ሀገራችን በዛሬው እለት ስድስተኛውን ሀገራዊ ምርጫ ታካሂዳለች፡፡ ዜጎችም በየምርጫ ጣቢያዎች በመገኘት ድምጻቸውን ይሰጣሉ፡፡ እኛም የዛሬው የአዲስ ዘመን ድሮ አምዳችን ዘገባን ምርጫ ምርጫ አንዲል በማሰብ ኢትዮጵያ በአንጻራዊ መልኩ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ አርጋበታለች ተብሎ በሚታወቀው በ1997 ሀገራዊ ምርጫ ወቅት ከተስተናገዱ አስደናቂ ዘገባዎች ይበልጥ የአንባቢን ትኩረት ይስባሉ ያልናቸውን ሰው ሰው የሚሸቱ ዜናዎችን ይዘን ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ፡፡
ድምጽ ለመሥጠት ከደቡብ ወሎ በኮንትራት ታክሲ ወደ አዲስ አበባ
ደሴ(ኢ.ዜ.አ.)፡-በአዲስ አበባ የሚኖሩ አንድ ግለሰብ ድምጽ ለመስጠት ሲሉ በመስክ ሥራ ከተሰማሩበት ከደቡብ ወሎ በኮንትራት ታክሲ ወደ አዲስ አበባ ትናንት ተመልሰዋል፤ህሙማንም ድምጽ ሰጥተዋል።
ለመስክ ሥራ በደሴ ከተማ የሚገኙት አቶ ሰለሞን ሰውነገር እንደገለጹት፤ትናንት ንጋት ላይ ወደ አዲስ አበባ ከተማ የተመለሱት የሚደግፉት ፓርቲ በአንድ ድምጽ ቢሸነፍ ከሚደርስባቸው ፀፀት ለመዳን ነው።
ከተሰማሩበት የመስክ ሥራ ፈጣን ተሽከርካሪ በመከራየት ለመራጭነት ወደ ተመዘገቡበት አዲስ አበባ አራዳ ክፍለ ከተማ ድምጽ እንደሚሰጡ ገልጸው፤ ዕለቱን ሲጠባበቁ መቆየታቸውን አስታውቀዋል።
ከደሴ አዲስ አበባ የተሸከርካሪ ወጪያቸውን ሸፍነው ድምጽ ለመስጠት የተመለሱት ምርጫውን ከማንኛውም ጉዳይ በማስቀደም ትኩረት በመስጠታቸው መሆኑን ገልጸዋል።
በሌላ በኩል በደሴ ከተማ ቀበሌ 18 ምርጫ ጣቢያ በመራጭነት የቀረቡት ወይዘሮ ራቢያ ኢብራሂም እንደገለጹት በቅርቡ የቀዶ ጥገና ተደርጎላቸው ከተኙበት አልጋ ተነስተው ድምጽ ለመስጠት ተገኝተዋል።
በኮምቦልቻ ከተማ በቀበሌ ዜሮ ሦስት ምርጫ አስተያየት የሰጡትና ማየት የተሳናቸው አቶ ሰዓድ ይመር የፓርቲዎቹን ዓላማና ፕሮግራም በሬዲዮ በመከታተላቸው የድምጽ መስጫውን ዕለት በጉጉት ሲጠባበቁ እንደነበር አስታውቀዋል።
ግንቦት 8 ቀን 1997 አም
ሙሽሮች ድምጽ ሰጡ
አዲስ አበባ (ኢ.ዜ.አ)፡-በጉለሌ ክፍል ከተማ ወረዳ 9 ምርጫ ክልል ቀበሌ 12 ነዋሪ ወይዘሮ ሰብለ እንግዳእሸት የጋብቻ ስነሥርዓቷን የምታከብርበት ዕለት ሳይበግራት ድምጽ ሰጠች።
ወጣቷ ሙሽራ ከሚዜዎቿና ከአጃቢዎቿ ጋር በመሆን ድምጽ ከሰጠች በኋላ እንደገለጸችው ዕለቱ ለእሷ ልዩ ነው። ዕለቱ ሀገሪቱ በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት የምትመራበት አቅጣጫ የሚወሰንበት በመሆኑ የእሷ ድምጽ የሚኖረውን ከፍተኛ ዋጋ በማወቋ ድምጽ መስጠቷን ገልጻለች።
የድምጽ መስጫ እለት ከጋብቻ በዓሏ መገጣጠሙ ታሪካዊ በመሆኑ የተሰማትን ድርብ ደስታ ገልፃለች። የሙሽሪት ባለቤት ዶክተር እንዳለ ወርቅዓለማየሁ በበኩላቸው፤በሚኖሩበት ቀበሌ ድምጽ መስጠታቸውን ገልጸዋል።
በተመሳሳይም በዚሁ ክፍለ ከተማ ወረዳ 11 ቀበሌ 16 ነዋሪ የሆነው ወጣት ሸዋንግዛው አከለ የጋብቻ ስነሥርዓቱን በሚፈጽምበት በትናንትናው ዕለት በድምጽ መስጫ ጣቢያ በመገኘት ድምጹን ሰጥቷል።
የ31 ዓመቱ አርቲስት ከሚዜዎቹና ከዕድምተኞቹ ጋር በመሆን ድምጽ ከሰጠ በኋላ እንደገለጸው ፤ዕለቱ የሀገሪቱ የወደፊት ዕጣ ፈንታ የሚወሰንበት በመሆኑ ከጋብቻ በዓሉ ጎን ለጎን ድምጽ ለመስጠት መምጣቱን ተናግሯል።
ሙሽሪትን ከመኖሪያዋ ለማምጣት ከመሄዱ በፊት ድምጹን ለመስጠት ወደ ጉለሌ ክፍለ ከተማ ድምጽ መስጫ የመጣው ወጣቱ ሙሽራ ዕለቱ ከጋብቻው በዓል ጋር መገጣጠሙ ለእርሱ ታሪካዊና አስደሳች እንደሆነለት ገልጿል።
ግንቦት 8 ቀን 1997 አም
የምርጫ ድምጽ ጠጅ ቤት ሲቆጥሩ የተገኙ በቁጥጥር ሥር ዋሉ
ሆሳዕና (ዋኢማ)፡-የሀዲያ ዞን ምርጫ ቦርድ ጽህፈት ቤት ከምርጫ አስፈጻሚዎች ጋር በመተባበር ጠጅ ቤት ውስጥ የምርጫ ድምጽ ሲቆጥሩ የተደረሰባቸው ሰዎች በፖሊስ መያዛቸውን አስታወቀ።
የጽህፈት ቤቱ አስተባባሪ አቶ ግርማ ሙዘይን ትናንት እንደገለጹት፤ በፖሊስ የተያዙት ግለሰቦች ከምሽቱ አራት ሰዓት ላይ በሶሮ 02 የምርጫ ክልል የኦሎዎች ቀበሌ የምርጫ ጣቢያ አስተባባሪዎች ከሌሎች ግብረአበሮቻቸው ጋር በመሆን ድምጽ ቆጠራ ሲያካሂዱ በመገኘታቸው ነው።
እንዲሁም በተለያዩ የምርጫ ክልሎች በሚገኙ አንዳንድ ጣቢያዎች ድምጽ የተሰጠባቸውን ኮሮጆዎች የመቅደድና ሌሎች የተፈጸሙ ችግሮችን ጽህፈት ቤቱ ውሳኔ እንደሚሰጥ አስረድተዋል ።
ግንቦት 14 ቀን 1997 አም
ድምጽ ለመስጠት ምርጫ ጣቢያ የተሰለፉ እዚያው ተገላገሉ
መቱ(ኢ.ዜ.አ)፡-በኢሊባቡር ዞን በያዩ ሁርሙ ወረዳ በአንድ የምርጫ ጣቢያ ድምጽ ለመስጠት ከትናንት በስተያ ተራ ይዘው ሲጠባበቁ ምጥ የያዛቸው አንዲት ሴት ወይዘሮ ወንድ ልጅ መገላገላቸውን ፖሊስ አስታወቀ።
የዞኑ ፖሊስ መምሪያ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ምክትል ኢንስፔክተር ጊዮን ቸርነት ትናንት እንደገለጹት፤ወይዘሮ መብራቴ ከበደ የተባሉት እኝሁ ወይዘሮ ከቀኑ ስምንት ሰዓት ላይ የተገላገሉት የመምረጥ መብታውን ለመጠቀም ተራ ይዘው እንዳለ ነው።
ድምጽ ለመስጠት ተሰልፎ የነበረው ኅብረተሰብ ሴትየዋን ጤና ተቋም ለማድረስ ርብርብ ቢያደርግም ሳይቻል በመቅረቱ እዚያው መገላገላቸውን ምክትል ኢንስፔክተሩ አስታውቀዋል።
