ባለፈው ሣምንት ከምርጫ ጋር የተያያዘ አንድ ዘገባ በዚህ ጋዜጣ መዝናኛ አምድ ላይ ወጥቶ አንብቤያለሁ:: ዘገባው የመራጮች ምዝገባን አስመልክቶ በሁሉም ሀገር ተመሳሳይ ሁኔታ አለመኖሩን ያመለክታል:: ከዘገባው ለጽሁፌ የሚጠቅመኝን አንዱን ጉዳይ ብቻ እጠቅሳለሁ::
በስዊድን ዜጎች መምረጥ የሚችሉት ግብር ለመክፈል የተመዘገቡ መሆን ሲችሉ ብቻ መሆኑን ዘገባው ያመለክታል:: በዚህ ሀገር ዜጎች ግብር ለመክፈል ሲመዘገቡ ለመምረጥ ብቁ መሆናቸውም ተረጋግጦ የመራጭነት ምዝገባውም በዚያው ይፈፀማል:: ስውዲናውያን ምርጫ ባለ ጊዜ የግብር ከፋይነት መታወቂያቸውን ይዘው በኩራት መርጠው ይውጣሉ:: ከዚህ የምንረዳው ግብር ምን ያህል ከሀገርና ህዝብ ጋር እንደተሳሰረ ነው::
እኛስ የት ላይ ነን? ርግጥ ነው በሀገራችን የሚሰበሰበው ግብር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መጥቷል:: መንግሥት የግብር መሰረቱን ለማስፋት እየሰራ መሆኑን ተከትሎ በግብር አሰባሰቡ ላይ ለውጥ እየታየ ነው:: እንዲያም ሆኖ ግን አሁንም ቢሆን ኢኮኖሚው የሚያመነጨው ግብር እየተሰበሰበ ላለመሆኑ መንግስትም ሁሌም እየገለፀ ነው፤ እኛም እየተመለከትን እንገኛለን::
ሌሎች ቦታዎች ሳንደርስ ዜጎች ቤታቸውን ሲያከራዩ ግብር የሚከፍሉበት ሁኔታ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ተግባራዊ ቢደረግም አሁንም ቢሆን ከቤት ኪራይ የሚሰበሰበው ግብር እዚህ ግባ የማይባል ስለመሆኑ አከራዮች ከሚፈጽሙት ህገወጥ ድርጊት መረዳት ይቻላል::
በአንድ ወቅት በግለሰብ ምግብ ቤት በአስተባባሪነት የሚሠራ ሰው አከራዩ የቤት ኪራይ እንደቀጠሉበት ነገረኝ፤ ለምን አልኩት የሠራተኞች (የመንግሥት) ደመወዝ ተጨመረ እንዳሉት ነገረኝ:: እሱ በግል ነጋዴ ቤት ተቀጣሪነት እንደሚሠራ ቢነግራቸውም፤ እኔ አላውቅም ካልጨመርክ ገንዘብ የተጨመረላቸው ኪራይ ጨምረው ይከራያሉ ብለው እንደገለጹለት ነግሮኝ እንደነበር አስታውሳለሁ::
ልብ በሉ እኚህ ሰው የቤት ኪራይ መጨመራቸው አይደለም እዚህ ላይ ያሳሰበኝ:: እሳቸው የቤት ኪራይ ግብር የሚከፍሉ ከሆነ በጨመሩት የኪራይ ዋጋ ልክ ለመንግስት ግብር የሚከፍሉ አለመሆናቸው ነው::
የቤት ኪራይ ጭማሪ ደግሞ አከራዮች የመብራት ዋጋ ጨመረ፣ የውሃ ሂሳብ ጨመረ፣ የሥጋ ዋጋ ጨመረ አልያም የዘይት ዋጋ ጨመረ ብለው ይጨምራሉ:: ደስ ካላቸው ጫት ጨመረ ብለው ኪራይ ሊጨምሩባችሁ ይችላሉ:: የሀገራችን የቤት አከራዮች በሙሉ በዚህ በኩል አንድ ናቸው:: በእያንዳንዱ ገቢ ግብር መክፈል እያለባቸው የማይከፍሉ የመንግስትና ህዝብ ባለዕዳ ናቸው::
