ወይዘሮ መአዛ መንክር የአእምሮ ህክምና ባለሙያ እና አማካሪ፤ ደራሲና አማካሪ ናት። በአስራ ዘጠኝ ሰባዎቹ መጀመሪያ አካባቢ ነበር በአዲስ አበባ የተወለደችው። መአዛ እናቷ መምህርት፣ አባቷ የቤተ-መጻሕፍት ባለሙያ ስለነበሩ የተመደቡበት አካባቢ ሄደው ይሰሩ ነበር። እሷ ስትወለድ ግን ኑሯቸው አዲስ አበባ ነበረ። ከዚያ በኋላ ቤተሰቦቿ ለስራ ወደ ኮረም ሲዘዋወሩ ልጆቻቸውም እዚያው መማር ይጀምራሉ። መአዛ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቷን በኮረም እስከ ስምንተኛ ክፍል ከተማረች በኋላ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን በአዲስ አበባ፣ ቦሌ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ታጠናቅቃለች።
የእውቀት አባትና እናት የሆኑ መምህራን ልጅ ናትና በትምህርት ዝቅ የማለት ነገር አይታሰብም ነበር። በወቅቱ በጣም ጥሩ የሚባል ውጤት ለማምጣትም መአዛን ያገዳት አንዳችም ነገር አልነበረም። የ2ኛ ደረጃ መልቀቂያ ፈተና በመውሰድ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም የሚያስገባትን ውጤት ካመጣች ስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ ትገባለች። በወቅቱ የመጀመሪያ ዓመት “የጋራ ኮርስ” ከወሰደች በኋላ “ኢጁኬሽናል ሳይኮሎጂ” ክፍለ-ትምህርትን ትቀላቀላለች። በወቅቱ በዚህ የትምህርት ዘርፍ የተማሩ ሰዎች በትምህርት ቤቶች ውስጥ የ”ጋይዳንስና ካውንሲሊንግ” አገልግሎት ባለሙያ ሆነው ይቀጠሩ ነበር። ክፍተት ሲኖርም እንዲያስተምሩ ፔዳጎጂ ኮርሶችን በብዛት ይወስዱ ነበር።በፔዳጎጂ የትምህርት ዘርፍ የመጀመሪያ ዲግሪዋን ያገኘችው መአዛ በወቅቱ የስራ እድል (በምደባ) ቢኖርም ያንን በመተው ከጓደኞቿ ጋር በመሆን የቅድመ መደበኛ መምህራን ማሰልጠኛ ትከፍታለች።
ለተወሰኑ ዓመታት በዚሁ ትምህርት ቤት ሁለት ሺህ ያህል ሴት የቅድመ መደበኛ መምህራንን ማስመረቅ መቻላቸውን የምታስታውሰው ይች ታታሪ ሴት፣ ኋላ ግን የመምህርነት ስልጠና በግል መሰጠት አይገባውም ተብሎ በኮተቤ መምህራን ማስልጠኛ ስልጠናው መሰጠት ሲጀምር ተቋማቸው ይዘጋል። ተቋማቸው እንደተዘጋ ከሴቶችና ከልጆች ጋር መስራት የነፍሷ ጥሪ የሆነው ይች ሴት የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት በመክፈት ስራዋን ትጀምራለች።
