 594 ነው።
ከተመዘገቡትም ውስጥ በአጠቃላይ 22 ሚሊዮን 610 ሺህ 690 መራጮች ድምፅ ሰጥተዋል፤ ከነዚህም ውስጥ 12 ሚሊዮን 058 ሺህ 511 ወንዶች ሲሆኑ የሴቶች ቁጥር ደግሞ 10 ሚሊዮን 552 ሺህ 179 መሆኑን ከምርጫ ቦርድ የተገኘው መረጃ ያስረዳል።
ይሄን ካልን በዘንድሮ ስድስተኛው አገራዊ ምርጫም በርካታ እጩ ሴቶች ተሳትፈው ለመመልከት ተችሏል። ከዚህም በተጨማሪ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እንዳስታወቀው ለ6ተኛው አገራዊ ምርጫ የተመዘገቡ መራጮች ቁጥር 37.4 ሚሊዮን ሲሆን ከነዚህ መካከልም 20 ሚሊዮን 317 ሺ 412 ወንዶች ሲሆኑ 17 ሚሊዮን 91 ሺ 128 ሴቶች መራጮች ናቸው።
የስድስተኛው አገራዊ ምርጫ አጠቃላይ እጩዎች ብሎ ምርጫ ቦርድ ካቀረበው መረጃ ላይ እንደተመለከተነው 9ሺ 505 አጠቃላይ የእጩዎች ቁጥር ሲሆን ከነዚህም መካከል 1ሺ 987 ሴቶች ናቸው።
በዚህኛው ምርጫ የሴቶች ቁጥር የጨመረ ቢሆንም የህብረተሰቡ ግማሽ ክፍል ለሆኑት ሴቶች ውክልና በቂ ነው የሚል እምነት የለኝም። ሰለቁጥሩ ይህን ካልን ዘንዳ የምርጫው ለት ሌሊት ጋቢያቸውን ደርበው ከወጡት አዛውንት እንስቶች አንስቶ ለስራ ጠደፍ ጠደፍ እያሉ ለምርጫው ቅድሚያ እንዲሰጣቸው እስከ ሚለምኑ ወጣቶች ድረስ ሴቶቻችን በነቂስ ወጥተው መርጠዋል።
በእያንዳንዱ ምርጫ ጣቢያ አግኝተን ያነጋገርናቸው ሴቶች የምንመረጠው ሰላምን የሚያሰፍንልን፣ ልጆቻችንን የምናሳድግበት ምቹ አገር የሚፈጥርልን፤ ከኑሮ ውድነት የፀዳች አገር ሊሰጠን የሚችል መሪ ነው በማለት ነው መልስ የሰጡን።
በጉለሌ ክፍለ ከተማ የምርጫ ክልል ከሚገኙ ምርጫ ጣቢያዎች በአንዱ በር ላይ በአንደኝነት ተሰልፋ ያገኘኋት የበረራ አስተናጋጅ ወጣት ረድኤት ሰብሰቤ በማለዳ ምርጫ ጣቢያ የተገኘችው ከሰዓታት በኋላ የአውሮፕላን በረራ ያላት የአየር መንገድ ሰራተኛ በመሆኗ መሆኑን ነው የነገረችኝ።
ለእያንዳንዱ ነገር መሰረት ሰላም ነው። ሰላም ሲኖር እድገትና ብልፅግና ይከተላል። ስለዚህም ለአገር ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን የሚሰራ መሪ ለመምረጥና በዚሁ ወደ ስራዋ ለመሄድ የደንብ ልብሷን ለብሳ ወደ ምርጫ ጣቢያው የመጣችው የበረራ አስተናጋጅ ከምንም ነገር በላይ ሰላም ለሰው ልጅ መሰረታዊ ነገር ስለሆነ ሰላምን ያሰፍናል ላልኩት ድምጼን ልሰጥ ተዘጋጅቻለሁ የምትለው።
ሰላም ለሰው ልጆች በተለይም ለሴቶች የንፁህ አየር ያህል የሚናፈቅ መሆኑን የምትናገረው ወጣት ሁሉም ዜጋ በተሰማራበት የስራ ዘርፍ ከግጭት የፀዳ ሰላማዊ አካሄድ ቢሄድና በተገቢው መልኩ አገርን ቢያገለግል ወጤት ያመጣል ብላ እንደምታስብ ትናገራለች።
ሌሎች ቀጨኔ አካባቢ በሚገኘው ወረዳ 6 ምርጫ ጣቢያ 11 ደጃፍ የተሰለፉ በርካታ ሰዎች ተመለከትኩ። ቁጥር ስፍር ከሌለው ሰው መካከል በእጃቸው የሚቋጩትን ነጠላ የያዙ እናቶች ተቀምጠዋል። መቅረፀ ድምፄን ይዤ ጠጋ ያልኳቸው እናቶች ብዙም መናገር በማይችሉት አማርኛ ሰላም እኩልነት የሚያመጣ ዘረኝነትን የሚያጠፋ መንግሥት እንዲመጣልን እንመኛለን ብለዋል።
እነዚህ እናቶች በፍፁም ቅንነት ለወለዷቸው ልጆች ተስፋ የሚጣልባት አገር ትኖረን ዘንድ እየተመኙ ውድ ጊዜያቸውን ብሎም ጠቃሚውን ድምፃቸውን በመስጠት አደራ ሊሉ የሰኔ ዝናብ እየወረደባቸው ተሰልፈው ነበር የዋሉት። በዚህ ልክ አደራ የጣሉ እናቶችን አደራ የሚያስቀጥል መሪ ያምጣልን ተባብለን ከእነዚህ መራጭ ሴቶች ተለያይተናል።
ሌላዋ ልጃቸውን በጀርባቸው አዝለው ለመምረጥ የተዘጋጁት ወይዘሮ ሙላቷ ንጋቱ “ምንም እንኳን ህፃን በመያዜ ቅድሚያ ቢሰጠኝም ሴቶች በዚህ ልክ ወጥተው ለመምረጥ መዘጋጀታቸው አስደስቶኛል” ይላሉ። ውዱን ድምፃችንን በአደራ የምንሰጠው መሪ፣ ልጆቻችን ቦርቀው የሚያድጉባት አገር፣ ሁሉንም ዜጋ እኩል ተመልክቶ ማንም ከማንም ሳይበልጥ በሀገሩ እንደልቡ እንዲኖር የሚያደርግ መንግሥት እንደሚሰጠንም ተስፋ አደርጋለሁ” ብለዋል።
ምርጫው የሴቶችን ተሳትፎ ከፍ ያደረገ፣ ሕዝቡም በነቂስ ወጥቶ ያለ ምንም ኮሽታ የመረጠበት ሁኔታ መኖሩን በተገኘሁበት የምርጫ ክልል ተመልክቻለሁ። እኔም እንደናንተ መጪውና አዲሱ ተመራጭ መሪያችን፣ ማንም ይሁን ማን፣ የእናቶችን እንባ የሚያብስ፣ አገርን በአንድነት ወደ ፊት የሚያስቀጥል ይሆንልን ዘንድ እመኛለሁ።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ሰኔ 20 ቀን 2013 ዓ.ም