በዚህ መካከል መንግስት ሊያገኛቸው ያልቻሉ ደላሎች አሉ፤ የነገር ስም የሆኑበት ይመስለኛል፤ አይታዩ አይዳሰሱ:: ተከራይ እንዳይቆም እንዳይቀመጥ የሚያደርጉት አንድም እነሱ ናቸው:: ለቤት አከራዮች በሺህ እና 500 ብር ጭማሪ የሚከራዩ አሉ እያሉ አከራዩን ይወተውታሉ፤ እነሱም ኮሚሽናቸውን ሲቀበሉ ለመንግስት ጠብ የሚል ነገር የለም:: በዚህች ሀገር ያለው የደላላ ብዛት መቼም ተጠንቶ አይታወቅም እንጂ ቢታወቅ ቁጥር ሥፍር እንደሌላቸው መረዳት ይቻላል:: ከእያንዳንዱ ኮሚሽናቸው ዝቅተኛ የተባለ ግብር እንኳን እንዲከፍሉ ቢደረግ ቢሊዮኖች ብር መሰብሰብ በተቻለ ነበር::
ስለ ቤት ኪራይ ለማንሳት የፈለግኩት ስለ ተከራይ እንግልትና ስለ አከራይ ኢሰብዓዊነት ለማንሳት ፈልጌ አይደለም፤ አንድ ሀገር በኢኮኖሚ መዳበር የምትችለውና የምታድገው ምጣኔ ሀብቱ ከሚያመነጨው ሀብት ተገቢውን ግብር መሰብሰብ ስትችል ነው:: በዚህ በኩል ሀገራችን ገና ብዙ መስራት የሚጠይቃት ተግባር እንዳለ ነው እንረዳለን::
ባለንበት በዚህ በዲጂታል ዘመን በሸገር በተለያየ ቦታ ሦስት አራት ቤት ኖሯቸው እያከራዩ የተሻለ ሕይወት የሚመሩ ጥቂት አይደሉም:: በቅርብ የማውቃቸው አንዲት እናት በመሐል ከተማ በአንድ ግቢ ስምንት ቤት በሦስት ሺህ ብር ያከራያሉ፤ ተከራዮቻቸው ገንዘቡን የሚከፍሏቸው በተለያየ ጊዜ ቢሆንም በሌላ የከተማዋ ዳር እየኖሩ በወር 24 ሺህ ብር ይቀበላሉ::
በዚህ ዘመን ገንዘብ በአብዛኛው በዲጂታል ዘዴ ነው እየተዘዋወረ ያለው:: እንዲህ ዓይነቶቹን ቤት አከራዮች መረጃ የአይ ሲቲና የፋይናንስ ባለሙያዎች ይጠበቡበትና ያረጋግጡት:: ኮሮና ከመጣ በኋላ የተላለፈው አዲስ መመሪያ ሰዎች ገንዘባቸውን ሲከፍሉ በባንክ በኩል እንዲሆን ተደርጓል:: ይህም አንድ ሰው በወር በአማካይ ምን ያህል ገቢ ሊኖረው እንደሚችል ፍንጭ ይሰጣል:: ይህን የገንዘብ ዝውውር ለግብር መተመኛ አይጠቅምም ተብሎ አይታሰብም::
በግብር አሰባሰቡ ላይ ለውጥ ቢታይም አሁንም ቢሆን በአብዛኛው ግብሩን የሚያስገባው በመንግሥት፣ በግል መሥሪያ ቤት የሚሰራውና ትላልቅ ድርጅት ያላቸው ነጋዴዎች ይመስሉኛል:: ዋና ዋና መንገድ ላይ የሚታዩ ሱቆች፣ ሆቴል ቤቶች እና የመሳሰሉት ግብር ይከፍላሉ:: በየበራቸው ላይ የሚለጠፉ የግብር ሰብሳቢው መሥሪያ ቤት መረጃዎችም ይህንኑ ያመለክታሉ::
ከዚህ በመለስ ግን የንግዱ እንቅስቃሴ ከቀን አልፎ በምሽትና በሌሊት / ለ24 ሰዓታት / የሚካሄድባቸው አካባቢዎች ሞልተዋል:: በእነዚህ አካባቢዎች ሌሊት ላይ ቫት እየተቆረጠ ይሰራል ብሎ መገመት ይከብዳል:: እንኳን በሌሊት በቀንም የቫት ጉዳይ የሌባና ፓሊስ ዓይነት ነገር ነው:: ግብር ሰብሳቢው አካል የሀገሮችን ተሞክሮም በመቀመር ቢሆን ሌሊቱን ሙሉ ከፍተኛ መጠን ያለው በሚዘዋወርባቸው አካባቢዎች ተገቢውን ግብር ለመሰብሰብ መስራት ይኖርበታል::