በዚህ ስራ ውስጥ በየእለቱ ከወላጆቻቸው ተነጥለው ለመማር የሚመጡ የተለያየ ባህሪ ካላቸው ህፃናት ጋር መገናኘት የእለት ከእለት ኑሮዋ መሆን ጀመረ። በባህርይም ሆነ የትምህርት ተሳትፎ የተለያዩ ልጆች ቢኖሩም የመአዛ ትኩረት ግን ትምህርታቸውን በአግባቡ መቀበል የማይችሉት ህፃናት ላይ ነበር። እናም እነዚህን ልጆች “በምን መልኩ ማገዝ እችላለሁ?” የሚል ሀሳብ ወደ ውስጧ ቢመላለስም ያንን ለማድረግ የሚያስችል በእውቀት ላይ የተመሰረተ ድጋፍ ለማድረግ አስባ የከፍተኛ ትምህርቷን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በመማር በልዩ ፍላጎት ትምህርት የማስተርስ ዲግሪዋን ትወስዳለች።
በዚህ የትምህርት ዘርፍ በቂ የተግባር ስልጠና ባታገኝበትም በተለያየ መንገድ እውቀቷን ሙሉ ለማድረግ እየጣረች በስራዋ ስኬታማ ለመሆን መጣር ትጀምራለች። በአንድ አጋጣሚ አንዲት ሴት ልጇን ወደ “መአዛ ትምህርት ቤት” ይዛ መጥታ ካስመዘገበች በኋላ በእንባ ስትታጠብ ትመለከታለች። ምን ሆና እንደሆነ ብትጠይቃትም ይች ሴት ከማልቀስ ውጭ ለማናገር የሚያስችል አቅም አላገኘችም ነበር። መአዛ ትንሽ እንድትረጋጋ ካደረገች በኋላ የዚህችን እናት ችግር መስማት ትጀምራለች።
ይች እናት የሚጥል ህመም ያለው፤ የሚጮህ፣ የሚያለቅስ፣ ከግርግዳ ጋር የሚጋጭ ልጅ እንዳላትና በእርሱ ምክንያት እንቅልፍ እንደሌላቸው፤ ህይወቷም እንደተመሰቃቀለ፤ ልጁንም ቤት ውስጥ ዘግታበት እንደሚውልና የኦቲዝም ኬዝ እንዳለበት ለወይዘሮ መዓዛ ደፍራ ትነግራታለች። ይች እናት ከሀገር ውጭ ትኖር የነበረች፣ ነገር ግን በዚሁ ልጅ ምክንያት ወደ ሀገሯ ተመልሳ የመጣች መሆኗንም ትገልጽላታለች።
ወይዘሮ መአዛ በልጇ ተስፋ ቆርጣ፤ በሀዘን ተውጣ የነበረችውን ይችን እናት ለመርዳት ልቧ ይነሳሳል። እናም የልጁን ሁኔታ ለመረዳት እንድታመጣው ትመክራታለች። እድሜው ከፍ ያለ ቢሆንም ሲመጣ በሞግዚት ታዝሎ ነበር። ከቤት ወጥቶ የማያውቀው ልጅ ከጸሃይ ብርሃን እጥረት የተነሳ ቆዳው ነጥቷል። ወይዘሮ መዓዛ ይህን ልጅ ባየችው ጊዜ ውስጧ አዘነ። እናቲቱን ለማገዝ ልጁንም ለመርዳት በሚል ተቀብላ ሞግዚት ተቀጥሮላት እርሷም ትኩረት ሰጥታ ክትትልና ድጋፍ ማድረግ ትጀምራለች።
በእግሩ መሬት የማይረግጠው ልጅ ከሚደረግለት እርዳታ በኋላ ለውጥ እያሳየ መምጣት ይጀምራል። ልጁም ቀደም ሲል የነበረውን ባህሪ ቀይሮ በፍፁም መረጋጋት ወስጥ ይሆናል። ከዚህ በኋላ በአንድ ልጀ የተጀመረው የኦቲዝምን በትምህርት ቤቱ የማካተት ስራ ሰፋ ባለ ሁኔታ መስራት ትጀምራለች።
ከስራው በሻገር በኦቲዝም ጥላ ስር ልጆች፣ ወላጆች የሚገጥሟቸውን ችግሮች በማየት የእነዚህን ሰዎች ችግር ሊያግዝ የሚችል ሞያተኛ ለመሆን ድጋሚ ወደ ዩኒቨርሲቲ በመግባት በክሊኒካል ሳይኮሎጂ የማስተርስ ዲግሪዋን ትማራለች።
‹‹ሻምፒየንስ የትምህርት አገልገሎት ተቋም›› የተባለ ድርጅት ከባለቤቷ ጋር በማቋቋም የአካቶ ትምህርትና ስልጠና በመስጠት እንዲሁም በአማካሪነት በማገልገል ላይ የምትገኘው ወይዘሮ መአዛ በህፃናት እና በአዋቂዎች የአእምሮ ጤና ዙሪያ በራሷ የማህበራዊ ገፆች ትምህርት እየሰጠች ትገኛለች።