ወይዘሮዋ በምርጫ ጣቢያው ተራ ይዘው ሲጠባበቁ በድንገት በያዛቸው ምጥ ሳቢያ ድምጽ ሳይሰጡ መቅረታቸውን ከኃላፊው ገለጻ ለመረዳት ተችሏል።
ግንቦት 1997 አም
አካል ጉዳተኛዋ በእግሯ ፊርማ ድምጽ ሰጠች
መቀሌ(ዋኢማ)፡-በመቀሌ ከተማ በነውሒ ንጉሥ ቀበሌ አንዲት አካል ጉዳተኛ ወጣት በእግሯ ፊርማ ድምጽ መስጠቷን የቀበሌው ባህልና ማስታወቂያ ኃላፊ ገለጹ።
ኃላፊው አቶ ገብረኪሮስ ዓለሙ ከትናንት በስቲያ እንደገለጹት፤ዕሁድ እለት ወደ ቀበሌው ምርጫ ጣቢያ ለመምረጥ የመጣቸው ወጣት ሁኔታና ድምጽ አሰጣጥ የሁሉም መራጭ ሕዝብ ቀልብ የሳበ ነበር።
ወጣቷ መዝገቡ መሬት እንዲነጠፍላት ከጠየቀች በኋላ በአንዱ እግሯ ጣቶች ስኪርቢቶውን ይዛ በመፈረምና ወደ ድምጽ ምስጢር መስጫ በመግባት ያለ ረዳት ለምትፈልገው ዕጩ ምልክት በማድረግ ወረቀቷን አጣጥፋ ወደ ኮሮጆው እንዲገባላት አድርጋለች ብለዋል።
30 ዓመቷ ወጣት ለተሩፋኤል ተካ ተጠይቃ በሰጠችው ምላሽ በተፈጥሮ ሁለት እጅ የሌላት ሆና መወለዷ ከማንኛውም ማኅበራዊ እንቅስቃሴ እንዳላገዳት ሁሉ በምርጫውም በእግሯ በመፈረም የሚጠቅማት ዕጩ መምረጧን ገልጻለች።
ወጣት ለተሩፋኤል ተካ ምርጫው ነጻና ዴሞክራሲያዊ እንደነበር ጠቅሳ ለአካል ጉዳተኞች ያስባሉ ያለቻቸውን ተወካዮች መምረጧን አብራርታለች።
ስለሀገሬ ሁሌ ስለምቆረቆር ከዚህ በፊት በነበሩት ሁለት ምርጫዎች ተሳትፌያለሁ ያለችው ወጣቷ በመደበኛ ትምህርት እስከ ስምንተኛ ክፍል ተምራ በችግር ምክንያት እንዳቋረጠች አመልክታለች።
ግንቦት 10 ቀን 1997 አም
የአባቱን የምርጫ ካርድ ሰርቆ ለመምረጥ የሞከረ ተቀጣ
ሐረር (ዋኢማ)፡-በምሥራቅ ሐረርጌ ዞን በአወዳይ ልዩ ከተማ የአባቱን የምርጫ ካርድ ሰርቆ ለመምረጥ የሞከረው ወጣት ሦስት መቶ ብር ወይም በሦስት ወር እስራት እንዲቀጣ የተፈረደበት መሆኑን ፖሊስ ገለጸ።
የዞኑ ፖሊስ መምሪያ የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ኃላፊ ምክትል ኢንስፔክተር ስዩም ደገፋ ትናንት የወጣቱን ሕገወጥ ድርጊት በማስረጃ አጣርቶ ቅጣቱን የወሰነበት የዓለምማያ ወረዳ ፍርድ ቤት ነው።
ወጣቱ የተቀጣው በወቅቱ የምርጫ ካርድ ባለመውሰዱ ተቆጭቶ የአባቱን የምርጫ ካርድ ሰርቆ በልዩ ከተማው በሊና ቀበሌ ገበሬ ማኅበር አታሎ ድምጽ ለመስጠት ሲሞክር ምርጫ አስፈጻሚዎች ለፖሊስ በሰጡት ጥቆማ ተይዞ መሆኑን የሕዝብ ግንኙነቱ ጠቁመዋል።
ግንቦት 9 ቀን 1997 አም
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ሰኔ 14/2013