እስቲ መርካቶን አንዳፍታ እንመልከታት፤ በመርካቶ ነጋዴው፣ ደላላው፣ ባለሙያው፣ ጫኝና አውራጁ ወዘተ ሁሉ በየራሳቸው አቅም ገቢ ይፈጥራሉ:: በትላልቅ ህንጻዎች ከሚንቀሳቀሰው ሀብት የማይተናነስ ሀብት ድክም ባሉ ቤቶችና ስርቻዎች ይንቀሳቀሳል:: የወደቀ የሚባለው ቤት ከፍተኛ የንግድ እንቅስቃሴ ይካሄድበታል:: በመርካቶ አይደለም ቤት ጎዳና ከፍተኛ መጠን ያለው ሀብት ይንቀሳቀሳል::
መርካቶ ሀገር ሊያስተዳድር የሚችል ሀብት የሚንቀሳቀስበት ነው:: መርካቶ ከአዲስ አበባ ተርፎ ሌሎችን የማኖር አቅም ያለው ሰው የተሰባሰበበት ሰፊ አካባቢ ነው፤ ይሁንና ግብር የማይከፍለውና እዚህ ግባ የሚባል ግብር የማይከፍለው ሲታሰብ ብዙ መስራትን ይጠይቃል::
መርካቶን ያነሳሁት የማይገብሩ ሰዎች የሚከብሩበት አንዱ ማሳያ ስለሆነ ነው:: ወደ ምዕራብ ሆቴል በተለምዶ አብዶ በረንዳ የሚባለው ጫት ተራ ዋነኛ የጫት ማከፋፈያ አካባቢ ያለውን የሰው ትርምስምስ ሄዳችሁ ማየት ትችላላችሁ፤ የጅምላና ችርቻሮ ጫት ነጋዴዎቹ እሁድም ክፍት ስለሆነ ይጠቀሙበታል፤ የንግድ ቤታቸው ግን ከላስቲክ ቤት የተሻለ አይደለም:: ነጋዴዎቹ ገቢው የማያመነጨውን “ሚጢጢ” ግብር እየገበሩ እነሱ በኢንቨስተር ደረጃ ይኖራሉ:: ሰዎቹ ለምን ባለሀብት ሆኑ የሚል እኩይ ዓላማ የለኝም፤ ገቢው የሚያመጨውን ግብር እንዲገብሩ መደረግ ግን አለበት::
ግብር መሰብሰብ የመንግሥት ግዴታ ብቻ ተደርጎ መታየት የለበትም። ሰዎችም ግብር በመገበር የዜግነት ግዴታቸውን ሊወጡ ይገባል፤ በሰሩት ልክ ግብር አለመክፈልም ሆነ ጨርሶ ግብር አለመክፈል ሀገርን ብዙ ያሳጣል:: ገቢው በአግባቡ ካልተሰበበ ልማቱን ማሳለጥም አይቻልም::
ከግብር ይውጣ ግብር ክፍያም ሆነ አሰባሰብ መውጣት ያስፈልጋል:: ይህ የሚመለከተው መንግሥትን ወይም ግብር ሰብሳቢውን አካል ብቻ አይደለም፤ መገበር እያለበት የማይገብረውን እንዲሁም ተገቢውን ግብር የማይከፍለውንም ጭምር ነው:: ለእናት ሀገሩ ሳይገብር ከሀገሩ ብዙ የሚፈልግ ዜጋ ሊኖረን አይገባም:: በመግቢያዬ እንደገለጽኩት ግብር ክፍያንና ዜግነትንም በቀጣይ እያስተሳሰሩ መስራት የሚያስፈልግ ይመስለኛል:: ዜጎች ግብር በመክፈላቸው ኩራት የሚሰማቸው እንዲሆኑ ማድረግ ድረስ የሚዘልቅ ስራ መሰራት ይኖርበታል::
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ በአንድ ወቅት ‹‹መገበር እያለባቸው የማይገብሩ ነጋዴዎችንና ባለሙያዎችን ወደ ግብር መረብ ለመክተት ጥረት ይደረጋል›› ሲሉ ገልፀዋል:: ይህን መሬት ላይ አውርዶ ግብር የማይከፍሉ እንዲከፍሉ ተገቢውን ግብር የማይከፍሉትም ተገቢውን ግብር እንዲከፍሉ ለማድረግ ጊዜ ሳይሰጠው ሊሰራ ይገባል:: መንግስት የግብር ሠራዊት አሰማራለሁ ያለውን ጊዜ ሳይሰጥ መፈፀም ይኖርበታል:: አለመገብርም አሣንሶ መገበርም ዋጋ እንዲያስከፍሉ አድርጎ መስራት ያስፈልጋል::
ይቤ ከዳጃት ውቤ
አዲስ ዘመን ሰኔ 20 ቀን 2013 ዓ.ም