ባለትዳርና የሁለት ልጆች እናት የሆነችው ወይዘሮዋ በትምህርት ቤቷ የሚመጡ ህፃናትን ተገቢውን ክህሎት አስጨብጣ ወደ መደበኛ ትምህርት ቤት እንዲቀላቀሉ ከማድረግ ባሻገር እናቶችም በልጆቻቸው ምክንያት የሚመጣባቸውን ጫና የማቃልል ስራ እየሰራች ትገኛለች።
ይህን ስራ ለመስራት አንድም ቀን የማስተዋወቅ ስራ ሰርታ የማታውቅ መሆኗንም ትናገራለች። ወይዘሮ መአዛ መጀመሪያ ልጇን ካመጣችው ወላጅ ጀምሮ በዙሪያዋ ያሉ ሰዎች እርስ በእርስ እየተነጋገሩ ወደሷ የሚያመጧቸው ልጆች ይበረክታሉ ትላለች። እስካሁን ድረስ ከአንድ ሺህ በላይ ህፃናት መጥተው ድጋፍ ተደርጎላቸው ተቀይረው በአቅራቢያቸው እንዲማሩ ተደርገዋል። አሁን 90 ልጆች በትምህርት ቤቱ አገልግሎት የሚያገኙ ሲሆን ኦቲዚም ኖሯቸው እስከ 9ኛ ክፍል የደረሱ ልጆች መኖራቸው ስኬታማ ስራ እንደሰራች እንድታስብ እንዳደረጋት ትናገራለች። ወይዘሮ መአዛ የተለያዩ ወጣቶችንም በማሰልጠን በዚህ ችግር ላይ ላሉ ልጆች እርዳታ በየአካባቢያቸው እንዲሰጡ ታደርጋለች።
አሁን ደግሞ የተለያየ ቦታ የሚገኙ የኦቲዝም ችግር ያለባቸውን ልጆች በቀላሉ በእውቀት ለመርዳት የሚያስችል ‹‹ሁሉ በአንድ›› የተባለ መጽሐፍ አሳትማለች። የዚህ መፅሃፍ ይዘት ኦቲዝም ምንድነው? ከሌላው የጤና ችግር በምን ይለያል? ታዲያ እነዚህን ልጆች በምን እንርዳቸው? በቋንቋና ባህሪ በማረቅ ስራ ውሰጥ ምን ምን መሰራት አለበት? የሚሉ ይዘቶችን ከመያዙም ባሻገር ወላጆች ተስፋ እንዲሰማቸው፤ ከዚህ ችግር ጋር የተወለዱ ልጆች ያላቸውን ወላጆች ተሞክሮ የያዙ አስር ታሪኮችን በማከትት የታተመ መፅሃፍ ነው።
አሥር ምእራፍ ያሉት ይህ መፅሀፍ አሥር እውነተኛ ታሪኮችን የያዘ ሲሆን እንደመነሻ በቤት ውስጥ ድጋፍ የሚፈለግ ልጅ ያላቸው ቤተሰቦች በምን ምልኩ ይሄንን ችግር ተቋቁመው ሊያልፉ እንደሚችሉ የመፍትሄ አቅጣጫ የሚያሳይ ነው። መፅሀፉ ‹‹ሁሉን በአንድ›› ሲባል እንደማንኛውም ሰው ፍቅር ተቀባይነትን፣ ሰው መወደድን፣ ብቻ የተለያዩ ሰሜቶችን አካቶ መመልከትን የሚያሳይ ነው። ‹‹ሁሉን በአንድ›› ሁሉን ሰሜቶች፣ ሀሳቦች አንድ ላይ የያዙ ልጆች ለማለት የተጠቀመችበት ስያሜ መሆኑን ታስረዳለች።
በኦቲዝም ጥላ ስር የሚገኙ ህፃናት ̋ካለብኝ ኦቲዝም ይልቅ ትኩረታችሁ እንደ ማንኛውም ልጅ ሰው መሆኔ ላይ ይሁን።” ይሉናል የምትለው ወይዘሮ መአዛ በስሜት ህዋሳት አማካኝነት የማገኛቸው መረጃዎች ከአብዛኛዎቻችሁ በተለየ ሊረብሹኝ ይችላሉ ትላለች። ̋አንዳንድ ነገሮች እንደተነገሩኝ ወዲያውኑ ላልረዳቸው እና ምላሽ ላልሰጥ እችላለሁ። በየእለቱ በድግግሞሽ የሚደረጉ ነገሮችን መረዳት ይቀለኛል። ድግግሞሽ የምማርበት መንገድ መሆኑን እወቁልኝ። ከሌሎች ልጆች ጋር አታነፃፅሩኝ። እጃችሁን እየጎተትኩ የምፈልገውን የማሳያችሁ በቃላት ሀሳብን እንዴት እንደምገልፅ ስለማላውቅ ነው። ስታስተምሩኝ በቃላት ብቻ ከምትነግሩኝ ይልቅ ብታሳዩኝ እና ብታስነኩኝ በቀላሉ ነገሮችን መረዳት እችላለሁ። ከሚያቅተኝ ነገር ይልቅ የምችለው ላይ አተኩሩ። ከሌሎች ጋር መሆን እፈልጋለሁ፤ ግን እንዴት ማድረግ እንዳለብኝ አስተምሩኝ። ያለምክንያት ውደዱኝ ይገባኛልና።” ይሉናል በማለት አንደበት ለሌላቸው አንደበት ትሆናለች።
ሌላው ከኦቲዝም ስንወጣ ሰው ልጅ መውለድ ሲባል እንደቀላል የሚያስበው ነገር በጣም ይገርማል። ሰው ልጅ ከመውለዱ በፊት የተለያዩ ዝግጅቶችን ማድረግ ይኖርበታል። ልጅ ከመወለዱ በፊት በርካታ ቅድመ ዝግጅቶች ያስፈልገዋል። ልጆች ከተወለዱ በኋላ ኃላፊነት መወሰድ ራስን መስጠት ነው። ወላጅነት ራስን መተካት ብቻ ሳይሆን ራስን መሰጠትም ነው።
ወላጆች ከተለያዩ ችግሮችና ጭንቀቶች ራሳቸውን አላቀው ነው መውለድ የሚገባቸው። ወላጆች አርአያ በመሆን ልጆችን ለማሳደግ በትክክል መነሳት አለባቸው። አንድ ሰው ስኬታማ ህይወት ለመምራት ከሚያስፈልጉት ክህሎት አንዱ የጠንካራ ስሜት ባለቤት መሆን ነው። የምትለው መአዛ ታዲያ ልጆች የጠንካራ ስሜት ባለቤት እንዲሆኑ ወላጆች ለልጆቻቸው የቀለም ትምህርት ስኬት አስፈላጊውን ድጋፍ እና ክትትል እንደሚያደርጉ ሁሉ ለልጆቻቸው ስሜት ትኩረት መስጠት ይኖርባቸዋል ትለናለች።
የልጆች የስሜት ብስለት መገለጫዎች የራስን የውስጥ ስሜት መረዳት፣ ስሜትን መቆጣጠር፣ የሌሎችን ስሜት መረዳት መቻል እና ከዚህም የተነሣ ጥሩ ማህበራዊ ግንኙነት መኖር ሲሆን ወላጆች የልጆችን ስሜት መቅረፅ ስናስብ ተገቢ የሆኑትን እና ተገቢ ያልሆኑትን ስሜቶች (ንዴት፣ ፍርሃት፣ ሀዘን፣ ቅናት፣ ጥላቻ፣ ቁጣና የመሳሰሉትን) በመለየት መርዳት ይቻላል።
ታዲያ ልጆች ተገቢ ያልሆነ ስሜት ሲያሳዩ እንዴት እንርዳቸው? የሚል ጥያቄ ከወላጆች ከተነሳ መልሱ ይሄ ነው ትለናለች ወይዘሮ መአዛ። የሚያሳዩትን ስሜት አቅሎ አለማየት። ልጅ ያልተገባ ስሜት ሲያሳይ በመደራደር እና በማታለል አለማስተካከል። ልጅ ስሜቱን በማልቀስም ሆነ በሌላ መንገድ እንዳይገለፅ አለመከልከል ናቸው። ይህም ቢሆን ግን ልጆች ያልተገባ ስሜት ሲያሳዩ ክስተቱን እንደ ጥሩ አጋጣሚ በመጠቀም ስሜቱን በምክንያታዊነት እንዲገልፅ ሠፋ ያለ ጊዜ ወስደው ስሜቱን እንዲረዳ አማራጭ መንገዶችን ማስተማርም ይጠበቃል።
ከዚህ ሁሉ በኋላም በልጆች የስሜት ብቃት እድገት ላይ በልጅ እና ወላጅ መካከል ያለ ጥብቅ ግንኙነት ወሳኝ እና ሚናውም ከፍተኛ መሆኑን ተረድተው በግዜ ይጠቀሙበት። “የራሱን ስሜት መቆጣጠር የቻለ ራሱን መምራት ቻለ፤ የሌሎችን ስሜት መረዳት የቻለ ተፅእኖ ፈጣሪ መሆን ቻለ” በማለት ወይዘሮ መአዛ ትመክራለች።
ልጆች የተሟላ እድገት እንዲኖራቸው ጨዋታ መሰረታዊ ነገር መሆኑን ወላጆች መረዳት እንዳለባቸው የምትናገረው ወይዘሮ መአዛ ስለጨዋታ ዘርዘር ያሉ ሀሳቦችን አካፍላናለች።
ጨዋታ ማለት ለልጆች ስራቸው ነው። ልጆች ጨዋታን በመጫወታቸው አካላዊ፣ አእምሯዊና ማህበራዊ እድገታቸው የተሟላ እንዲሆን ያግዛቸዋል፤ ደስታንም ያገኙበታል፤ ጨዋታ ልጆች ራሳቸው በፈቃደኝነት የሚፈጥሩት፣ በነፃነት ራሳቸው የሚመሩት፣ የሚቆጣጠሩት እና ድርጊቱን በማድረጋቸው የውስጥ እርካታን እና ስኬታማነትን የሚፈጥርላቸው ነው።
ጨዋታ በልጆች የእድገት ሂደት ውስጥ ብዙ ሚና አለው። በጨዋታ ውስጥ ልጆች እንደ ቀለማት፣ ቅርፃ-ቅርፅ፣ በነገሮች መካከል ስላሉ ግንኙነቶችና ልዩነቶች፣ ማህበራዊ ግንኙነት፣ አካላዊ እንቅስቃሴን ሁሉ ይማሩበታል።
ጨዋታ የልጆችን የቋንቋ፣ የማሰብ፣ የማስታወስ እና ችግር የመፍታት አቅምን ያዳብራል። በተጨማሪም ማህበራዊ ግንኙነት፣ ተራ መጠበቅ፣ በጋራ ተባብሮ መስራት፣ ለሌሎች መራራት፣ ማካፈልን፣ አክብሮትን እና በመደራደር ችግር መፍታትን ይማሩበታል። ጨዋታ ልጆች በውስጣቸው ያለን ደስታ፣ ችሎታ ፍርሃት፣ ሀዘን፣ ጭንቀት፣ ተስፋ፣ የሚወዱ እና የሚጠሉትን ነገር ይገልፁበታል። በልጆች የአእምሮ ጤና ምርመራ እና ህክምና ውስጥ ጥሩ ውጤት ለማግኘት የምንጠቀምበት አንዱ ዘዴ ጨዋታ ነው።
በጨዋታ ግዜ ወላጆች፣ ወንድም እና እህቶች ተሳታፊ ሲሆኑና አብረው ተረት ሲያነቡ፣ ኳስ ሲጫወቱ፣ አብረው ሳይክል ሲነዱ፣ ውሃ ሲራጩ እና የመሳሰሉ ድርጊቶችን ሲያደርጉ ልጆች የበለጠ በራስ መተማመናቸው እና አስፈላጊ ነኝ ብለው እንዲያስቡ ያደርጋቸዋል።
ምንም እንኳን ልጆች ቴሌቪዥን መመልከት፣ የኮምፒዩተር ጌም መጫወት እና በባትሪ የሚሰሩ የተለያዩ አሻንጉሊቶችን መጠቀም ቢወዱም ራሳቸው የሚፈጥሩትን ጨዋታ ያህል ከጨዋታ የሚገኙ ጥቅሞችን እንዲያገኙ አያግዛቸውም።
ልጆች መጫወት የሚገባቸው የጨዋታ አይነቶች፡- ሩጫ፣ መዝለል፣ አየሁህ/አየሁሽ መባባል፣ ስዕል መሳል፣ ከለር መቀባት፣ እቃ መደርደር ቤት መስራት፣ የተለያዩ የሚገጣጠሙ ነገሮችን መገጣጠም፣ የተለያዩ አሻንጉሊት ወንድ/ሴት እያደረጉ መጫወት፣ ገመድ መዝለል፣ አባሮሽ፣ እቃ-እቃ፣ የተለያዩ ሙያዎችንና አዋቂዎችን ማስመሰል፣ ድራማ መስራት፣ ሳይክል መንዳት፣ ኳስ መጫወት ወዘተ፤ በተለያዩ በዓሎች የተለያዩ የጨዋታ አይነቶች አሉ። ልጆች ከተወለዱ እስከ 12 ዓመት እንዲጫወቱ ማበረታታት እና ለንባብ/ለጥናት ግዜ እንደምንመድብ ሁሉ ለጨዋታም ጊዜ መመደብ ያስፈልጋል።
ጠንካራ ሀሳቦችን እያነሳች የኔ ጥያቄ ሳያስፈልጋት ሀሳቧን በተቀናጀ መልኩ ያካፈለችኝ ወይዘሮ መአዛን ክብረት ይስጥልኝ፤ እንዳንቺ ያልታዩትን የሚያዩ ሰዎችን ያበርክትልን እላለሁ። አመሰግናለሁ።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ሰኔ 13/2013